Saturday, September 30, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዓለምየአፍሪካ ኅብረት የቡድን 20 ቋሚ አባልነት ያገኝ ይሆን?

የአፍሪካ ኅብረት የቡድን 20 ቋሚ አባልነት ያገኝ ይሆን?

ቀን:

ህንድ የአፍሪካ ኅብረት የቡድን 20 (ጂ 20) ሙሉ አባል እንዲሆን ምክረ ሐሳብ ያቀረበችው በኒውደልሂ በተካሄደው የቡድኑ ጉባዔ ላይ ነው፡፡

የቡድን 20 ክፍል በሆነውና በዓለም አቀፍ ደረጃ በንግዱ ዓለም የተሰማሩ አካላት ሐሳባቸውን በሚገልጹበት ጉባዔ የተገኙት የህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ፣ ቡድን 20 አሳታፊ መሆን እንዳለበትና ለዚህም የአፍሪካ ኅብረት ሙሉ አባል እንዲሆን ሐሳብ ሰንዝረዋል፡፡

ቡድኑ አሳታፊ እንዲሆን የአፍሪካ ኅብረትን በቋሚ አባልነት መቀበል አለበት ያሉት ሞዲ፣ አፍሪካ ኅብረትም ቡድኑን እንዲቀላቀል ጋብዘዋል፡፡

ከጳጉሜን 4 እስከ 5 ቀን 2015 ዓ.ም. በህንድ ከሚካሄደው የቡድን 20 አባል አገሮች ጉባዔ አስቀድሞ በተካሄደው ጉባዔም፣ ዓምና በጠቅላላ የአገር ውስጥ ምርት ሦስት ትሪሊዮን ዶላር ያስመዘገቡት ፓን አፍሪካን በቡድኑ እንዲካተቱ ጥሪ ማቅረባቸውን አልጀዚራ ዘግቧል፡፡

የአፍሪካ ኅብረት የቡድን 20 ቋሚ አባልነት ያገኝ ይሆን? | Ethiopian Reporter | ሪፖርተር
የአፍሪካ ኅብረት የቡድን 20 ቋሚ አባል እንዲሆን የህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ጠይቀዋል (አሶሽየትድ ፕሬስ)

ቡድን 20 በኢኮኖሚ የበለፀጉ 19 አገሮችና የአውሮፓ ኅብረት የተቀናጁበት ነው፡፡ አባል አገሮቹም 85 በመቶ ያህሉን የዓለም ጠቅላላ የአገር ውስጥ ምርት ይይዛሉ፡፡ ሁለት ሦስተኛ የዓለም ሕዝብ በአባል አገሮቹ ይገኛል፡፡ ከአፍሪካ ደግሞ ደቡብ አፍሪካ ብቻ የቡድኑ አባል ናት፡፡

ከስምንት ወራት በፊት በአሜሪካ በተካሄደው የአሜሪካ አፍሪካ መሪዎች ጉባዔ፣ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን የአፍሪካ ኅብረት የቡድን 20 ቋሚ አባል እንዲሆን ድጋፍ እንደሚሰጡ መናገራቸው ይታወሳል፡፡

አፍሪካ በሁሉም ዘርፍ ከአሜሪካ ጋር ያላት ትብብር መጠናከር እንዳለበትና በዓለም አቀፍ ችግር ዙሪያ ውይይት ሲደረግም ሆነ በየትኛውም ተቋም ውይይት ሲኖር አፍሪካንም እንደሚመለከትም አክለዋል፡፡

የአፍሪካ ኅብረት የቡድን 20 አባል ለመሆን ረዥም ጊዜ ወስዶበታል፣ አሁን ጊዜው እየደረሰ ነው ሲሉም ለአፍሪካ መሪዎች ገልጸው ነበር፡፡

ከሳምንት በኋላ ህንድ በምታስተናግደው የቡድን 20 ጉባዔ፣ በአባላት መካከል ያሉ ልዩነቶችንና ውጥረቶችን ለማርገብ እየታገለች እንደሆነ ያነሳው የአልጀዘራ ዘገባ፣ በተለይ በሩሲያና ዩክሬን መካከል ያለውን ጦርነት አስመልክቶ ያሉ ልዩነቶችን ለማጥበብ እየሠራች እንደሆነ አስታውሷል፡፡

በሩሲያና ዩክሬን መካከል የተነሳውን ጦርነት ተከትሎ የምዕራቡ ዓለም ሩሲያን ማግለሉን የምትቃወመው ህንድ፣ ከሩሲያ ድፍድፍ ነዳጅ በመግዛት ግንባር ቀደም መሆኗንም አመላክቷል፡፡

55 አባል አገሮች ያሉትና አምስቱን መፈንቅለ መንግሥት በመደረጉ ምክንያት ያገደው የአፍሪካ ኅብረት፣ የቡድን 20 ቋሚ አባል እንዲሆን የወተወቱት አሜሪካና ህንድ ብቻ አይደሉም፡፡ ጥናት አድራጊዎችም አፍሪካ ኅብረት የቡድኑ ቋሚ አባል መሆን እንዳለበት ምክረ ሐሳብ ሰጥተዋል፡፡

በሚያዝያ 2015 ዓ.ም. ማብቂያ ኢትዮጵያን የጎበኙት የጀርመኑ መራሔ መንግሥት ኦላፍ ሾልዝ፣ አፍሪካ ኅብረት የቡድኑ አባል መሆኑን እንደሚደግፉ ማስታወቃቸውም ይታወሳል፡፡

የአፍሪካ ኅብረት የቡድኑ ቋሚ አባል ለመሆን ያቀረበውን ጥያቄ እንደሚደግፉ ከገለጹ አገሮች መካከል ፈረንሳይም ትገኝበታለች፡፡

የአፍሪካ ኅብረት ለመጀመርያ ጊዜ የቡድን 20 ጉባዔ ላይ የተሳተፈው እ.ኤ.አ. በ2010 ነው፡፡ ደቡብ አፍሪካ በተናጠል አባል ብትሆንም፣ የአፍሪካን ጉዳይ ከራሷ አጀንዳ አስቀድማ ልታነሳ አትችልም፡፡

ዘ አፍሪካን ሪፖርት እንደሚለውም፣ አፍሪካውያን እንደ አውሮፓውያን በኅብረታቸው መወከልና ድምፃቸው መሰማት አለበት፡፡

አፍሪካ ኅብረትን የቡድን 20 አባል ማድረግ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለሚመዘገበው ዕድገትና የተረጋጋ አስተዳደር አጠቃላይ መፍትሔ ለማምጣትም ያግዛል፡፡

አፍሪካ እምቅ ሀብት ያላት ሲሆን፣ የአውሮፓ ኅብረት አገሮች ብቻ 68 በመቶ ኮባልትና 36 በመቶ ታንታለም ከኮንጎ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ፣ 71 በመቶ ፕላቲኒየም ከደቡብ አፍሪካ ይወስዳሉ፡፡

በተናጠል ከአፍሪካ አገሮች ጋር ያላቸው ኢኮኖሚያዊ ግንኙነትም አፍሪካ ኅብረትን ከቡድን 20 የኢኮኖሚ ማኅበረሰብ እንዲቀላቀል የሚያደርግ ነው፡፡ ሆኖም እ.ኤ.አ. በመስከረም 1999 ማለትም ከ24 ዓመታት በፊት የተመሠረተው ቡድኑ አፍሪካ ኅብረትን ቋሚ አባል አላደረገም፡፡

ከሳምንት በኋላ በህንድ በሚካሄደው የቡድን 20 ጉባዔ የአፍሪካ ኅብረት የቋሚ አባልነት ጥያቄ ምላሽ ያገኝ ይሆን?

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የአማራ ክልል ወቅታዊ ሁኔታ

እሑድ ጠዋት መስከረም 13 ቀን 2016 ዓ.ም. የፋኖ ታጣቂዎች...

ብሔራዊ ባንክ ለተመረጡ አልሚዎች የውጭ አካውንት እንዲከፍቱ ለመጀመሪያ ጊዜ የፈቀደበት መመርያና ዝርዝሮቹ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የውጭ ምንዛሪ አጠቃቀምንና ተያያዥነት ያላቸው ጉዳዮችን...

እነ ሰበብ ደርዳሪዎች!

ከሜክሲኮ ወደ ዓለም ባንክ ልንጓዝ ነው። ሾፌርና ወያላ ጎማ...