Wednesday, December 6, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜና‹‹አሁን በሚደረጉ ግራና ቀኝ ትግሎች መንግሥትን ማሸነፍ ከባድ ነው›› ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ...

‹‹አሁን በሚደረጉ ግራና ቀኝ ትግሎች መንግሥትን ማሸነፍ ከባድ ነው›› ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር)

ቀን:

  • በዶላር ከመገዳደል በሐሳብ መገዳደር ይሻላል ብለዋል

ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) አሁን እየተደረጉ ባሉ ግራና ቀኝ ትግሎች መንግሥትን ማሸነፍ ይከብዳል አሉ፡፡

ዓብይ (ዶ/ር) እንዳሉት ከቀዝቃዛው ጦርነት በኋላ በአንድም የዓለም አገር የታጠቁ ኃይሎች ተደራጅተውና ተዋግተው መንግሥትን አሸንፈው አያውቁም፡፡ ‹‹እዚህ የሚታገሉ ሰዎች ግን ይህን የሚያውቁ አይመስለኝም፤›› ያሉት ማክሰኞ ኅዳር 4 ቀን 2016 ዓ.ም. የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ላቀረቡላቸው ጥያቄዎች በሰጡት ምላሽ ነው፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ መስከረም 28 ቀን 2016 ዓ.ም. ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ለሕዝብ ተወካዮችና ለፌዴሬሽን ምክር ቤቶች ባቀረቡት የፌዴራል መንግሥት ዓመታዊ ዕቅድ የመክፈቻ ንግግር፣ ከምክር ቤት አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ነው ማብራሪያ የሰጡት፡፡

ኢትዮጵያ በደርግ ዘመነ መንግሥት የነበራት አጠቃላይ አገራዊ ምርት አሥር ቢሊዮን ዶላር ገዳማ እንደነበር፣ ነገር ግን አሁን የአገሪቱ የካፒታል ፕሮጀክት በጀት ብቻ ከአሥር ቢሊዮን ዶላር በላይ መድረሱን ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም አገሪቱ ከቸገራትና በህልውናዋ ከመጣ፣ እነዚያን ፕሮጀክቶቿን አዘግይታ ራሷን መከላከል ትችላለች ብለዋል፡፡ አሥር ቢሊዮን ዶላር ታጥቀው ለሚታገሉ አካላት መርዳት ቀርቶ ማበደር የሚችል አንድ መንግሥት በዓለም ላይ የለም ሲሉ አስታውቀዋል፡፡

 በአንድ በኩል የውጭ ምንዛሪ የለም እየተባለ በሌላ በኩል ደግሞ በኮንትሮባንድ መሣሪያ እየገባ መሆኑን ጠቁመው፣ ‹‹ለኢትዮጵያውያን ያለኝ ምክር በዶላር ከመገዳደል በሐሳብ መገዳደር ይሻላል፤›› ብለዋል፡፡

በአማራ ክልል የታወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አንፃራዊ ሰላም ማምጣቱንና የክልሉን መንግሥት ከመፍረስ መታደግ መቻሉን፣ ነገር ግን የተሟላ ሰላም ባለመምጣቱ ተጨማሪ ውይይትና ሥራ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል፡፡ ይሁን እንጂ የነበረው ሥጋት ግን ተቀልብሷል ሲሉ አስረድተዋል፡፡

ባለፉት አምስት ዓመታት በብልፅግና የሚመራውን መንግሥት ደርግ፣ ሸኔ፣ እንዲሁም ደግሞ ዘውዳዊ ነው የሚል ስያሜ እንደሚሰጠውና ብልፅግና መቼም በአንዴ ሦስቱንም መሆን አይችልም ብለዋል፡፡ ‹‹ይህ የሚያሳየው ስሜትና ሴራ በመብዛታቸው የሚወጡ የዳቦ ስሞች በራሳቸው ገላጭ መሆን አይችሉም፡፡ በመሆኑም እነዚህ የዳቦ ስሞች እኛን አይገልጹንም፣ እኛ ለየትኛውም ሠፈር ፅንፍ የወጣ ዋልታ የረገጠ ዕሳቤ መጠቀሚያ አንሆንም፤›› ብለዋል፡፡

የተዛባ፣ ነጠላና አፍራሽ ትርክት አገር የማይገነባ በመሆኑ አገራዊ ትርክት መፍጠር እንደሚያስፈልግ ገልጸው፣ ‹‹አብዝተን የምንሻው ሰላም በአገራችን እንዲሰፍን ነው፤›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡

‹‹ባለፉት አምስት ዓመታት በእኛ መሻትና በእኛ ዕቅድ አንድም ጦርነት አልተካሄደም፡፡ ይህ እውነት ነው፣ አንድም ግጭት እኛ አቅደንና አስበን ጀምረን አናውቅም፡፡ አንዱ ይነሳና ሁለት ወር ይበቃኛል ይላል፡፡ ያም ይነሳና ይህንን መንግሥት በቀላሉ በኃይል እገለብጠዋለሁ ይላል፣ ያኔ መቼም አልሞት ባይ ተጋዳይ ሆነን እንከላከላለን እንጂ፣ እስካሁን ለማጥቃት ተነስተንና ሙከራ አድርገን አናውቅም፤›› ብለዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአማራና የኦሮሞ ሕዝቦች በሰላም ለመኖር ያላቸው ምርጫ ቢፈልጉም ባይፈልጉም የአንድ አባት ልጆች፣ የአንድ አገር ዜጎች፣ እህትና ወንድማማቾች መሆናቸውን አውቀው ተከባብሮ አብሮ ለመኖር በሚያስችል ማንነት መጓዝ ብቻ ነው ብለዋል፡፡ አክለውም ከዚያ ውጪ ያለው አማራጭ ምንም ፋይዳ እንደሌለውና ውጤትም እንደማያስገኝ ገልጸው፣ ሌሎች ብሔሮችም ቢሆኑ ከየትኛውም ኢትዮጵያዊ ጋር በሰላምና በፍቅር፣ እንዲሁም በትብብር ከመኖር ውጪ ያለው አማራጭ አዋጭ አይደለም ሲሉ አሳስበዋል፡፡

በኢትዮጵያ በጣም በርካታ ጥያቄዎች የነበሩ ቢሆንም ብልፅግና የሚወቀስ ከሆነ ለመፍታት ባደረገው ድፍረቱ መሆኑን አስረድተው፣ በርካታ ጥያቄዎች ተመልሰዋል፡፡ ሙሉ በሙሉ ግን ተመልሷል ማለት አይቻልም ብለዋል፡፡

በአማራና በትግራይ ክልሎች የሚነሱ የይገባኛል ጥያቄዎችን ለመፍታት መንግሥት የሕዝበ ውሳኔ አማራጭን መከተል የተሻለ መሆኑን አምኖ ሁለቱን ክልሎች ማወያየቱንና አቅጣጫ ማስቀመጡን ጠቅሰው፣ አሁንም እየተሠራበት እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ ‹‹ነገር ግን ይህ ምርጫ ብቸኛ ባለመሆኑ የሁለቱ ክልሎች ምሁራን፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የአገር ሽማግሌዎች ተወያይተው ዘላቂ ሰላም የሚያመጣ መፍትሔ አለን ካሉ በደስታ እንቀበላለን፡፡ የሚፈለገው ነገር ሁለቱ ክልሎች በሰላም እንዲኖሩና ሕግን በተከተለ መንገድ በሕገ መንግሥቱ መሠረት የሕዝቡን ውሳኔ የተከተለ አማራጭ ያስፈልጋል፤›› ብለዋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ታዋቂው የኤሌክትሮኒክስ ብራንድ አይቴል የስትራቴጂ ለውጥ አካል የሆነውን አዲስ አርማ እና መለዮ ይፋ አደረገ።

በአለማችን ታዋቂ ከሆኑት የኤሌክትሮኒክስ ብራንዶች መካከል አንዱ የሆነው እና...

የጠቅላላ ጉባኤ ስብሰባ ጥሪ ለሸገር አነስተኛ የፋይናንስ ተቋም አ.ማ ባለአክሲዮኖች በሙሉ

ለሸገር አነስተኛ የፋይናንስ ተቋም አ.ማ ባለአክሲዮኖች በሙሉ የሸገር አነስተኛ የፋይናንስ...

[የክቡር ሚኒስትሩ ጸሐፊ፣ የሌላ ሚኒስትር ጸሐፊ ከሆነችው የቅርብ ወዳጇ ጋር በስልክ እየተጨዋወቱ ነው]

አንቺ ግን ምን ሆነሽ ነው? ጠፋሁ አይደል? ጠፋሁ ብቻ?! ምን ላድርግ ብለሽ...

በሱዳን ላይ ያጠላው የመከፋፈል ዕጣና ቀጣናዊ ተፅዕኖው

የሱዳን ጦርነት ስምንተኛ ወሩን እያገባደደ ይገኛል፡፡ ጄኔራል አብዱልፈታህ አልቡርሃን...