የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን በግብርና ሚኒስቴርና በሥሩ በሚገኙ ዘጠኝ ተጠሪ ተቋማት ውስጥ ለሙስና ተጋላጭ ያላቸውን አሠራሮችና ዘርፎች በሚመለከት ባደረገው የዳሰሳ ጥናት፣ ሚኒስቴሩ ለከፍተኛ ሙስና ተጋላጭ የሚያደርጉት አሠራሮች መኖራቸውን ማረጋገጡን ይፋ አደረገ፡፡
ከተቋማቱ ነባራዊ ሁኔታና ቁመና በመነሳት ያለባቸውን የሙስና ሥጋት የዳሰሰ ጥናት ማክሰኞ ጥቅምት 27 ቀን 2016 ዓ.ም. የግብርና ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማቱ፣ እንዲሁም የኮሚሽኑ ሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት ይፋ ተደርጓል፡፡
በግብርና ሚኒስቴር ግምታቸው 131 ሚሊዮን ብር የሚሆኑ ግዥዎች በፕሮፎርማ ወይም በዋጋ ማቅረቢያ የግዥ ዘዴ የተከናወኑ መሆናቸው፣ በስድስት ሚሊዮን ብር ያለ ዕቅድ የተፈጸመ ግዥ መኖሩ፣ ግምታቸው ግማሽ ቢሊዮን ብር፣ እንዲሁም 270 ሺሕ የአሜሪካ ዶላር የሚያወጡ ከአንድ አቅራቢ ብቻ የተገዙ ዕቃዎች መገኘታቸው ተቋሙ ለሙስና ከፍተኛ ተጋላጭነት ያለበት መሆኑን ያሳያል ተብሎ በጥናቱ ተመልክቷል፡፡ በተመሳሳይ የኢትዮጵያ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኤጀንሲ ያለ ዕቅድ ግዥ 73 ሚሊዮን ብር መፈጸሙን፣ እንዲሁም በ ፕሮፎርማ 32 ሚሊዮን ብር ግዥ እንደተገኘበት ተገልጿል፡፡
በጥናቱ መሠረት ለሙስና ተጋላጭ ከተባሉት አሠራሮችና ዘርፎች የኅብረት ሥራ ማኅበራትና አሠራራቸው፣ የማዳበሪያ ግዥ ዋጋ መናርና የሥርጭት ችግር፣ የማዳበሪያ አቅርቦትና ከወደብ በወቅቱ በሚፈለገው ፍጥነት አለመነሳት ለሙስና የተጋለጡ አሠራሮች መሆናቸውን የኮሚሽኑ የሙስና መከላከል ጥናት ዴስክ ኃላፊ አቶ ተስፋዬ ከፈለ ባቀረቡት የጥናት ሰነድ ተመላክቷል፡፡
የግብርና ምርት አቅርቦትና ኤክስፖርት አስተዳደር፣ የአበባ ልማትና ኢንቨስትመንት መሬት አጠቃቀም፣ የእርሻ መሬት ለኢንቨስትመንት የሚሰጥበት አሠራር፣ የፕሮጀክት አስተዳደርና አፈጻጸም፣ የመስኖ ግድቦች ሕጎችና የተጠያቂነት ጉዳይ ለሙስና የተጋለጡ መሆናቸውን አቶ ተስፋዬ ጥናቱን አጣቅሰው አስረድተዋል፡፡
አቶ ተስፋዬ ባቀረቡት ጥናት በተቋማቱ ውስጥ በርካታ የፕሮፎርማ ግዥዎች መስተዋላቸውን፣ ከአንድ ድርጅት ብቻ የሚሰበሰቡ ፕሮፎርማዎች መብዛታቸው፣ ክፍያ ማዘግየት፣ ፕሮጀክቶች የደረሱበት ደረጃ ሳይታወቅ የሚፈጸም ክፍያ መኖር፣ ሊገዛ የሚፈለገው ንብረት መኖሩ ሳይረጋገጥ ግዥ መፈጸም፣ በማዳበሪያ ሥርጭት መዘግየት ምክንያት ለሕዝቡ የተዛቡ መረጃዎች መስጠት የሚሉት የሙስና ሥጋት መገለጫዎች መሆናቸው ተጠቅሷል፡፡
ፀረ ሙስና ኮሚሽን ሁሉም የመንግሥት ሠራተኞችና ባለሥልጣናት ሀብት እንዲያስመዘግቡና እንዲሳያውቁ በጀመረው ሥራ፣ በዲጂታል መንገድ አስመዝግቡ ከተባሉ 27 የሥራ ኃላፊዎች መካከል ሦስቱ አለማስመዝገባቸው በጥናቱ ተካቷል፡፡
የግብርና ሚኒስትር ደኤታዋ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) ኮሚሽኑ ከሰዎች ንክኪ የፀዳ የሀብት መመዝገቢያ ዲጂታል ዘዴ ይፋ አደረግኩ ቢልም፣ አሁን የማይሠራ መሆኑን ጠቁመው፣ ኮሚሽኑ ጠያቂ ብቻ ሳይሆን በዚህ ጉዳይ ሊጠየቅ ይገባል ብለዋል፡፡
ኮሚሽኑ ለሀብት ምዝገባ ያመቻል በማለት ያመጣው አሠራር አለመሥራቱን ጠቅሰው፣ ‹‹ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ስለአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ እያስተማሩ ባሉበት በዚህ ወቅት፣ እኛ በወረቀት የምንሞላ ከሆነ፣ ትንሽ ስላሚያስቸግር ወደ መዘመን ብትሄዱና የት ላይ እንዳላችሁ ራሳችሁን ብትፈትሹ ጥሩ ነው፤›› ብለዋል፡፡