በአፍሪካ ከ72 ሚሊዮን በላይ ወጣቶች አልተማሩም፣ ሥራ አልተቀጠሩም ወይም ሥልጠና አላገኙም፡፡ ከእነዚህም አብዛኞቹ ሴቶች ናቸው፡፡
አፍሪካ በ2030 የዘላቂ ልማት ግብ ስምንት፣ ማለትም ለሁሉም ሥራ የሚለውን ለማሳካት የፆታ እኩልነትንና የወጣቶች ሥራ ፈትነትን መቅረፍ ይጠበቅባታል፡፡
ሆኖም አሁን ላይ በአፍሪካ ከአራት ወጣቶች አንዱ ሥራ የለውም፣ አልተማረም ወይም ሥልጠና የለውም፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ሁለት ሦስተኛው ሴቶች ናቸው፡፡
አፍሪካ የሕዝብ ቁጥሯ በተለይም የወጣቱ እየጨመረ መምጣቱ ለአኅጉሪቱ ዕድገት መልካም ቢሆንም፣ ፈተና ይዞም መጥቷል፡፡ ለወጣቶች ትምህርት የማዳረስና ሥራ የመቅጠር ሁኔታ ለአብዛኞቹ የአፍሪካ አገሮች ፈተና ሆኗል፡፡
ዓለም አቀፉ የሥራ ድርጅት በ2023 ሪፖርቱ እንደሚለውም፣ 11.2 በመቶ ወጣት አፍሪካውያን ሥራ የላቸውም፡፡ 60 ሚሊዮን ወጣት ያልሆኑ አፍሪካውያን ደግሞ ትምህርት አልተማሩም፣ ሥራም አልተቀጠሩም፡፡ ይህ ቁጥር ባለፉት ሁለት ዓመታት ከነበረው ለውጥ አላሳየም፡፡
ከእነዚህ አብዛኞቹ የችግሩ ሰለባ የሆኑት ሴቶች ሲሆኑ፣ ተምረው ሥራ ለመቀጠር ከወንዶች ይልቅ ችግር የሚገጥማቸውም ሴቶች ናቸው፡፡
ከሰሃራ በታች በሚገኙ የአፍሪካ አገሮች፣ ወጣት ሴቶች ቢማሩም ለመቀጠር ያላቸው ዕድል አነስተኛ ነው፡፡ በከፍተኛ ደረጃ የተማሩ ሴቶችም ቢሆኑ፣ ሥራ የማግኘት ዕድላቸው ከወንዶች ዝቅተኛ መሆኑን ያነሳው ዓለም አቀፉ የሥራ ድርጅት፣ ችግሩ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ አሳስቧል፡፡
በአፍሪካ ትምህርት አጠናቀው ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የተመረቁ ወጣቶች ሥራ ፍለጋ የሚባዝኑ መሆኑን ራይት ፎር ኢዱኬሽንም ይገልጻል፡፡ በአኅጉሪቱ የሚታየው የወረደ የመማር ማስተማር ሥርዓት፣ የኢኮኖሚ ማሽቆልቆል፣ የፖለቲካ አለመረጋጋት በአፍሪካ ያሉት የሥራ ገበያዎች ውስን መሆን ለወጣቱ መቀጠር ፈተናም ሆነዋል፡፡
ወጣቶችን ወደ ሥራ ለማስገባት በቅድሚያ የትምህርት አሰጣጥንና የክህሎት ሥልጠና ማሻሻል እንደሚገባ፣ ለወጣቶች በቂ የሥራ ፈጠራ እንዲኖር የሚያስችል ፖሊሲ እንደሚያስፈልግም ራይት ፎር ኢዱኬሽን መክሯል፡፡
ዓለም አቀፍ የሳይንስ የትምህርትና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) ከዓለም አቀፉ የሥራ ድርጅት ጋር በመሆን መንግሥታት፣ የግል ድርጅቶችና ዓለም አቀፍ ለጋሾች ለወጣቶች ሥራ የሚፈጥሩና በትምህርት ቤትና በሥራ መካከል ያለውን የሽግግር ሒደት የሚያሻሽሉ የተሟሉ ፖሊሲዎችንና ስልቶችን እንዲከተሉ ሐሳብ ያቀረቡት ከዓመታት በፊት ነው፡፡
ለደመወዝ፣ ለሥራ ደረጃዎች፣ ለወጣቶች ማኅበራዊ ጥበቃን ለማሻሻል ፖሊሲዎችን እንዲያሻሽሉ፣ ችግረኛ ወጣት ሴቶች ላይ የሚያነጣጥሩ ፕሮግራሞች እንዲቀረፁ ችሎታቸውንና የመቀጠር ዕድላቸውን እንዲያሰፉ መርዳት ያስፈልጋልም ብለዋል፡፡
ዝቅተኛ ወይም ምንም ዓይነት መሠረታዊ ትምህርት ወይም ችሎታ ለሌላቸው ግለሰቦች ትምህርት ወይም ሥልጠና እንዲያገኙ በማስቻል ቀጣይ የሕይወት ዘመናቸውን እንዲያስተካክሉ መርዳት ያስፈልጋል ሲሉም መክረዋል፡፡
የወጣቶችን ድምጽ ማዳመጥና ለውይይት ዕድሎችን መፍቀድ፣ ያስፈልጋል ያሉት ድርጅቶቹ፣ ወጣቶች በሚያውቁትና አሠሪዎች በሚያስፈልጓቸው የሥራ መስክ መካከል ያለውን አለመጣጣም ለመፍታት መሥራትም እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል፡፡