‹‹በዚህች ‹ጠብታ እና ቅጽበት›› በተሰኘች መለስተኛ ድርሰት ውስጥ ምጥን እና ዝንቅ የሆኑ የትዝብት፣ የኩሸት፣ የተግሳፅ እና የጥያቄ ሐሳቦቼን ከምናብ ወንዜ ጨልፌ አቅርቤያለሁ፡፡ ልክ ባልትና ቤቶች በርበሬና ሽሮ ሌላውንም ቅመም በማቀናበር አሽገው ለገበያ እንዲያቀርቡ፣ እዚህች መጽሐፍ ውስጥም እንደ በርበሬ ወይም እንደ ሽሮ ለየብቻቸው በሰፊው ሊቀርቡ የሚችሉ ሐሳቦች በትዝብት ማንኪያ እየተቆነጠሩ ተቀላቅለው ይገኛሉ፡፡ ከሚዛን ልክ አልፈው እንዳያከስሩ፣ ጎለውም ኃጢያት እንዳይሆኑ ያለ ቃላት ጋጋታና ያለ ህፀፀ ሐተታ በሚገባቸው ልክ ለሆድ መጣማቸው፣ ለህሊና መሞታቸውና ከመንፈስ መስማማታቸው እየታዩ ቀርበዋል፡፡››
በመግቢያው ላይ የተጻፈው ይህን ሐተታ ያቀረቡት ‹‹ጠብታ እና ቅጽበት›› በሚል ርዕስ መጽሐፍ ያሳተሙት እፁብ ድንቅ ስለሺ (ዶ/ር) ናቸው፡፡ በመጽሐፋቸው 567 አጫጭር ወጎቻቸውን አቅርበዋል፡፡
የዚህ ጽሑፍ መሠረቶች የቆሎ ተማሪነትና በኋላም የጉልምስና ጨዋታና ልዩ ልዩ ትዝብቶቻቸው መሆኑን የገለጹት ደራሲው፣ ያቀረቧቸው አሳቦች እንደ ለማኝ እንጀራ ልዩ ልዩ ናቸው ይላሉ፡፡ ‹‹ለማኝ ካንዱ ቤት የነጭ ጤፍ፣ ከሌላው ቤት የቀይ ጤፍ፣ ከሌላው ቤት ሌላ ነገር ይቀበላል፡፡ ሊጎርስ እጁን ወደ አኮፌዳው ሲሰድ የሚያገኘው ብዙ ነገር የተጠናቀረበት ጉርሻ ነው፡፡ የዓባይ ወንዝንም ብናይ ልዩ ልዩ ከሆኑ ሽጦችና ትናንሽ ገባር ወንዞች ጠብታዎች ተጠራቅመው እንደገነቡት እንረዳለን፡፡ ባንዷ የግዮን ጠብታ የብዙ ወንዞች ቀና፣ ቀለም፣ ጥራትና ድፍርስነት ሊገኝ ይችላል፡፡ በዚህች መጽሐፍም ጠብታዎች ከተለያዩ ገጠመኞች (ሸጦች) ተጉዘው፣ ባንድ ሰው ዓለም ማያ (መነጽረ ህሊና) ተዳውረው፣ በስሙር ኅብረት የማይነጥፍ የሐሳብ ወንዝ ሁነዋል ብየ አስባለሁ፣›› ብለዋል
በመጽሐፉ ያነሷቸው አሳቦች ከረዥሙ የሰው ልጅ ምድራዊ ኑሮ እንደየአጋጣሚው በተለያየ ቅጽበት የታዘቡትንና የተደነቁበትን፣ ያዩትንና ያሳዘናቸውን በየጊዜው በጋን መዝገባቸው ውስጥ አከማችተው፣ ያለማንዛዛት ባጭሩ ማቅረባቸውን ጠቁመዋል፡፡