ከሐምሌ መገባደጃ ጀምሮ ለአሥር ቀናት ተካሂዶ በነበረው 16ኛ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ተካፋይ ለነበረው የኢትዮጵያ ብሔራዊ አትሌቲክስ ልዑክ ማክሰኞ መስከረም 2 ቀን 2010 ዓ.ም. በሐዋሳ የገንዘብ ሽልማት ተበረከተለት፡፡
ኢትዮጵያ በአልማዝ አያና 10,000 ሜትር፣ በሙክታር እድሪስ በ5,000 ሜትር የወርቅ፤ እንዲሁም ታምራት ቶላ በወንዶች ማራቶን፣ ጥሩነሽ ዲባባ 10,000 ሜትርና አልማዝ አያና 5,000 ሜትር ባስመዘገቡት የብር፣ በድምሩ በአምስት ሜዳሊያ ከዓለም ሰባተኛ ሆና ሻምፒዮናውን ማጠናቀቋ ይታወሳል፡፡ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በለንደኑ ዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ለተሳተፈው ቡድንና አትሌቶቹ ባስመዘገቡት ውጤት ከ40 ሺሕ እስከ አምስት ሺሕ ብር በአጠቃላይ ከ800 ሺሕ ብር በላይ መሸለሙ ይታወሳል፡፡
ማክሰኞ መስከረም 2 ቀን 2010 ዓ.ም. ምሽት የወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር በሐዋሳ ኃይሌ ሪዞርት ባዘጋጀው ሥነ ሥርዓት በለንደኑ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ውጤት ላስመዘገቡ አትሌቶችና ልዑካን ቡድን ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በተገኙበት የገንዘብ ሽልማት አበርክቷል፡፡
በሌላ በኩል በአዲስ አበባ ሽኝት የተደረገለት የኢትዮጵያ ብሔራዊ አትሌቲክስ ቡድን የገንዘብ አሰጣጡ ሥነ ሥርዓት በሐዋሳ የተደረገበትን ምክንያት አስመልክቶ፣ የወጣቶችና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ተስፋዬ ይገዙ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ሽልማቱን የሚሰጡት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ለደኢሕዴን ጉባኤ በሐዋሳ በመሆናቸው እንደሆነና ከጉባኤው በኋላ ደግሞ ለተባበሩት መንግሥታት ጠቅላላ ጉባኤ ከአገር ውጪ ስለሚሆኑ የሽልማቱ ጊዜ እንዳይራዘም በማሰብ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡