‹‹ኪነጥበብ አባቴ፣ ንጉሤና አሳዳሪዬ ነው፡፡ እፈራዋለሁ፡፡ አከብረዋለሁ፡፡ የኪነጥበብ ባሪያ ነኝ፤ ከኪነጥበብ የምለየው ስሞት ነው፡፡››
በ93 ዓመታቸው ዜና ዕረፍታቸው የተሰማው፣ ሁለገቡ የጥበብ ባለሙያ ተስፋዬ ሳህሉ ዓምና ለክብራቸው በተዘጋጀው መድረክ ላይ የተናገሩት፡፡
በብዙዎች ዘንድ ‹‹አባባ ተስፋዬ›› በመባል የሚታወቁት፣ ኪነጥበበኛው ተስፋዬ ሳህሉ ተዋናይ፣ ድምፃዊ፣ የተረት አባት፣ የግጥምና ዜማ ደራሲ፣ የዳንስ አሠልጣኝ፣ መድረክ መሪና ምትሀተኛ ነበሩ፡፡ ለአምስት አሠርታት ግድም ለኪነጥበብ ያበረከቱትን አስተዋጽኦ ለመዘከር የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባህል ማዕከል ሚያዝያ 13 ቀን 2008 ዓ.ም. ባዘጋጀው መድረክ ጥበባዊ ሥራዎቻቸው ተዘክረው ነበር፡፡