Thursday, November 30, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

[ክቡር ሚኒስትሩ ለሚመሩት ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት ተጠሪ የሆነው ተቋም የዋና ሥራ አስኪያጅና ለእሳቸውም የቅርብ ወዳጅ የሆኑትን ግለሰብ ቢሯቸው አስጠርተው ከበላይ አካል እንዲሰጡ የታዘዙትን ደብዳቤ እያዘኑ አቀበሏቸው] 

  • የምን ደብዳቤ ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • ከበላይ አካል የተወሰነ ነው።
  • የምን ውሳኔ ነው?
  • እስኪ ተመልከተው።
  • እሺ… አዋከብኩዎት አይደል …. ምን? ምንድነው ክቡር ሚኒስትር? ከሥራ መሰናበትዎን ስለማሳወቅ ነው እኮ የሚለው፡፡
  • እኔም ልክ እንደተነገረኝ በጣም ነው የተገረምኩት።
  • ክቡር ሚኒስትር ምንድነው የተፈጠረው?
  • አንተ አቅም ያለህ ባለሙያ በመሆንህ የትኛውም ቦታ ተቀጥረህ መሥራት የምትችል ነህ፣ የትኛውም ተቋም እጅህን ስሞ ነው የሚቀበልህ፣ ስለዚህ ብዙ ሊያሳስብህ አይገባም።
  • ደብዳቤው እኮ የተባረርኩበትን ምክንያት አይገልጽም።
  • ስለእሱ ብዙ ባትጨነቅ?
  • እንዴት ክቡር ሚኒስትር? ስንት ዓመት ከሠራሁበት ተቋም በሁለት መስመር ደብዳቤ እንዴት በድንገት እባረራለሁ? ለዚያውም ምክንያቱ ሳይነገረኝ?
  • ምክንያቱንማ ምን ብለው ይገልጹታል?
  • እንዴት?
  • የሚሆን ነገር አይደለማ… ያሳጣቸዋል።
  • እና እርስዎም ምክንያቱን አያውቁትም ክቡር ሚኒስትር?
  • እኔማ ምክያቱን በግልጽ ካልተነገረኝ ደብዳቤውን አልሰጥም በማለቴ ነግረውኛል።
  • ምንድነው ምክንያቱ?
  • ባለፈው ግምገማ ላይ በሰጠኸው አስተያየት ነው፣ በእርግጥ እኔም ምክንያቱ ይህ እንደሚሆን ጠርጥሬ ነበር።
  • ለምን?
  • ግምገማው ላይ የሰጠኸው አስተያየት ለችግሩ መንግሥትንና የመንግሥት ተቋማትን በቀጥታ ተጠያቂ ያደረገ ነው።
  • እውነታው እንደዚያ ከሆነ ምን ማድረግ እችላለሁ ክቡር ሚኒስትር?
  • ቢሆንም… ቢሆንም…
  • በተጨማሪም መንግሥት በግልጽ እንድንነጋገር አቅጣጫ አስቀምጧል።
  • ቢሆንም በዚያ ደረጃ በቀጥታ ትችትና ወቀሳ መሰንዘርህ ትክክል አይደለም።
  • እና ምን ማድረግ ነበረብኝ ክቡር ሚኒስትር?
  • ሐሳብህን በሥልት ማቅረብ ትችል ነበር።
  • የምን ሥልት?
  • ለምሳሌ የመንግሥት ተቋማትን ከፍተኛ አመራሮችን በቀጥታ ተጠያቂ ሳታደርግ ሐሳብህን ማቅረብ ትችል ነበር።
  • ችግሩን መፍታት ያልተቻለው እኮ እነዚህ ተቋማት ኃላፊነታቸውን እየተወጡ ባለመሆኑ ነው።
  • ገብቶኛል።
  • እና ኃላፊነታቸውን ባለመወጣታቸው መወቀስ የለባቸውም ክቡር ሚኒስትር?
  • እንደዚያ ማለቴ አይደለም።
  • እ…?
  • ይህንኑ ሐሳብህን በሌላ መንገድ መግለጽ ትችል ነበር ማለቴ ነው።
  • በሌላ መንገድ ሲሉ ምን ማለትዎ ነው?
  • መንግሥትንና ተቋማትን በጥቅሉ ከምተቸት ይልቅ በሌላ መንገድ መግለጽ ትችል ነበር።
  • ለምሳሌ?
  • ለምሳሌ አንዳንድ የመንግሥት ተቋማት ማለት ትችል ነበር።
  • እህ…?
  • እንዲያውም ከዚህ የተሻለ አገላለጽ መጠቀም ትችል ነበር።
  • ቀደም ብለው ካነሱት ሌላ ማለት ነው?
  • አዎ፣ በቀጥታ ተቋማቱን ከመተች ይልቅ በሌላ መንገድ መግለጽ ትችል ነበር።
  • እንዴት?
  • ድብቅ አጀንዳና ተልዕኮ ያላቸው አንዳንድ አካላት ማለት ትችል ነበር።
  • እህ…?
  • አንተ ግን ከዚያ አልፈህ ከፍተኛ አመራሩ ማዕድ ማጋራት ላይ ተጠምዷል ብለህ እኮ ነው ያፍረጠረጥከው?
  • ቢሆንም አምኜበት ነው እንደዚያ የተናገርኩት ክቡር ሚኒስትር።
  • ሊሆን ይችላል፣ ግን ደግሞ የበላይ አመራሩን እንደሚያስቆጣ ተረድተህ በሌላ መንገድ ብትገልጸው ይሻል ነበር።
  • ቆይ ክቡር ሚኒስትር….
  • እ….
  • ዘርፉን የመከታተል ኃላፊነት የተጣለበት አካል ዋና ሥራውን ትቶ ትኩረቱን ማዕድ ማጋራት ላይ ማድረጉ መሠራታዊ ችግሩን ሊቀርፍ እንደማይችል አይታወቅም?
  • ሐሳብህ እኮ ችግር የለበትም።
  • ታዲያ?
  • ይህንኑ ሐሳብህን በሌላ መንገድ መግለጽ ትችል ነበር እያልኩህ ነው።
  • እንዴት አድርጌ?
  • መጀመሪያ መንግሥት ምንም የማይወጣለት ፖሊሲና ስትራቴጂ ቀርጿል ብለህ በማወደስ ትነሳለህ።
  • እሺ… ከዚያስ?
  • ዘርፉን የሚከታተለው የበላይ አካል ግን ጉድለት አለበት ማለት ትችል ነበር።
  • የምን ጉድለት ሲባልስ?
  • መፍጠንና መፍጠር ላይ ጉድለት አለበት ብትል የተሻለ ይሆን ነበር።
  • ያልኩት ይህንኑ ነው የሚያመለክተው።
  • ይህንንማ አይደለም።
  • መፍጠንና መፍጠር የሚል ቃል አልተጠቀምኩም እንጂ ያልኩት ይህንኑ ነው።
  • እንዴት?
  • አንድ ነገር ልጠይቅዎት ክቡር ሚኒስትር?
  • እሺ፡፡
  • አሁን የገጠመንን ችግር ማዕድ በማጋራት በዘላቂነት መፍታት ይቻላል ብለው ያምናሉ?
  • አይቻልም።
  • አመራሩ ማዕድ ማጋራት ላይ ተጠምዷል ስል ችግሩን በዘላቂነት የሚፈታ መፍትሔ ማፍለቅ ወይም መፍጠር አልቻለም ማለቴ ነው፣ በተጨማሪም…
  • ምን?
  • ማዕድ ማጋራት ችግሩን እያስታመመ ያቆየዋል፣ ይህ ደግሞ ከችግሩ ጋር አብሮ መዝለቅን እንጂ ፈጣን መፍትሔ አይደለም፣ በአጠቃላይ አመራሩ መፍጠርና መፍጠን አልቻለም ማለቴ ነበር።
  • ቢሆንም….
  • ቢሆንም ምን ክቡር ሚኒስትር?
  • በዚህ መንገድ የተረዳህ ሰው ያለ አልመሰለኝም።
  • እህ…
  • ገባህ አይደል?
  • አዎ ክቡር ሚኒስትር፣ መንግሥት መፍጠንና መፍጠር ይበል እንጂ የሚፈልገው ሌላ ነገር እንደሆነ ገብቶኛል።
  • ምንድነው?
  • ማጉረስና መወደስ!

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

የመቃወም ነፃነት ውዝግብ በኢትዮጵያ

ስሟ እንዳይገለጽ የጠየቀችው በአዲስ አበባ ከተማ በተለምዶ የሾላ አካባቢ...

የሲሚንቶን እጥረትና ችግር ታሪክ ለማድረግ የተጀመረው አጓጊ ጥረት

በኢትዮጵያ በገበያ ውስጥ ለዓመታት ከፍተኛ ተግዳሮት በመሆን ከሚጠቀሱ ምርቶች...

የብሔር ፖለቲካው ጡዘት የእርስ በርስ ግጭት እንዳያባብስ ጥንቃቄ ይደረግ

በያሲን ባህሩ በሪፖርተር የኅዳር 9 ቀን 2016 ዓ.ም. ዕትም “እኔ...

ሀብቱንና ትርፉን እያሳደገ የቀጠለው አዋሽ ባንክ

አዋሽ ባንክ በአዲስ አበባ ከተማ አዲስ ዋና መሥሪያ ቤት...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ የሩብ ዓመት የሥራ አፈጻጸማቸውን ለተከበረው ምክር ቤት ካቀረቡ በኋላ ከምክር ቤቱ አባላት የሚነሱ ጥያቄዎችን እየተቀበሉ ማብራሪያ በመስጠት ላይ ናቸው]

ክቡር ሚኒስትር መንግሥት ለሕዝብ ይፋ ያደረገው ነገር ከምን እንደደረሰ ቢያብራሩልን? ምንድነው ይፋ ያደረገው? ጥያቄውን ትንሽ ቢያብራሩት? ከአራት ዓመት በፊት በኦጋዴን አካባቢ ነዳጅ መገኘቱን ለሕዝብ በቴሌቪዥን አብስሮ...

[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ የካቢኔና የማክሮ ኢኮኖሚ ኮሚቴ አባል የሆኑ ከፍተኛ አመራር የሚያቀርቡትን ቅሬታ እያደመጡ ነው] 

ክቡር ሚኒስትር እየሆነ ያለው ነገር በእጅጉ ስላሳሰበኝ ነው በአካል አግኝቼ ላነጋግርዎት የፈለግኩት። ጥሩ አደረግህ፣ ምን አሳሳቢ ነገር ገጥሞህ ነው? ክቡር ሚኒስትር ተወያይተንና ተግባብተን ያስቀመጥናቸው አቅጣጫዎች፣ በተለይም...

[ጉባዔው በወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮች ላይ ክቡር ሚኒስትሩን ለመጠየቅና ምላሽና ማብራሪያቸውን ለማድመጥ ተሰብስቧል። የጉባዔው አባላትም ማብራሪያ የሚሹ ጥያቄዎቻቸውን ለክቡር ሚኒስትሩ እያቀረቡ ነው]

ክቡር ሚኒስትር፣ ይህ ጉባዔ ለሚያነሳቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ለመስጠት በመካከላችን ስለተገኙ አመሰግናለሁ። ክቡር ሚኒስትር፣ ኢትዮጵያ ባለፈው ዓመት የብሪክስ አባል እንድትሆን የሰጡት በሳል አመራር የሚደነቅ ነው። አገራችን...