በቀለም ውስጥ የሚገኝን የሊድ መጠን መቆጣጠር የሚያስችል ረቂቅ ደንብ የአካባቢ ደንና አየር ንብረት ለውጥ ሚኒስቴር አዘጋጀ፡፡ ረቂቁ በቀለም ውስጥ የሚገኘውን የሊድ መጠን በሊትር ከ90 ሚሊ ግራም እንዳይበልጥ የሚከለክል ነው፡፡ በቀለም ብቻ ሳይሆን በሌሎች ምርቶች ላይ በተለይም በሕፃናት መጫወቻ ዕቃዎች ውስጥ የሚኖረውን የሊድ መጠንም መቆጣጠር የሚያስችል መሆኑ ታውቋል፡፡
በሚኒስቴሩ የፖሊሲ ሕግና ደረጃዎች ጥናትና ዝግጅት ዳይሬክቶሬት የፖሊሲ ጥናት ባለሙያው አቶ በላቸው ኃይለ ማርያም እንደሚሉት፣ የተዘጋጀው ረቂቅ በሊትር ከ90 ሚሊ ግራም በላይ የሊድ መጠን ያለው ምርት የሚያመርቱ፣ የሚያስመጡና የሚልኩ እንዲሁም የሚያከፋፍሉ ድርጅቶችና ግለሰቦችን የሚገድብ ነው፡፡
በተጨማሪም የቀለም ፋብሪካዎች ስለሚጠቀሟቸው የተለያዩ ኬሚካሎች ዝርዝር መረጃና ኬሚካሎቹ በጤና ላይ ስለሚፈጥሩት አሉታዊ ተፅዕኖ ማስጠንቀቂያ ጭምር የያዘ ሌብል (መግለጫ) በምርቶቻቸው ላይ እንዲለጥፉ የሚያስገድድም ነው፡፡ ረቂቁ በመስከረም 2010 ዓ.ም. ለሚኒስትሮች ምክር ቤት እንደሚቀርብም ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
በሌሎች አገሮች በቀለም ውስጥ የሚገኘው የሊድ መጠን ላይ ገደብ ከተጣለ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ አብዛኛዎቹ አገሮች 90 ሚሊ ግራም በሊትር (90 ፓርትስ ፐር ሚሊዮን) በሚለው መሥፈርት እየተጠቀሙ ይገኛሉ፡፡ በኢትዮጵያ ግን ኬሚካሉ በጤና ላይ ስለሚያስከትለው ጉዳት ግንዛቤው ባለመኖሩ እስካሁን ልኬት ሳይወጣለት ቆይቷል፡፡
ፔስቲ ሳይድ አክሽን ኔክሰስ አሶሴሽን የተባለው ድርጅት ባለፈው ሳምንት ያወጣው ጥናት እንደሚያመለክተው፣ ጉዳዩ አሳሳቢ ነው፡፡ በጥናቱ ከተካተቱት የቀለም ምርቶች 80 በመቶ የሚሆኑት 10 ሺሕ ሚሊ ግራም በሊትር የሊድ መጠን እንደተገኘባቸው ያሳያል፡፡ ብርትኳናማ ቀለም ባላቸው ሁለት ምርቶች ላይም 10 ሺሕ ፒፒኤም የሊድ መጠን መገኘቱን፣ ይህም ከተፈቀደው 90 ሚሊ ግራም በሊትር ልኬት 1100 ጊዜ የበለጠ እንደሆነ ወይም በሊትር 10 በመቶ መሆኑን በጥናቱ ተገልጿል፡፡
‹‹ኬሚካሉ በሕፃናት ዕድገትና ባህሪ ላይ የሚያደርሰው ተፅዕኖ ቀላል አይደለም፡፡ በጥቂት መጠን እንኳ ከተጋለጡ የመንቀዥቀዥና የትኩረት ማጣት ባህሪ ያሳያሉ፡፡ ተጋላጭነታቸው ከፍተኛ የሆኑ ልጆች ደግሞ በትምህርት ወደ ኋላ የመቅረት፣ የመስማትና ሌሎችም የዕድገት ችግሮች ያጋጥሟቸዋል፤›› በማለት የድርጅቱ ዳይሬክተር ታደሰ አመራ (ዶ/ር) የችግሩን አሳሳቢነት ገልጸዋል፡፡
ሁኔታው በየዓመቱ 600 ሺሕ ሕፃናት የመማር እክል እንዲኖርባቸው እያደረገ እንደሚገኝ፣ መካከለኛና ዝቅተኛ ገቢ ባላቸው አገሮች በየዓመቱ 977 ቢሊዮን ዶላር ኪሳራ እያደረሰ መሆኑን፣ በአፍሪካ ብቻ በየዓመቱ የሚደርሰው ኪሳራም 134.7 ቢሊዮን ዶላር እንደሆነ በሚኒስቴሩ የፖሊሲ ሕግና ስታንዳርዶች ዳይሬክተሩ አየለ ሄገና (ዶ/ር) ተናግረዋል፡፡
ለተለያዩ ምርቶች ግብዓት የሚሆኑ አደገኛ ኬሚካሎችን አጠቃቀም እስከ 2020 ድረስ በከፍተኛ መጠን ለመቀነስ ዕቅድ መያዙን አስታውሰው፣ በቀለም ውስጥና በተለያዩ ምርቶች ላይ የሚገኘው የሊድ መጠን ልኬት እንዲኖረው ማድረግ የተያዘውን ዕቅድ ዕውን ለማድረግ አንድ ዕርምጃ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡