Sunday, March 26, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜናኦሕዴድ በውጭ ከሚኖሩ የኦሮሞ ተወላጆች ጋር ለመሥራት የሚያስችል አደረጃጀት ፈጠረ

ኦሕዴድ በውጭ ከሚኖሩ የኦሮሞ ተወላጆች ጋር ለመሥራት የሚያስችል አደረጃጀት ፈጠረ

ቀን:

የኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦሕዴድ) በውጭ ከሚኖሩ የኦሮሞ ተወላጆች ጋር ለመሥራት የሚያስችል አደረጃጀት ፈጠረ፡፡

ኦሕዴድ ሰሞኑን ባካሄደው ስብሰባ አዳዲስ መዋቅሮችንና ሹመቶችን አፅድቋል፡፡ በዚህም መሠረት በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ የድርጅቱን ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ለሦስተኛ ጊዜ ለመቀየር ተገዷል፡፡ በሦስተኛ የኃላፊነት ምደባ የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንትና የኮንስትራክሽንና ከተማ ልማት ቢሮ ኃላፊ የነበሩትን ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) የኦሕዴድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አድርጎ መድቧል፡፡

በ2009 ዓ.ም. ነሐሴ ወር ላይ የቀድሞ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር የነበሩት አቶ በከር ሻሌ ወደ ኦሕዴድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊነት ቢመጡም፣ እስከ ግንቦት 2009 ዓ.ም. ድረስ አገልግለው ለትምህርት ወደ ውጭ አገር ሄደዋል፡፡ ቀጥሎም የቀድሞ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትር አቶ አብዱላዚዝ አህመድ የተተኩ ቢሆንም፣ ከወራት በላይ እንዲቀጥሉ በፓርቲው አልተፈለገም፡፡

‹‹በኦሮሚያ ውስጥ ላለው ፖለቲካዊ ችግር መንስዔው የፓርቲው ደካማነትና የሕዝቡን ፍላጎትና ጥያቄ አለመመለስ ነበር፡፡ በፓርቲው ውስጥ ከ2009 ዓ.ም. ጀምሮ በተደረገ መሻሻል ውጤቶች ቢመዘገቡም፣ አሁንም አሸንፎ ለመውጣት ጠንካራ ኦሕዴድን መገንባት ያስፈልጋል፤›› ሲሉ ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ አንድ የፓርቲው አመራር ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

ለዚህም ሲባል በኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ውስጥ ከፍተኛ ንቅናቄን እየፈጠሩ የሚባልላቸው ዶ/ር ዓብይ አህመድን ወደ ፖለቲካ ሥራ እንዲመጡ መደረጉን ተናግረዋል፡፡ ዶ/ር ዓብይ በአጭር ጊዜ ውስጥ በኢትዮጵያ የፖለቲካ መሰላልን በመራመድ ወደ ጫፍ የደረሱ ሲሆን፣ በአንድ ዓመት ከስድስት ወራት ጊዜ ውስጥ ከፓርላማ አባልነት ወደ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስትርነት ከፍ ብለዋል፡፡

እዚህ ደረጃ ከመድረሳቸው በፊት በውትድርና መስክ በአገር መከላከያ ሠራዊት ውስጥ ሻለቃ ነበሩ፡፡ በኋላም በመረጃ መረብ ደኅንነት ኤጀንሲ ዳይሬክተርነት ለአጭር ጊዜ አገልግለዋል፡፡ በኮምፒዩተር ኢንጂነሪንግ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ያገኙ ሲሆን፣ ከዚህ ጋር ተያያዥነት ባላቸው መስኮች እስከ ዶክትሬት ዲግሪ ትምህርታቸውን ተከታትለዋል፡፡

ኦሕዴድ በተለይ 2008 ዓ.ም. ከገባበት ፖለቲካዊ ቀውስ ለመውጣት ባካሄደው የለውጥ እንቅስቃሴ፣ ከሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ለኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዚዳንትነትና ለክልሉ የኮንስትራክሽንና ከተማ ልማት ቢሮ ኃላፊነት ተሹመዋል፡፡

ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉት የፓርቲው አመራር በኦሮሚያ የፖለቲካ ቀውስ እንዲፈጠር ካስቻሉ መሠረታዊ ምክንያቶች መካከል ዋነኞቹ፣ የአዲስ አበባና የኦሮሚያ የወሰንና የፖለቲካ ግንኙነት፣ እንዲሁም የሥራ አጥነት ችግሮች ተጠቃሽ ናቸው ይላሉ፡፡

ዶ/ር ዓብይ በኦሮሚያ ክልል የኃላፊነት ጊዜያቸው የተጠቀሱትን ችግሮች የመፍታት ቀጥተኛ ኃላፊነት በተሰጠው የኮንስትራክሽንና ከተማ ልማት ቢሮ ከፍተኛ ሚና መጫወታቸውንም ገልጸዋል፡፡

በቆይታቸው የኦሮሚያና የአዲስ አበባ ወሰን ተለይቶ እንዲከለል ተግባራዊ እንቅስቃሴ ማስጀመራቸውን፣ በአዲስ አበባ የኦሮሚያ ልዩ ጥቅም ጉዳይ ሕጋዊ ጥበቃ እንዲያገኝ ከሌሎች የፓርቲው አባላት ጋር በመሆን ጥረት ማድረጋቸውን ተናግረዋል፡፡

‹‹ኦሕዴድ ዶ/ር ዓብይን ከክልሉ መንግሥት ሥራ አስፈጻሚነት ወደ ፓርቲው ጽሕፈት ቤት ኃላፊነት ሲያመጣቸው በመንግሥት ሥራ አፈጻጸም ላይ የተወሰነ ጉድለት ይፈጠራል የሚል ሥጋት ቢጎላም፣ የፓርቲውን የፖለቲካ እንቅስቃሴ ለማጠናከር ሲባል ግን ወደ ፖለቲካ ሥራ እንዲዘዋወሩ ማድረግ አስፈላጊ ነበር፤›› ብለዋል፡፡

ዶ/ር ዓብይን ወደ ኦሕዴድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊነት እንዲመጡ ፓርቲው ሲወስን ተቋማዊ የመዋቅር ማሻሻያም ማድረጉ ታውቋል፡፡ ከዚህም መሀል ግንባር ቀደሙ በውጭ አገሮች የሚኖሩ የኦሮሞ ተወላጆችን ያማከለ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ለማድረግ፣ የፌዴራል ቢሮዎችና የውጭ አገር የአባላት አደረጃጀት ዘርፍ በፓርቲው ውስጥ ተፈጥሯል፡፡ የኦሕዴድ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል በሆኑት አቶ ፍቃዱ ተሰማ እንዲመራ ተወስኗል፡፡ የምሁራን አደረጃጀት ኃላፊ ደግሞ አቶ ስለሺ ጌታሁን፣ የአዲስ አበባ ከተማ አደረጃጀት ኃላፊ ሆነው የተሾሙት ደግሞ አቶ ጌታቸው ባልቻ ናቸው፡፡

የገጠር የፖለቲካ አደረጃጀትን በአቶ ብርሃኑ ፀጋዬ፣ የከተማ የፖለቲካ አደረጃጀትን ደግሞ አቶ ሀብታሙ ኃይለ ሚካኤል እንዲመሩት ተወስኗል፡፡ ይህ የኦሕዴድ አወቃቀር ከሌሎች የኢሕአዴግ መሥራች አባል ፓርቲዎች የተለየ ነው፡፡ ሌሎቹ በአንድ የፖለቲካ አደረጃጀት ዘርፍ የሚመሩ ናቸው፡፡

የኦሕዴድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ የነበሩት አቶ አብዱላዚዝ አህመድ ምክትል ፕሬዚዳንትና የኮንስትራክሽንና ከተማ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሆነው ተሹመዋል፡፡

ኦሕዴድ አምስት አዳዲስ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላትን መርጧል፡፡ በድርጅቱ ታሪክ ሦስት ሴቶች ማለትም ወ/ሮ አዳነች አቤቤ፣ ወ/ሮ ሎሚ በዶ፣ ወ/ሮ አዚዛ አብዲ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ሆነዋል፡፡ አቶ ብርሃኑ ፀጋዬና አቶ ፍቃዱ ተሰማም ተካተዋል፡፡ ወ/ሮ ብርቱካን አያኖ (አምባሳደር) የክልሉ የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ሆነዋል፡፡ 

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ለፋይናንስ ዘርፉ ብቃት ያለው የሰው ኃይል የማፍራት የቤት ሥራን የማቃለል ጅማሮ

የአገሪቱ የፋይናንስ ዘርፍ እያደገ ለመሆኑ ከሚቀርቡ ማስረጃዎች ውስጥ  የግል...

የምድር ባቡርን የሚያነቃቃው የመንግሥት ውሳኔ

በኢትዮጵያ ወደብ አልባነት ላይ የተደመረውን የሎጀስቲክስ ችግር ለመፍታት ግዙፍ...

የፓርላማ አባላት ስለሰላም ስምምነቱ አፈጻጸም ግልጽ መረጃ የለንም አሉ

‹‹ሕወሓትን ለፍረጃ አብቅተውት የነበሩ ጉዳዮች በአብዛኛው መልክ ይዘዋል›› ሬድዋን...