- መንግሥት ሆደ ሰፊ በመሆን ታጣቂዎችም ትጥቃቸውን በመፍታት መነጋገር ይችላሉ ተብሏል
የአገራዊ ምክክር ኮሚሽነር መስፍን አራዓያ (ፕሮፌሰር) ታጣቂዎች ያለምክንያት ጫካ እንደማይገቡ ጠቅሰው የሰው ደም ሳይፈስ፣ አጀንዳዎች ወደ ምክክር እንዲመጡ ጠየቁ፡፡
ዋና ኮሚሽነሩ የተቋማቸውን የ2016 ዓ.ም የመጀመሪያ አራት ወራት ዕቅድ አፈጻጸም ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጥቅምት 29 ቀን 2016 ዓ.ም. ባቀረቡበት ወቅት ‹‹እኛ የሰላምን ጥያቄ ነጥለን ታጣቂዎችን ፕሪቶሪያ ወይም ዛንዚባር ወስደን የምናደርግበት ዘዴ የለንም፣ ነገር ግን እናበረታታለን›› ብለው፣ ምክር ቤቱ አስፈጻሚው ላይ ጫና እንዲያደርግ ጠይቀዋል፡፡
‹‹ጉልበት ያላችሁ እናንተ ናችሁ፤ ስለዚህ ወደ ሰላም ኑ፣ መንግሥትም ሆድህን አስፋ ተቀባይ ሁን፣ እናንተም ትጥቃችሁን አስቀምጣችሁ ወደዚህ ኑ፣ የሚለውን ነገር ከእኛ ይልቅ ጉልበትና አቅም ያላችሁ እናንተ ናችሁ፤›› በሚል ለፓርላማው ጥያቄ አቅርበዋል፡፡
‹‹የትም አገር የተካሄደ ውጊያ መጨረሻው ውይይት በመሆኑ ከመተላለቃችንና ከመጨፋጨፋችን በፊት አሁንም አልመሸም፣ ይህ ጉዳይ በምክር ቤቱ ፊት ሊተላለፍ ይገባል ፣ ወደ ምክክር እንምጣ ›› የሚል ጥሪ አቅርበዋል፡፡
‹‹ጉዳዩ ውስብስና ግዙፍ እንደሆነ እንደምትረዱ ይገባኛል›› አንድ ምክክር ውጤታማ ይሆናል የሚባለው በአብዛኛው አሳታፊ ሆኖ ኮሚሽነሮች በሚያወጡት ዕቅድ ብቻ ሳይሆን፣ የሕዝቡን ሐሳብ ወስዶ በማዳመጥ የየዓውዱን ሁኔታ ተረድቶ ተሳታፊዎችን ሲያስመርጥና አጀንዳ ሲሰበስብ ነው›› ያሉት ደግሞ ምክትል ዋና ኮሚሽነር ሒሩት ገብረሥላሴ ናቸው፡፡
‹‹በጣም በቆዩ ችግሮች ላይ የሚካሄድ ምክክር እንደመሆኑ መጠን በጣም በጥንቃቄ ልንሄድበት ይገባል›› ብለዋል፡፡
ኮሚሽኑ በአንዳንድ ክልሎች ነፍጥ ካነሱ አካላት ጋር የጀመረው ጥረት ካለ ተብሎ የተጠየቀውን ጥያቄ ሲመልሱ፣ ኮሚሽኑ በጀመረው የምክክር ሒደት ላይ እየሠራበትና እየገፋበት ሲመጣ፣ እነዚህን የማኅበረሰብ ክፍሎች በሒደቱ ማካተት አስፈላጊነት ለማንም ግልጽ ስለመሆኑ ተናግረዋል፡፡
በመሆኑም እነዚህን አካላት በምክክር ሒደቱ ለማካተት ለሚመለከታቸው አካላት በማሳወቅ ጥረት እየተደረገ መሆኑንና የተለያዩ ባለድርሻ አካላትን በማነጋገርና እነዚህ አካላትንም በተወካይ ለማነጋገር ጥረት እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ግጭት ያለባቸው አካባቢዎች ችግሩ መፈታት እንዳለበት የገለጹት ምክትል ኮሚሽነሯ፣ የምክክር ሥራውን በስኬት ለማጠናቀቅ ይህ የሚደረገው ጥረት መቀጠል እንዳለበትም ተናግረዋል፡፡ አገሩ በጣም ትልቅ፣ ሰፊ ሕዝብ፣ በርካታና የቆዩ ችግሮች ያሉበት በመሆኑ፣ ሥራውን ግዙፍ አንዳደረገው የሚናገሩት ኮሚሽነር ሒሩት፣ ሕዝቡ የሚጠበቀው ትልቅ ነገር በመሆኑና ሁሉም ችግር በኮሚሽኑ የሚፈታ የሚመስላቸው መኖራቸው በራሱ ያስጨንቀናል ብለዋል፡፡
ኮሚሽኑ የሚያወጣውን ዕቅድ ለመፈጸም አዳጋች ማነቆዎች እንደገጠመውና በአንዳንድ ክልሎች ሥራ ለመጀመር ታቅዶ ከሁለት ወር በላይ መሄድ አለመቻሉን ተናግረዋል፡፡
አገራዊ ኮንፈረንሱ በሚካሄድበት የምክክር ሒደት የተወሰኑ ችግሮች ተነቅሰው ከወጡ፣ ሁለት ክልሎች አንድ ቦታ ተቀምጠው እንደሚነጋገሩ የገለጹት ምክትል ኮሚሽነሯ፣ የጥቂት ክልሎች የጋራ ችግሮች በሚኖርበት ጊዜ በልዩ መስተንግዶ ይስተናገዳል ብለዋል፡፡
ዋና ኮሚሽነሩ የሚዲያን አጠቃቀም በተመለከተ ‹‹ግብር የምንከፍልባቸው የራሳችን ሚዲያዎች ሳይቀሩ የተዛቡ መረጃዎች ያቀርቡ እንደነበር›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ከምክር ቤቱ ዘገያችህ በሚል የተነሳውን ጥያቄ ሲያብራሩ ከኮሚሽኑ ቁጥጥር ውጪ የሆኑ ያልተጠበቁ ዕሳቤዎች ማጋጠማቸውንና በዚህም የተነሳ ኮሚሽኑ በዕቅዱ መሠረት መሄድ አልቻለም የሚሉት ኮሚሽነሩ፣ ነገር ግን ‹‹ፓርላማው አይ የተወሰኑትን ክልሎችና ሰላም የሆኑትን አነጋግሩና በዚያ ላይ ውይይት አካሂዱ ብላችሁ ብትሰጡን ግን አገራዊ አይሆንም›› ብለዋል፡፡ ‹‹እንዴት አድርገን ትግራይን ትተን አገራዊ ምክክር እናካሂዳለን፣ እንዴት አድርገን ብዙ የኦሮማያ ዞኖች ያልተካተቱበትን ትተን ምክክር እናካሂዳለን፣ እነዚህ ሁሉ ግምት ውስጥ መግባት አለባቸው ብለዋል፡፡