ፕሬዚዳንት ሙላቱ ተሾመ
ኢትዮጵያ ሦስተኛውን ሚሊኒየም የተቀበለችበት አሥረኛ ዓመትና የዘመን መለወጫ ክብረ በዓል መጀመርን ይፋ ያደረጉት ፕሬዚዳንት ሙላቱ ተሾመ (ዶ/ር)፣ ያለፉት አሥር ዓመታት ጉዞ አልጋ በአልጋ እንዳልነበር አስታወቁ፡፡
ፕሬዚዳንቱ የክብረ በዓሉን መጀመር ሐሙስ ነሐሴ 25 ቀን 2009 ዓ.ም. በሸራተን አዲስ ሆቴል ይፋ ሲያደርጉ ‹‹ባለፉት አሥር ዓመታት የሄድንበት የልማትና ፀረ ድህነት ትግል ስኬታማ የመሆኑን ያህል፣ አልጋ በአልጋ ነበር ማለት አያስደፍርም፤›› ብለዋል፡፡
ልማቱን ሊያደናቅፉ የሚችሉና ፈተና የነበሩ በርካታ ተፈጥሮአዊና ሰው ሠራሽ ችግሮች፣ ባለፉት አሥር ዓመታት አገሪቱን ገጥመዋታል ብለዋል፡፡
‹‹በተከታታይ የገጠመን የድርቅ አደጋ አንዱ ፈታኝ ችግር ነበር፤›› ያሉት ፕሬዚዳንቱ፣ ከዩኒቨርሲቲ ተመርቀው የሚወጡ ወጣቶች ቁጥር መጨመር በአንድ በኩል ደስታ በሌላ በኩል ተግዳሮት እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡
በየዓመቱ የሚመረቁ ወጣቶች ቁጥር እየጨመረና እነሱን ወደ ሥራ ፈጠራ ለማስገባት አለመቻል፣ ያለፉት አሥር ዓመታት ትልቅ ተግዳሮት እንደነበር ተናግረዋል፡፡
‹‹ከዚሁ እኩል የሕዝብ የልማት ፍላጎትና ይህንን ፍላጎት መመለስ አለመቻላችን ሌላው ተግዳሮት ነው፤›› ብለዋል፡፡
ለመንግሥት ሥልጣን የተዛባ አስተሳሰብ ያላቸው የመንግሥት ሹማምንት የፈጠሩት የሙስናና የመልካም አስተዳደር ችግሮችም ሌላ እንቅፋት እንደነበሩ ጠቅሰዋል፡፡ ችግሮቹን ለመቅረፍ መንግሥት ዛሬ ላይ ቆም ብሎ መሥራት እንዳለት ያሳሰቡት ፕሬዚዳንቱ፣ ይህንንም እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
‹‹ድህነትን ወደ መቃብሩ ካልወሰድነው ከዓለም ተለዋዋጭ ባህሪ አንፃር አሸናፊ ሆነን መውጣት አንችልም፤›› ብለዋል፡፡
በዚህ ሥነ ሥርዓት ላይ የተገኙት የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አቶ ድሪባ ኩማ በበኩላቸው፣ ‹‹በተግዳሮት በታጀበው የአሥር ዓመት ጉዞ በከተማዋ ስኬቶች ተመዝግበዋል፤›› ብለዋል፡፡
‹‹ሚሊኒየሙን ስንጀምር የነበረው የአንዳንድ መንደሮች ገጽታ በኮንዶሚኒየም ቤቶች ውበት ተቀይሯል፡፡ በቀላል ባቡር የዘመነው የትራንስፖርት አቅርቦት በሜትር ታክሲና በሸገር ባስ ታጅቧል፤›› ሲሉ ከስኬቶቹ መካከል ጠቃቅሰዋል፡፡
ባለፈው ሐሙስ ምሽት የተበሰረው የአዲስ ዓመት (2010) የመቀበያና ያለፉት አሥር ዓመታት ጉዞ መዘከሪያዎች በተለያዩ ፕሮግራሞች እንደሚከናወኑ ተገልጿል፡፡
ከእነዚህ መካከልም የሰላም ቀን፣ የኢትዮጵያ ቀን፣ ያለፉት አሥር ዓመታት ስኬቶችና ተግዳሮቶች መገምገሚያ ቀን ይገኙበታል፡፡