በኦሮሚያ ክልል የ17,126 ነጋዴዎች የቀን ገቢ ግምት እንዲስተካከል መደረጉን የክልሉ መንግሥት አስታወቀ፡፡
የኦሮሚያ ክልል የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ አዲሱ አረጋ ዓርብ ሐምሌ 21 ቀን 2009 ዓ.ም. ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ በክልሉ ከቀን ገቢ ግምት ጋር በተያያዘ 84,230 ነጋዴዎች ቅሬታ አቅርበዋል፡፡ ከእነዚህ መካከልም የ27,155 ነጋዴዎች ቅሬታ ውድቅ ተደርጓል፡፡ የነጋዴዎቹ ቅሬታ ውድቅ የተደረገው መንግሥት ባቋቋመው የቅሬታ ሰሚ ኮሚቴ ታይቶና ተመርምሮ ተገቢ ሆኖ ባለመገኘቱ እንደሆነም አቶ አዲሱ አስረድተዋል፡፡
የቅሬታ አቀራረብ መንገድ ተጠቅመው ቅሬታቸውን ካቀረቡት ነጋዴዎች መካከል፣ የ1,232 ነጋዴዎች የግብር መክፈያ ደረጃቸው መስተካከል መቻሉንም ገልጸዋል፡፡
ከእነዚህ ነጋዴዎች መካከል የአብዛኛዎቹ ነጋዴዎች የግብር ደረጃ ዝቅ እንደተደረገም ጠቁመዋል፡፡ በክልሉ ውስጥ ይቀርቡ የነበሩ ቅሬታዎች የአድማ መልክ በመያዝ ሱቆችን በመዝጋት፣ የትራንስፖርት አገልግሎት በማቋረጥና አልፎ አልፎ ደግሞ በጊንጪና በአምቦ አካባቢ ኃይል የተቀላቀለበት ረብሻ ያስነሱ እንደነበሩ አቶ አዲሱ አስታውሰዋል፡፡
ከዚህ በመነሳት ያለውን ችግር ለመፍታት በክልሉ ውስጥ ከሚኖረው የንግድ ማኅበረሰብ ጋር ተደጋጋሚ ውይይት መደረጉን ገልጸው፣ ‹‹በኦሮሚያ 328 ወረዳዎችና 18 ለክልሉ መንግሥት ተጠሪ የሆኑ ከተሞች ስላሉ፣ በእነዚህ አካባቢዎች ውስጥ ከሚኖሩ ነጋዴዎች ጋር ግልጽ ውይይት ተደርጓል፤›› ሲሉም አብራርተዋል፡፡ ከዚህ በመነሳት ነጋዴዎች በአሁኑ ወቅት ቅሬታቸውን ከአድማ ይልቅ በመደበኛ የመንግሥት አሠራር አቅርበው እንዲፈታ እያደረጉ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
በአሁኑ ጊዜ የክልሉ መንግሥት የንግዱን ማኅበረሰብ ቅሬታ ለመፍታት ዋነኛ የቤት ሥራው አድርጎ እየሠራ መሆኑን የገለጹት አቶ አዲሱ፣ የተነሱ ቅሬታዎች በዋናነት ከገማች ኮሚቴው የአሠራር ችግር ጋር የተያያዙ ሆነው መገኘታቸውንም አክለዋል፡፡ በተዘረጋው የቅሬታ ማቅረቢያ አሠራርም ገማቾች በሚገምቱበት ጊዜ፣ በተወሰኑ ነጋዴዎች ላይ የተጋነነ ግምት ሠርተው መገኘታቸውን ጠቅሰዋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል ሙሉ በሙሉ በሚባል ሁኔታ ባለፉት ሁለትና ሦስት ቀናት የንግድ ተቋማትና የትራንስፖርት አገልግሎቶች ምንም መስተጓጎል ሳይደርስ አገልግሎት እየሰጡ መሆናቸው ንም አቶ አዲሱ አስረድተዋል፡፡
በቅርቡ ከቀን ገቢ ግምት ጋር በተያያዘ በኦሮሚያ ክልል ተነስቶ በነበረው ተቃውሞ በሦስት ተሽከርካሪዎች ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱ ይታወሳል፡፡ የክልሉ ፕሬዚዳንት አቶ ለማ መገርሳ ባለፈው ሳምንት በወሊሶ ከተማ ከአካባቢው የንግድ ማኅበረሰብ ጋር ውይይት ማድረጋቸው አይዘነጋም፡፡