የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ሥልጠና ቢሮ፣ ከግል ድርጅቶች ጋር በአጋርነት መሥራት የሚያስችል ረቂቅ መመርያ ማዘጋጀቱን አስታወቀ፡፡
ቢሮው ይህን ያስታወቀው መስከረም 10 ቀን 2016 ዓ.ም. በንፋስ ስልክ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ፣ የመጀመርያውን ረቂቅ መመርያ የሚመለከታቸው አካላት እንዲተቹት ባዘጋጀው መድረክ ነው፡፡
በቴክኒክና ሙያ ተቋማት አማካይነት የሚሰጡ ሥልጠናዎችን ውጤታማ ለማድረግ ከግል አምራች ኢንዱስትሪዎችና ከአገልግሎት ሰጪዎች ጋር በትብብር በመሥራት፣ በተቋማቱ ውስጥ የሚሠለጥኑ ተማሪዎች 30 በመቶ የንድፈ ሐሳብና 70 በመቶ የተግባር ሥልጠና እንዲወስዱ የሚረዳ መመርያ መሆኑን የቢሮው የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክተር አቶ አብረኃለይ ገብረ ሊባኖስ ተናግረዋል፡፡
ከማሠልጠኛ ተቋማትና ከግል አገልግሎት ሰጪ ድርጅቶች ጋር በአጋርነት መሠራት እንዳለበት በትምህርትና ሥልጠና ፖሊሲ ላይ የተገለጸ ቢሆንም፣ እስካሁን ድረስ ወጥነት ያለው የአሠራር ሥርዓት ተዘርግቶለት እየተተገበረ ባለመሆኑ በሚጠበቀው ልክ ውጤታማ እንዳልነበረ የገለጹት፣ የመመርያውን ረቂቅ በመድረኩ ያቀረቡት በንፋስ ስልክ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ አሠልጣኝና የፕሮጀክት አስተባባሪ አቶ ሙሉጌታ ዓለሙ ናቸው፡፡
‹‹ይህ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ የመጣውን ለኢንዱስትሪው የበቃ የሰው ኃይል በማቅረብ የሥልጠና ጥራትና አግባብነትን ማረጋገጥ ላይ ተፅዕኖ እየፈጠረ በመሆኑ፣ ቢሮው የአጋርነት የአሠራር ሥርዓት አንዲኖረው መመርያ አዘጋጅቷል፤›› ሲሉ አቶ ሙሉጌታ አስረድተዋል፡፡
የመንግሥት ማሠልጠኛ ተቋማትና የግል ድርጅቶች በአጋርነት እንዲሠሩ ወጥ የሆነ፣ ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለው ሥርዓት በመዘርጋት የከተማዋን ነዋሪዎች ተጠቃሚነት የሚያሳድግ መመርያ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
መመርያው በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ውስጥ ባሉ ከመንግሥት የቴክኒክና ሙያ ማሠልጠኛ ተቋማትና ጋር አጋርነት በፈጠሩ የግል አገልግሎት ሰጪ ድርጅቶች መካከል ተፈጻሚ እንደሚሆን የገለጹት አቶ ሙሉጌታ በጨርቃ ጨርቅ፣ በቆዳና የቆዳ ውጤቶች፣ በእንጨትና በብረታ ብረት ምርቶች፣ በአግሮ ፕሮሰሲንግ፣ በኮንስትራክሽን የማጠናቀቂያ ምርቶችና በብሎኬት ምርት፣ በኤሌክትሮኒክስና በሜካኒካል ማሽነሪዎች ጥገና፣ በአውቶሞቢል፣ በኮንስትራክሽን፣ በሆቴልና ቱሪዝም፣ በአይሲቲ አገልግሎቶች ላይ ተፈጻሚ እንደሚሆን አቶ ሙሉጌታ ገልጸዋል፡፡
በሁለቱ አካላት መካከል የሚደረገው የአጋርነት የቆይታ ጊዜ በውል ስምምነት ፊርማ መሠረት በዓመቱ የሚታደስ እንደሆነ፣ ሪፖርተር ያገኘው ረቂቅ መመርያ ይገልጻል፡፡
በተፈጠረው የአጋርነት የአሠራር ሥርዓት መሠረት ውጤት ማስመዝገብ ያልቻሉ የመንግሥት የማሠልጠኛ ተቋማት፣ በውል መሠረት ተጠያቂ እንደሚሆኑ በመመርያው ተጠቅሷል፡፡
ከሁለት አንደኛው ወገን ግዴታውንና ኃላፊነቱን ካልተወጣና ከአጋርነት ስምምነቱ ውጪ የሆነ ድርጊት ፈጽሞ ከተገኘ፣ የውል ስምምነቱ በየትኛውም ጊዜ መቋረጥ ይችላል ተብሏል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ተቋማትን መልሶ ማደራጀት አዋጅ ቁጥር 79/2015 በተሰጠው ተግባርና ኃላፊነት የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ሥልጠና ቢሮ የማሠልጠኛ ወርክ ሾፖች ከሥልጠና ባሻገር የማምረቻ ማዕከላት እንዲሆኑ፣ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች ጋር የአጋርነት፣ የትስስርና የትግበራ ሥርዓት መዘርጋት፣ መቆጣጠርና ክትትል የማድረግ ኃላፊነት የተሰጠው መሆኑ ይታወቃል፡፡
በተጨማሪም በዝቅተኛና በመካከለኛ ደረጃ ብቁ የሰው ኃይልን በማፍራት፣ ለኢንዱስትሪው እንደሚያቀርብ ቢሮው የተቋቋመበት ዋነኛ ዓላማ መሆኑ ይታወቃል፡፡
ሆኖም በመድረኩ የተገኙ የግል አምራች ድርጅቶች የቴክኒክና ሙያ ተቋማት፣ ኢንዱስትሪው የሚያስፈልገውን ያህል ብቁ የሰው ኃይል እያቀረቡ እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡