ሐቻምና በምሥራቅ አዲስ አበባ ኢምፔሪያል አካባቢ ተተክሎ የነበረው የቦብ ማርሌ ሐውልት፣ በመስቀለኛ መንገድ የማስፋፋት ሥራ ሳቢያ ሰኔ 16 ቀን 2009 ዓ.ም. እንዲነሳ ተደርጓል፡፡ አራት ሜትር ቁመት ያለው ሐውልቱ ቦብ ‹‹አፍሪካ ዩናይት›› ብሎ ሲዘፍን የሚያሳይ ሲሆን፣ የተሠራውም በቀራፂ ተስፋ ብዙነህ ነው፡፡ ሐውልቱ በቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን እና በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን አዳራሽ መካከል፣ በፊንፊኔ ወንዝ ዳርቻ በተሠራው የሕዝብ መናፈሻ መካከል ይቆማል ተብሏል፡፡ ሚያዝያ 11 ቀን 2007 ዓ.ም. በይፋ የተመረቀው የቦብ ማርሌ ሐውልት ግንባታ ሒደት አምስት ዓመት መውሰዱ፣ አደባባዩን ለመጠገን ብቻ ከ200 ሺሕ ብር መውጣቱን ድምፃዊ ዘለቀ ገሠሠን ጠቅሶ ሪፖርተር መዘገቡ ይታወሳል፡፡ ፎቶዎቹ የድሮውንና የአሁኑን የአደባባዩን እና የሐውልቱን ገጽታ ያሳያሉ፡፡
ፎቶ በታምራት ጌታቸው
አውጣኝ
…ፍቅር ከሌለው ሰላምታ
ውበት ከሌለው ፈገግታ
…ጥልቀት ከሌው እውቀት
መሠረት ከሌለው እምነት
እውነት ከሌለው ምርምር
ደግነት ከሌለው ፍቅር
አውጣኝ
ህሊናዬ አውጣኝ፡፡
እኔ በቁሜ እንዳላይ የበድን ሬሳን ዕጣ
ህሊናዬ ጠንከር በርታ ባስቀይምህ
ቢያስቀይሙህ
በቀላሉ አትረታ
ጥለኸኝ እንዳትበረግግ
ፈርጥጠህ እንዳትጠፋ፡፡
- ፈቃደ አዘዘ (1994)
******
‹‹ማን ነው?…››
አንዱን ሊቅ ‹‹ማን ነው ብልህ?›› ቢሉት፡-
ከያንዳንዱ ሰው ሊማር የሚችል፤
‹‹ማን ነው ጠንካራ ሰው?›› ቢሉት፡-
ስሜቱን የሚቆጣጠር፤
‹‹ማን ነው ሀብታም?›› ቢሉት፡-
በቃኝን የሚያውቅ፤
‹‹ማን ነው የተከበረ ሰው?›› ቢሉት
ሰውን የሚያከብር፤ ብሎ መለሰ ይባላል፡፡
- የወግ ገበታ
አሽከርካሪ አልባ መኪናዎችን የምትፈትነው ካንጋሩ
የቮልቮ ራሱን በራሱ የሚያሽከረክር የመኪና ቴክኖሎጂ፣ መንገድ ላይ የሚያጋጥሙ ካንጋሩዎችን መለየት ባለመቻሉ ችግር ውስጥ ገብቷል፡፡
ቢቢሲ እንደዘገበው፣ የስዊድን መኪና አምራቹ 2017 ኤስ 90 እና ኤክስ ሲ 90 ሞዴሎች እንስሳትን መለየት የሚያስችል ቴክኖሎጂ አላቸው፡፡ ቴክኖሎጂውም ድብ፣ ኤልክና ካሪቡን መለየት ይችላል፡፡ ሆኖም ካንጋሩን ለመለየት መቸገሩ ተገልጿል፡፡ የአውስትራሊያ ብሔራዊ የሞተረኞች አሶሲየሽንም 80 በመቶ የሚሆነው የመኪና ግጭት ከካንጋሩ ጋር ነው ብሏል፡፡ የቮልቮ የደኅንነት ኢንጅነሮች ካንጋሩዎች በየመንገዱ ላይ ያላቸውን ባህሪ መቅረጽ የጀመሩት በ2015 ሲሆን፣ የሚገኘው መረጃም የመኪኖች ራዳር ካንጋሩዎችን እንዲለዩ ለማስቻል፣ ከዚህ ጋር የተያያዙ አደጋዎችንም ለማጥፋት መሆኑን ዘገባው ያሳያል፡፡
******
በረሃውን ገነት የሚያደርገው ‹‹የነፍስ ምግብ››
አንድ ሊቅ ሰው ‹‹እኔ ጠንካራ ሠራተኛ ነው አዕምሮዬ ሲደነዝዝ ቴኒስ በመጫወት እደሰታለሁ ሐዘኔን ልረሳው እንድችል ያደረገኝ ግን የተዋቡ ሙዚቆችን መስማት ነው፤›› አለ በእርግጥም በሰውና በዓለሙ መካከከል ፍፁም ሰላም ሰጭ ሁኖ የሚያስታርቀው የዕርቅ መስዋዕት ጣዕም ያለው ዘፈንና ሙዚቃ ቃና ነው፡፡
ውብ ድምፅ ያላቸው ወፎች በረሃ አገራቸው ነው፡፡ ቃና ባለው ዜማ ከተዋበ ድምፃቸው ጋራ ሲዘምሩ ግን በረሃውን ገነት ያደርጉታል፡፡ እንዳዘነም ልብ የነበረውን ምድረ በዳ የገነት ያህል ሊለውጡት ችሎታ ሲኖራቸው አዳኞች አይተዋል፡፡ እንዲሁም የላባው ውበት ሊያኮራው የሚችል የቁራ አሞራ ደግሞ በዜማውና በድምፁ ክፋት እንደገነት ያማረችውን አገር በረሃ ያደርጋታል፡፡
ሰውም በሚኖርበት ርስቱ ላይ እንዲሁ ነው፡፡ የተዋጣ ቅያስ ባላቸው መንገዶች መጓዝ አይታው ሁሉ ደስ ያሰኘዋል፡፡
አበቦችም በተተከሉበት ቦታ መጠለል አዲስ ስሜትና ዕረፍት ይሰጠዋል፡፡ ቅርፁ እጅግ አምሮ በታነፀ ቤት መኖርም ይመቸዋል፡፡ በሰገነት መቀመጥም እጅግ ክብር ያለው ሆኖ ያገኘዋል፡፡ ነገር ግን የነፍሰን አሥራው በማንቀሳቀስ ሰውን ደስ ሊያሰኘው የሚችል ጣዕም ያለው ሙዚቃና ባህል ያለው ዘፈን ባይኖር የማንኛውም የሚታይ ውበት ሁሉ ግምቱ አባይ ይሆናል፡፡
ተመስገን ገብሬ ‹‹ሰንደቅ ዓላማችን›› (ኀዳር 1935)
*******