Friday, December 8, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

ክቡር ሚኒስትሩ አንድ የባንክ ኃላፊ ጋ ደወሉ

  • ሰላም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • እንዴት ነህ ወዳጄ?
  • አለሁ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • አንተ በቃ እኔ ካልደወልኩ አትደውልም?
  • ምን ክቡር ሚኒስትር ያው ጊዜው ሒሳብ የምንዘጋበት ወቅት እኮ ነው?
  • እሱማ የጠፋኸው ለምን እንደሆነ ይገባኛል?
  • በጣም ቢዚ ነበርን፡፡
  • ያው ካገኘኸው ቦነስ ጋብዘኝ እንዳልልህ ነው አይደል?
  • ኧረ ሰሞኑን እንዲያውም አመም አድርጎኝ ነበር፡፡
  • ውይ ምነው?
  • ለሕክምና ወደ ውጭ ሄጄ ነበር፡፡
  • ያው ዳጐስ ያለ አበል ይዘህ ነዋ የሄድከው?
  • ኪኪኪ…
  • እንደ እርስዎ መስሎዎት ነው አይደል?
  • ማለት? አበል አልተሰጠኝም ለማለት ነው?
  • ኧረ እኔ ራሴ ባጠራቀምኳት ገንዘብ ነው የምታከመው፡፡
  • እሱን እንኳን ተወው፡፡፡
  • እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
  • የውጭ ምንዛሪው በእጅህ አይደል እንዴ ያለው?
  • ቢኖርስ ክቡር ሚኒስትር?
  • ያው የቻልከውን ያህል ዘገን አድርገህ ነው የምትሄደው ብዬ ነዋ፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ባንኩ እኮ የግሌ ሳይሆን የሕዝብ ነው፡፡
  • ታዲያ መቼም ውጭ አገር በኢትዮጵያ ብር አትገበያይ?
  • ክቡር ሚኒስትር እኔ ግን በራሴ ገንዘብ ነው የምታከመው፡፡
  • እኔ እኮ ጉንፋን ሲያመኝ ለአበሏ ስል ዘልዬ ባንኮክ ነው የምሄደው፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር እኛ ጋ ግን እንደዚያ የለም፡፡
  • ለማንኛውም ዛሬ ለቁም ነገር ፈልጌህ ነው፡፡
  • ምን ልታዘዝ ክቡር ሚኒስትር?
  • አዲሱ የበጀት ዓመት ጀመራችሁ አይደል እንዴ?
  • ልክ ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • አዲሱን ዓመትም እየተቃረበ ነው፡፡
  • እሱማ ትንሽ ይቀረዋል፡፡
  • አይ ያው ዝግጅቱን ከዚሁ ነው የምትጀምሩት ብዬ ነው፡፡
  • የምን ዝግጅት ክቡር ሚኒስትር?
  • ይኼ የካላንደርና የአጀንዳ ኅትመቱን ነዋ፡፡
  • እሱንማ ጨረታ አውጥተናል፡፡
  • ጨረታ ምን ያደርጋል?
  • እንዴት ማለት ክቡር ሚኒስትር?
  • እኛው ነና ጉዳዩን መጨረስ ያለብን፡፡
  • እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
  • ባለፈው ነግሬህ ነበር እኮ?
  • ምኑን ክቡር ሚኒስትር?
  • አዲስ ያቋቋምኩት ማተሚያ ቤት አለ ብዬ ነዋ፡፡
  • ተወዳደሩ እንጂ ክቡር ሚኒስትር?
  • እኔ እኮ በውድድር አላምንም፡፡
  • ታዲያ በምንድነው የሚያምኑት?
  • ልማታዊ አስተሳሰብ አለው ወይ በሚለው ነዋ፡፡
  • ይቅርታ ያድርጉልኝና ክቡር ሚኒስትር፣ እኛ ደግሞ በውድድር ነው የምናምነው፡፡
  • አንተ አይገባህም እንዴ?
  • ጨረታውን ካልተወዳደሩ ምንም ልረዳዎት አልችልም፡፡
  • እኔ እኮ ሁላችንም የምንጠቀምበትን መንገድ አስቤ ነው፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር አጣብቂኝ ውስጥ እየከተቱኝ ነው፡፡
  • የምን አጣብቂኝ ነው?
  • ያው ባንኩ እኮ በቦርድ ነው የሚመራው፡፡
  • ለሥራው አዲስ ነህ እንዴ? ከሌሎቹስ ጋር እንደዚህ አይደል እንዴ የምሠራው?
  • እኔ የሌሎቹን አላውቅም፡፡
  • አንተ ሐሳብ የሆነብህ ነገር ምንድነው?
  • ሥራዬን እንዳያሳጡኝ ነዋ፡፡
  • ስለእሱ አታስብ፡፡
  • የልጆች አባት እንደሆንኩ ያውቃሉ?
  • ከተባረርክም እኔ አስቀጥርሃለሁ፡፡
  • የት?
  • የእኛው ባንክ!

[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ የመንግሥት የልማት ድርጀት ኃላፊ ጋ ይደውላሉ]

  • ሰላም ወዳጄ፡፡
  • እንዴት ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • ዛሬ እንዴት ደወሉልኝ እባክዎ?
  • ለብርቱ ጉዳይ ፈልጌህ ነው፡፡
  • ምነው ያቺን ሪፖርት ፈልገው ነው?
  • የምን ሪፖርት ነው?
  • ባለፈው ቦርድ ስብሰባ ላይ የቀረበውን ነዋ፡፡
  • ስማ እኔና አንተ ከቦርድ ባለፈ ወዳጅነታችንን ማጠንከር አለብን፡፡
  • ካሉማ ደስ ይለኛል፡፡
  • አንተን ሳይህ ንቁ ነገር ስለሆንክ አንድ ፕሮጀክት አስቤልህ ነበር፡፡
  • አመሰግናለሁ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ያው ከፊታችን አዲስ ዓመት አለ፡፡
  • ግን ገና ነው እኮ ክቡር ሚኒስትር?
  • ቢሆንም አንድ ነገር አስቤ ነበር፡፡
  • ምንድነው ክቡር ሚኒስትር?
  • ያው ድርጅታችሁ ካላንደርና አጀንዳ ማሳተሙ አይቀርም ብዬ ነው፡፡
  • እሱማ በመላው አገሪቷና በውጭ ባሉን ኤምባሲዎቻችን ነው የምናሰራጨው፡፡
  • አየህ እዚህ ላይ ነው ጥሩ ሥራ የምንሠራው፡፡
  • ምን ክቡር ሚኒስትር?
  • ሥራውን ለእኔ ትሰጠኛለህ?
  • የምን ሥራ ክቡር ሚኒስትር?
  • የካላንደሩንና የአጀንዳውን ሥራ ነዋ፡፡
  • እንዴ ክቡር ሚኒስትር አካሄዱን እያወቁት?
  • አካሄዱ ምን ችግር አለው?
  • ማለቴ ስንትና ስንት የግዢ ሒደት አለዋ፡፡
  • ምን በፊት ከነበረው ኃላፊ ጋር እንደዚህ አይደል እንዴ የምንሠራው?
  • ቢሆንም ግን ትንሽ ያሠጋል፡፡
  • እኔው አይደለሁ እንዴ የቦርድ ሰብሳቢ?
  • እሱንማ አውቃለሁ፡፡
  • ታዲያ ከሥራዬ እንዳልፈናቀል ብዬ ነዋ፡፡
  • ብትፈናቀልስ?
  • የልጆች አባት መሆኔን ረሱት እንዴ?
  • ከዚህ የምታገኘው ኮሚሽን እኮ አንቀባሮ ነው የሚያኖርህ፡፡
  • ስለዚህ ክቡር ሚኒስትር?
  • ያዋጣሃል፡፡
  • ምኑ?
  • ሙስናው!

[ለክቡር ሚኒስትሩ አንድ ኢንቨስተር ይደውልላቸዋል]

  • ሄሎ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ዛሬ ከየት ተገኘህ እባክህ?
  • እኔ እኮ ዘመድ ጠያቂ ነኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • እሱ እንኳን ጉዳይ ሲኖርህ ነው የምትደውለው፡፡
  • በእውነት ዛሬ ሰላም ልልዎት ነው የደወልኩት፡፡
  • ቁም ነገረኛ ወጥቶሃል ማለት ነው?
  • በዚህ እንኳን አልታማም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ሥራ እንዴት ነው ታዲያ?
  • ያውቁት የለ የእኛን ሥራ፣ አንዱ ሲደክም ሌላው ይነሳል፡፡
  • ጥሩ ነው ይልቁንስ እንኳን ደወልክ፡፡
  • ምነው ክቡር ሚኒስትር?
  • እናንተ ካላንደርና አጀንዳ ታሳትማላችሁ አይደል?
  • ኧረ ለእኛ ሥራ እኮ እንደዚህ ዓይነቱ ነገር ብዙም አይጠቅምም፡፡
  • አየህ ቢዝነስህ የሚደክመው እኮ ለዚህ ነው፡፡
  • እንዴት?
  • ፕሮሞሽን ላይ እየሠራህ አይደለም?
  • ያው የእኛ ሥራ እኮ ኤክስፖርት ማድረግና እዚህ አገር የምናስገባቸውን ዕቃዎች መጋዘን ተከራይቶ መሸጥ ነው፡፡
  • ቢሆንም አየህ የምትሠራውን ሥራ ለመንግሥትም ሆነ ለሌሎች አካላት ማስተዋወቅ አለብህ፡፡
  • ታዲያ ምን እየመከሩኝ ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • ካላንደርና አጀንዳ ማሳተም ግዴታ ነው፡፡
  • ችግሩ ደግሞ የማውቀው ማተሚያ ቤትም የለም፡፡
  • ስለእሱ አታስብ፡፡
  • እንዴት?
  • እኔ ያስመጣሁዋቸው የማተሚያ ማሽኖች አሉ፡፡
  • እንደዚያ ከሆነማ ለእኔ ሥራ አቀለሉልኝ፡፡
  • ስለዚህ ሥራውን ትሰጠኛለህ?
  • አዎ ግን ከእርስዎም የምፈልገው ነገር አለ፡፡
  • ምን?
  • 10 ሺሕ ሔክታር መሬት!

[የክቡር ሚኒስትሩ ሚስት ስልክ ደወሉላቸው]

  • እሺ የእኛ አዋቂዎች፡፡
  • ምን እያልሽ ነው?
  • ምን እያደረጋችሁ እንደሆነ ታውቃላችሁ?
  • ያው አገሪቷን በልማት ጎዳና እያስጓዝናት ነው፡፡
  • እኔ አንድ ጥያቄ ልጠይቅህ?
  • ጠይቂኝ፡፡
  • ከልጅ ልጅ ቢለዩ፣ ዓመትም አይቆዩም ሲባል አልሰማህም?
  • ሰምቻለሁ፡፡
  • እኛ ታዲያ የእንጀራ ልጆች ነን?
  • ማን ናችሁ እናንተ?
  • እኛ ‹‹ሀ››ዎች፡፡
  • ‹‹ሀ››ዎች ስትይ?
  • እኛ ደረጃ ‹‹ሀ›› ግብር ከፋዮች፡፡
  • ራስሽን ከጉሊትና ከጀበና ቡና ሻጭ እኩል ማየት ጀመርሽ?
  • አየህ ግብር እኮ ለሁሉም ፍትሐዊ መሆን አለበት፡፡
  • እሱማ ፍትሐዊ ነው፡፡
  • ታዲያ ለምንድነው አንድ አገር ውስጥ ሁለት ዓይነት አሠራር የሚኖረው?
  • አንቺ ሴትዮ ጤነኛ ነሽ?
  • በጣም ጤነኛ ነኝ፡፡
  • ምን እያልሽ ነው ታዲያ?
  • በጣም ብዙ ሰዎችን እያስከፋችሁ ነው፡፡
  • ማለት?
  • የከተማው ሚሊየነር፣ ቢሊየነር እንዲሁም የከተማው ከፍተኛ ኢንቨስተር ተከፍቷል፡፡
  • እንዴት ነው እናንተ ከጉሊት ቸርቻሪ ጋር አንድ የምትሆኑት?
  • ምን አለበት?
  • ሴትዮ ምን ይደረግ እያልሽ ነው?
  • እኛ እንደ ጉሊት ቸርቻሪዎቹ ያመነውን እንክፈል፡፡
  • ኪኪኪ…
  • ምን ያስቅሃል?
  • ሲባል አልሰማሽም እንዴ?
  • ምን?
  • ነጋዴን ያመነ…
  • እ…
  • ጉም የዘገነ!

[ክቡር ሚኒስትሩ ለአንድ ኢንቨስተር ስልክ ደወሉ]

  • ሄሎ ወዳጄ እንዴት ነህ?
  • እንዴት ነዎት ክቡር ሚኒስትር?
  • ዛሬ ከየት ተገኙ?
  • ያው አንተ ስለማትደውል፣ እኔ ልደውል ብዬ ነው፡፡
  • ሥራ ስለሚበዛብኝ እኮ ነው፡፡
  • እስቲ ስለአንዳንድ ነገር እንወያይ ብዬ ነው፡፡
  • ስለምን ክቡር ሚኒስትር?
  • ያው እናንተ ትልልቅ ባለሀብቶች ስለሆናችሁ ካልረዳችሁን የት እንደርሳለን ብለህ ነው?
  • የቻልነውን እያደረግን ነው እንግዲህ?
  • አሁን ካሳዑዲ የሚመጡ ወገኖቻችንን እዚህ ለማቋቋም አስበናል፡፡
  • ጥሩ ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ግን የእናንተንም ዕርዳታ እንፈልጋለን፡፡
  • እና ከሕዝብ ገንዘብ ሊሰበስቡ ነው?
  • መጀመሪያማ ከባለሀብቱ ነው እንጂ፡፡
  • እኛ ምን በወጣን?
  • ምን እያልክ ነው?
  • በቃ ሁሉም በዚህ መዋጮ በምትሉት ነገር ደስተኛ አይደለም፡፡
  • ለምን?
  • የሚወራውን አይሰሙም እንዴ ክቡር ሚኒስትር?
  • ምን ተወራ ደግሞ?
  • ባለፈው ለቆሼ ተብሎ በገንዘብና በዓይነት ከመቶ ሚሊዮን ብር በላይ ነው የተሰበሰበው፡፡
  • ጥሩ ነዋ ታዲያ?
  • ግን ተጎጂዎቹ በሚገባ እየተረዱ አለመሆኑን ሚዲያዎች እያናፈሱት ነው፡፡
  • ወሬኞች በላቸው፣ አርፈው ሥራቸውን አይሠሩም?
  • ይኼ አይደል እንዴ ሥራቸው?
  • ማቃጠር?
  • ማቃጠር ሳይሆን በተለያዩ አካላት የሚሠሩ ስህተቶችን ማጋለጥ፡፡
  • እነሱ እባክህ ያልበላቸውን ነው የሚያኩት፡፡
  • እሱ ብቻ አይደለም፡፡
  • ሌላ ምን አለ?
  • ይኸው በዚህ 40/60 እንኳን ስንቱ ሙሉ ክፍያ ከፍሎ ቤት ሲጠባበቅ ጥቂቶች ብቻ ነው ቤት ያገኙት፡፡
  • መንግሥት እንግዲህ የቻለውን እያደረገ ነው፣ ከዚህ በላይ ምን ይደረግ?
  • እኔማ ክቡር ሚኒስትር ለሳዑዲ ተመላሾች ብለው አፍዎን እንዳያበላሹ ብዬ ነው፡፡
  • ማለት?
  • የሚወራውማ መንግሥት በተለያዩ የመዋጮ ጉዳዮች ጨዋታ ጀምሯል እየተባለ ነው፡፡
  • የምን ጨዋታ?
  • እሟ ቀሊጦ!

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

ታዋቂው የኤሌክትሮኒክስ ብራንድ አይቴል የስትራቴጂ ለውጥ አካል የሆነውን አዲስ አርማ እና መለዮ ይፋ አደረገ።

በአለማችን ታዋቂ ከሆኑት የኤሌክትሮኒክስ ብራንዶች መካከል አንዱ የሆነው እና...

የጠቅላላ ጉባኤ ስብሰባ ጥሪ ለሸገር አነስተኛ የፋይናንስ ተቋም አ.ማ ባለአክሲዮኖች በሙሉ

ለሸገር አነስተኛ የፋይናንስ ተቋም አ.ማ ባለአክሲዮኖች በሙሉ የሸገር አነስተኛ የፋይናንስ...

[የክቡር ሚኒስትሩ ጸሐፊ፣ የሌላ ሚኒስትር ጸሐፊ ከሆነችው የቅርብ ወዳጇ ጋር በስልክ እየተጨዋወቱ ነው]

አንቺ ግን ምን ሆነሽ ነው? ጠፋሁ አይደል? ጠፋሁ ብቻ?! ምን ላድርግ ብለሽ...

በሱዳን ላይ ያጠላው የመከፋፈል ዕጣና ቀጣናዊ ተፅዕኖው

የሱዳን ጦርነት ስምንተኛ ወሩን እያገባደደ ይገኛል፡፡ ጄኔራል አብዱልፈታህ አልቡርሃን...

ኦሮሚያ ኢንሹራንስ በግሉ ኢንሹራንስ ዘርፍ ሁለተኛውን የገበያ ድርሻ ለመያዝ ያስቻለውን ውጤት ማስመዝገቡን ገለጸ

ኦሮሚያ ኢንሹራንስ ኩባንያ የባንኮች የጥሬ ገንዘብ እጥረት፣ የመለዋወጫ ዕቃዎች...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[የክቡር ሚኒስትሩ ጸሐፊ፣ የሌላ ሚኒስትር ጸሐፊ ከሆነችው የቅርብ ወዳጇ ጋር በስልክ እየተጨዋወቱ ነው]

አንቺ ግን ምን ሆነሽ ነው? ጠፋሁ አይደል? ጠፋሁ ብቻ?! ምን ላድርግ ብለሽ ነው? እንዴት? አለቃዬ ዕረፍት የለው፣ እኔንም አላፈናፍን ብሎኛል። ታድለሽ። ታድለሽ? ሥራ ገደለኝ ዕረፍት አጣሁ እኮ ነው ያልኩሽ? ገብቶኛል። ምነው እኔንም...

[ክቡር ሚኒስትሩ የሩብ ዓመት የሥራ አፈጻጸማቸውን ለተከበረው ምክር ቤት ካቀረቡ በኋላ ከምክር ቤቱ አባላት የሚነሱ ጥያቄዎችን እየተቀበሉ ማብራሪያ በመስጠት ላይ ናቸው]

ክቡር ሚኒስትር መንግሥት ለሕዝብ ይፋ ያደረገው ነገር ከምን እንደደረሰ ቢያብራሩልን? ምንድነው ይፋ ያደረገው? ጥያቄውን ትንሽ ቢያብራሩት? ከአራት ዓመት በፊት በኦጋዴን አካባቢ ነዳጅ መገኘቱን ለሕዝብ በቴሌቪዥን አብስሮ...

[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ የካቢኔና የማክሮ ኢኮኖሚ ኮሚቴ አባል የሆኑ ከፍተኛ አመራር የሚያቀርቡትን ቅሬታ እያደመጡ ነው] 

ክቡር ሚኒስትር እየሆነ ያለው ነገር በእጅጉ ስላሳሰበኝ ነው በአካል አግኝቼ ላነጋግርዎት የፈለግኩት። ጥሩ አደረግህ፣ ምን አሳሳቢ ነገር ገጥሞህ ነው? ክቡር ሚኒስትር ተወያይተንና ተግባብተን ያስቀመጥናቸው አቅጣጫዎች፣ በተለይም...