ከሚመለከተው አካል ሕጋዊ ፈቃድ ሳያገኙ ወይም ሳያስፈቅዱ በመዋሀድ የንግድ እንቅስቃሴ እያደረጉ ነው የተባሉት አምቦ የማዕድን ውኃ አክሲዮን ማኅበርና ኢስት አፍሪካ ቦትሊንግ ክስ ተመሠረተባቸው፡፡
ክሱ የተመሠረተው በንግድ ውድድርና ሸማቾች ጥበቃ ባለሥልጣን አስተዳደራዊ ፍርድ ቤት መሆኑ ታውቋል፡፡
ድርጅቶቹ ከባለሥልጣኑ ፈቃድ ሳይኖራቸው የንግድ ውድድር ውስጥ በመግባታቸው፣ በሌላ ተወዳዳሪ ላይ ጉዳት እንደሚያደርሱ ተጠቁሟል፡፡
ሁለቱ ድርጅቶች በአገር ውስጥ ስምምነት ፈጽመው ውህደት ባያደርጉም፣ መዋሀዳቸውን የሚያመላክት ተግባር እየፈጸሙ መሆናቸውን ባለሥልጣኑ በክሱ መጠቆሙ ተገልጿል፡፡
ሁለቱ ድርጅቶች የሚያመርቷቸውን የለስላሳ መጠጦች አምቦ ውኃን በተናጠል ሲያከፋፍሉ የነበሩ አከፋፋዮች ሁለቱንም በጥምር እንዲያከፋፍሉ መገደዳቸውን፣ ባለሥልጣኑ በክሱ መግለጹ ታውቋል፡፡ አንዱን ምርት ብቻ እንደሚያከፋፍሉ የሚናገሩ አከፋፋዮች፣ የውል ጊዜያቸው ሳይጠናቀቅ እንዲቋረጥ እንደተደረገባቸውም አክሏል፡፡ እስከ መቶ የሚደርሱ አከፋፋዮችም ከሥራ ውጪ እንዲሆኑ መደረጋቸውም ተጠቁሟል፡፡
ባለሥልጣኑ በመሠረተው ክስ ድርጅቶቹ የሚሸነፉ ከሆነ፣ በአዋጁ መሠረት ከዓመታዊ ገቢያቸው አሥር በመቶ እንደሚወሰድባቸው ታውቋል፡፡ ዓመታዊ ገቢያቸውን ማወቅ ካልተቻለም ከ300,000 ብር እስከ 600,000 ብር ቅጣትና ከሦስት እስከ አምስት ዓመታት ሊታሰሩ እንደሚችሉ ታውቋል፡፡
መንግሥት በአምቦ ማዕድን ውኃ አክሲዮን ማኅበር ውስጥ ያለውን 33 በመቶ አክሲዮን ድርሻ፣ በ19,782,807 ዶላር አምቦ ኢንተርናሽናል ሆልዲንግ ሊሚትድ በሚል ስያሜ ለሚታወቀው የሞሪሽየስ ኩባንያ መሸጡ ይታወሳል፡፡