በአዲሱ ዓመት መባቻ መስከረም 14 ቀን 2010 ዓ.ም. በታዋቂው የበርሊን ማራቶን ውድድር የዓለም ሦስት ታላላቅ የማራቶን ሯጮችን ያገናኛል፡፡ ኢትዮጵያዊው ቀነኒሳ በቀለ ከሁለቱ ኬንያውያን ኢሉድ ኪፕቾጌ እና ዊልሰን ኪፕሳንግ ጋር ይፎካከራል፡፡
የዓለም ማራቶን ክብረወሰን በተደጋጋሚ ያስተናገደችው የጀርመኗ በርሊን ከተማ የምታገናኛቸው ሦስቱ ዕውቅ የጎዳና ላይ ፈርጦች ከወዲሁ ዝግጅታቸውን የጀመሩ ሲሆን፣ አዲስ ሪከርድም ያስመዘግባሉ ተበሎ ይጠበቃል፡፡ ኪፕቾጌ የአገሩ ልጅ ዴኒስ ካሚቶ የገባበትን 2፡02.57 ክብረወሰን እንደሚሰብር እየተነገረ ይገኛል፡፡ ቀነኒሳ ለስምንተኛ ጊዜ የሚያከናውነውን የማራቶን ውድድር እንደምንጊዜውም በቂ ዝግጅት ማድረጉም ታውቋል፡፡
ውድድሩ ከሌላው ጊዜ በተሻለ ትልቅ ትኩረትን የሳበ መድረክ ሆኗል፡፡ በጎዳናው ውድድር ላይ የሚሳተፉት ሦስቱ አትሌቶች ያላቸው ተቀራራቢ ሰዓት ፉክክሩን የበለጠ አጓጊ ያደርገዋል፡፡
ዘንድሮ በተደረገው የበርሊን ማራቶን ቀነኒሳ በቀለ 2፡03.03 በድል በማጠናቀቅ ያስመዘገበው ጥሩ ሰዓቱ ነው፡፡ ከሦስት ዓመት በፊት የመጀመሪያውን ማራቶን ውድድር ያደረገው ቀነኒሳ 2፡05.04 በመግባት ስድስተኛው ምርጥ ሰዓት ሆኖ ተመዝግቦለታል፡፡ የወቅቱ የዓለም ሁለተኛ የማራቶን ክብረወሰን ባለቤት የሆነው ቀነኒሳ በዘንድሮ ካከናወናቸው የማራቶን ውድድሮች መካከል የዱባይና የለንደን ውድድሮች ተጠቃሾች ናቸው፡፡ ለንደኑ ማራቶን ላይ መነሻ ቦታ ላይ በተፈጠረ መገፋፋት ከግማሽ በላይ ርቀት መጓዝ ባይችልም፣ ከወራት ቆይታ በኋላ በለንደን ማራቶን ላይ በመሳተፍ ኬንያዊውን ዳንኤል ዋንጅሩ በመከተል 2፡05.57 በመግባት አጠናቋል፡፡
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድን ወደ ለንደን ዓለም ሻምፒዮና ሲያመራ በማራቶን ይሳተፋል ቢባልም በወቅታዊ አቋም ምክንያት መሳተፍ እንደማይችል መግለጹ ይታወሳል፡፡
42.195 ኪሎ ሜትር በሚሸፍነው ማራቶን የቀድሞው ባለ ክብረወሰን ዊልሰን ኪፕሳንግም ይጠበቃል፡፡ ኪፕሳንግ በ2006 ዓ.ም. በተደረገው የበርሊን ማራቶን 2፡03.23 ማጠናቀቁ የሚታወስ ነው፡፡ ኪፕሳንግ የሁለት ጊዜ የፍራንክፈርት ማራቶን (እ.ኤ.አ. በ2010 እና 2011) ያሸነፈ ሲሆን፣ (2012 እና 2014) ለንደንና ኒዮርክ ማራቶንን እንዲሁም ዘንድሮ (2017) ቶኪዮ ማራቶን ማሸነፍ ችሏል፡፡
በተጨማሪም በግማሽ ማራቶን 58፡59 በመግባት የራሱን ምርጥ ሰዓት ማስመዝገብ ችሏል፡፡ አትሌቱ ካለው የጎዳና ላይ ልምድ አንፃር በዘንድሮ በርሊን ማራቶን ትልቅ ግምት ተሰጥቶታል፡፡ በዓምናው የበርሊን ማራቶንም ኪፕሳንግ 2፡03፡13 በማጠናቀቅ አራተኛውን ፈጣን ሰዓት አስመዝግቧል፡፡ አትሌቱ በበርሊን ማራቶን ላይ ድል ለመቀዳጀት ከምንጊዜውም በላይ ዝግጅቱን እያደረገ እንደሆነ አስተያየቱን ሰጥቷል፡፡
ሌላኛው ተፎካካሪ ኢሉድ ኪፕቾጌ ሲሆን፣ ከመም ውድድሮች ጀምሮ እስከ ጎዳና ድረስ ትልቅ ልምድ ያለው አትሌት ነው፡፡ እ.ኤ.አ. ከ2003 ጀምሮ በ5,000 ሜትር ውድድሩን ማድረግ የጀመረው አትሌቱ በዓለም ሻምፒዮና፣ በኦሊምፒክና የዓለም የቤት ውስጥ ሻምፒዮና በረዥም ርቀት በመሳተፍ ውጤታማ ሆኗል፡፡
በተለይ በጎዳና ላይ ሩጫ እ.ኤ.አ. 2013 በርሊን 2፡04.5 በመግባት፣ 2014 ቺካጎ ማራቶን 2፡04.11 በማጠናቀቅ፣ ሮተርዳም 2፡05.00 እና በ2016 ለንደን ማራቶን 2፡03.05 ሪከርድን ማስመዝገብ ችሏል፡፡
እ.ኤ.አ. ከ1974 ጀምሮ የተለያዩ የጎዳና ላይ ውድድሮችን ሲያዘጋጅ የነበረው በርሊን ማራቶን እስካሁን ከተደረጉት የማራቶን ውድድሮች እ.ኤ.አ. 2014 ዴኒስ ካሚቶ የገባበት 2፡02፡57 የዓለም ክብረወሰን ተደርጎ ተመዝግቧል፡፡ በውድድሩ በሁለቱም ጾታ አሸናፊ ለሚሆኑ ለሽልማት ከአንድ ሚሊዮን ዶላር በላይ ተዘጋጅቶላቸዋል፡፡
የወንዶች የበርሊን ማራቶን ክብረወሰን |
|||
1998 |
ሮናልዶ ዳ ኮስታ |
ብራዚል |
2፡06፡05 |
2003 |
ፖል ቴርጋት |
ኬንያ |
2፡04፡55 |
2007 |
ኃይሌ ገብረሥላሴ |
ኢትዮጵያ |
2፡03፡59 |
2008 |
ኃይሌ ገብረሥላሴ |
ኢትዮጵያ |
2፡03፡38 |
2011 |
ፓትሪክ ማክዋ |
ኬንያ |
2፡03፡23 |
2013 |
ዊልሰን ካፕሰንግ |
ኬንያ |
2፡03፡23 |
2014 |
ዴኒስ ካሚቶ |
ኬንያ |
2፡02፡57 |