የሥነ ምግባር ጉድለት ተገኝቶባቸዋል በተባሉ 129 ዳኞች፣ የሕግ ኦፊሰሮችና ድጋፍ ሰጪ ሠራተኞች ላይ አስተዳደራዊ ዕርምጃ መወሰዱን የኦሮሚያ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት አስታወቀ፡፡
የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት አቶ አዲሱ ቀበኔሳ ለክልሉ ምክር ቤት ባቀረቡት ሪፖርት እንደናገሩት፣ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 500,000 የክስ መዝገቦች ቀርበው 517,000 የሚሆኑት መዝገቦች ውሳኔ አግኝተዋል፣ የበጀት ዓመቱ የሥራ አፈጻጸምም 91 በመቶ ነው፡፡
ምንም እንኳን ጥሩ የሆነ የሥራ አፈጻጸም የታየ ቢሆንም፣ በዘርፉ ይታዩ የነበሩ የሥነ ምግባር ጉድለቶች ለማስተካከል ጥረት ሲደረግ መቆየቱን አስረድተዋል፡፡ የተደረገውን ጥረት በመተላለፍ የሥነ ምግባር ጉድለት መፈጸማቸው በተረጋገጠባቸው 129 ዳኞችን፣ የሕግ ኦፊሰሮችና ድጋፍ ሰጪ ሠራተኞችን ከሥራ ከማሰናበት ጀምሮ ከደረጃ ዝቅ ማድረግና ከቦታ የማንሳት አስተዳደራዊ ዕርምጃ መወሰዱን ፕሬዚዳንቱ ገልጸዋል፡፡
ዳኞቹ፣ የሕግ ባለሙያዎቹና ድጋፍ ሰጪ ሠራተኞቹ የፈጸሙዋቸው የሥነ ምግባር ጉድለቶች ከተገልጋዮች ጉቦ መቀበል፣ የጥቅም ግንኙነት መፍጠር፣ ፍትሕ ማጓደልና አድሎአዊ አሠራር መሆናቸውን ፕሬዚዳንቱ ጠቁመዋል፡፡
በበጀት ዓመቱ ፍርድ ቤቶች ባደረጉት ጥረት ተገልጋዮች ባሉበት ሆነው የይግባኝ ጉዳዮችን እንዲከታተሉ የቪዲዮ ኮንፈረንስ አገልግሎት በማዘጋጀት፣ ከ360 በላይ መዝገቦች ላይ ውሳኔ መሰጠቱንና ተገልጋዮችን ከእንግልት ማዳን መቻሉን ፕሬዚዳንቱ ገልጸዋል፡፡
ከስምንት ዩኒቨርሲቲዎች ጋር በመሆን ሕፃናት፣ ሴቶችና አረጋውያን በነፃ ጥብቅና አገልግሎት እንዲያገኙ በመደረጉ ከ100,000 በላይ ዜጎች ተጠቃሚ መሆናቸውንና 46,000 ያህሉ ሴቶች መሆናቸውን አቶ አዲሱ አስረድተው፣ የኦሮሚኛ ቋንቋ ለማይችሉ 7,800 ሰዎችም አስተርጓሚ በመመደብ ጉዳያቸውን እንዲከታተሉ መደረጉንም አክለዋል፡፡