የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሌኒየም የሕክምና ኮሌጅ የኢንዶስኮፒ ማሠልጠኛ ማዕከል ሰኔ 28 ቀን 2009 ዓ.ም. ተመርቆ ተከፈተ፡፡
ከጃፓኑ ፉጂ ፊልም ኩባንያና ከጃፓን ኤምባሲ በተገኘ የሁለት ሚሊዮን ብር ድጋፍ በሕክምና ኮሌጁ ውስጥ የተከፈተው ማዕከሉ፣ በአገሪቱ ውስጥ ያለውን ከፍተኛ የኢንዶስኮፒ ሐኪሞች እጥረት ለመፍታትና የኢንዶስኮፒ አገልግሎት ተደራሽነትን ለማሳደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ የኮሌጁ የሕክምና ዘርፍ ኃላፊ ዶ/ር ብርሃኔ ረዳኢ ተናግረዋል፡፡
እንደ ኃላፊው አገላለጽ በተለያዩ የጨጓራ፣ የጉበትና የሆድ ዕቃ በሽታዎች ችግር ያለባቸውና እንዲሁም የጨጓራ፣ የጉበትና የሆድ ዕቃ ካንሰር ሕሙማንን ለማከም የማዕከሉ መከፈት ከማስፈለጉም በላይ የኢትዮጵያን ኢንዶስኮፒ ሐኪሞች ቁጥር እንዲጨምር ያደርጋል፡፡ የአገልግሎት ተደራሽነትንም በማስፋት ብዙ ፈላጊዎችን ተጠቃሚ ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ማዕከሉ በዓመት ለ20 የኢንዶስኮፒ ሐኪሞች አጫጭር ሥልጠናዎች መስጠት የሚችል ሲሆን፣ በተጨማሪም በዓመት አራት ጊዜም የኢንዶስኮፒ አገልግሎት በሌሉባቸው ቦታዎች የሕክምና አገልግሎት ይሰጣል፡፡
እ.ኤ.አ. በ1943 የተመሠረተው የሕክምና መሣሪያዎች አምራቹ ፉጂ ፊልም በተለያዩ አገሮች የኢንዶስኮፒ ማሠልጠኛ ማዕከል እንዳሉት ያመለከቱት፣ የፉጂ ፊልም የምሥራቅና መካከለኛው አፍሪካ ሥራ አስኪያጅ አቶ አንተነህ እውነቱ፣ ኩባንያው ለተለያዩ ተቋማት የሕክምና ባለሙያ ማሠልጠንና የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉን ይቀጥላል ብለዋል፡፡
የሕክምና ኮሌጁ የጨጓራ፣ የጉበት፣ የአንጀት፣ የሆድ ዕቃዎችና ሌሎች በሽታዎች ሕክምና የሚሰጥ ባለ ሰባት ወለል ሕንፃ በመንግሥት በጀት እያስገነባ ይገኛል፡፡ ከሁለት ዓመት በኋላ የሚጠናቀቀው ይህ ሕንፃ ዘመናዊ አገልግሎት የሚሰጥበት ማዕከል እንደሚሆን ተጠቁሟል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ የማዕከሉን መከፈት አስመልክቶ በኩባንያውና የሕክምና ኮሌጁ መካከል የመግባቢያ ሰነድ ስምምነት በዚሁ ዕለት ተፈርሟል፡፡ በስምምነቱ መሠረት ኩባንያው፣ ማዕከሉና የሚገለገልባቸውን የሕክምና ማሽኖች የመጠገንና ሥልጠና የመስጠት ሥራ እንደሚያከናውን ለማወቅ ተችሏል፡፡