ንብ ባለክንፍ ተንቀሳቃሽ፣ ተባትን እንስት አበባን ኹሉ እየቀሰመች የምትጋግር፣ የማር ዐበዛ፣ ትጉ (ትግህት) ሠራተኛ፡፡ ቀፎዋን የነካባትን እሾኽ በሚመስል ፍላጻዋ ጦር መሣሪያዋ (መርዟ) ትነድፋለች፡፡ ዐርኬና በሚባል ዕልፍኝ የሚውሉ ባጀብ የሚኼዱ አውራ ንጉሥና ንግሥት ውኃ ቀጂ ድንጉል አሏት፡፡ አውራው ከንግሥቲቱ ጋር ተራክቦ ካደረገ በኋላ ንቦቹ ይገድሉታል ይባላል፡፡ ከንግሥትም ንግሥት በተወለደች ጊዜ የናቷን ሠራዊት ከፍላ ከቀፎ ወጥታ ታጅባ ወደ ሌላ ሥፍራ ትኼዳለች፡፡ ሥነ ሥርዐቷ አይቃወስም፡፡
ሙያን ኹሉ የምታውቅ ሴት በምሳሌ ንቡት ትባላለች፡፡
ካፏ ማር ይዘንባል ከከንፈሯ ጠጅ
ወይዘሮ ንቡት የትጋት ወዳጅ፡፡
‹‹ንቦ ንቦ አትናደፊ፣
የነከሌ ነኝ ብለሽ እለፊ፤›› እየተባለም ይዜማል፡፡
- ደስታ ተክለወልድ ‹‹ዐዲስ ያማርኛ መዝገበ ቃላት›› (1962)