የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርና ፍርድ ቤቶችን ሲያነጋግር በቆየው የዕግድ ጉዳይ ላይ፣ ከንቲባ ድሪባ ኩማ በተገኙበት የመጀመሪያ ውይይት ተካሄደ፡፡
ረቡዕ ሰኔ 14 ቀን 2009 ዓ.ም. በተካሄደው ውይይት፣ የከተማው የመሬት ሥሪት ባለሥልጣናትና የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ዳኞች ተገኝተዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ምክትል ቢሮ በዕግድ ምክንያት እየተፈጠረ ያለውን ችግር ለዳኞች አስረድቷል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ መኮንን አምባዬ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በአስተዳደሩ ዕግድ እየበዛ ልማቱን እያደናቀፈ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
‹‹ጉዳዮቹ በከተማ ቦታ ማስለቀቅና የካሳ ጉዳዮች ይግባኝ ሰሚ ጉባዔ ሳይታዩ በቀጥታ ወደ ፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት እየሄዱ ነው፤›› ሲሉ አቶ መኮንን ገልጸዋል፡፡ ‹‹መሄዳቸው ችግር የለውም፣ የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤቶች ለምን አዩ ሳይሆን፣ አጭር ቀጠሮ እየተሰጠ በፍጥነት ሊቋጩ ይገባል ነው የምንለው፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡
‹‹አስተዳደሩ ዕርምጃ ሲወስድ ሕገወጥ ብሎ ሲሆን፣ ዕርምጃ የተወሰደባቸው ደግሞ ሕጋዊ ነን ይላሉ፡፡ ስለዚህ ፍርድ ቤቶች ዕግድ ሲሰጡ ጠያቂዎቹ የይዞታው ባለቤት ስለመሆናቸው ማረጋገጥ ይኖርባቸዋል፤›› ሲሉ አቶ መኮንን አብራርተዋል፡፡
‹‹በሌላ በኩል ዕግድ የሚወጣው በግንባታ ወቅት ነው፡፡ አቤቱታ አቅራቢዎች መንግሥት ላይ ሁከት ይወገድ ይላሉ፡፡ በዚህ መሠረት እኛ ዕርምጃ መውሰድ ስናቆም እነሱ ግን ግንባታቸውን ይቀጥላሉ፡፡ የፍርድ ቤቱ ውሳኔ ለሁለቱም ወገኖች ላይ ቢሠራ መልካም ነው፤›› ሲሉ አቶ መኮንን ገልጸዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት በአዲስ አበባ ከ100 በላይ እንጥልጥል የመሬት ጉዳዮች የፍርድ ቤት እየታዩ ይገኛሉ፡፡ እነዚህም በመልሶ ማልማት፣ በወሰን ማስከበር፣ በማስፋፊያ ቦታዎች የመሬት ወረራ እንዲስፋፋና የልማት እክሎች ሆነዋል ተብሏል፡፡
በስብሰባው ላይ የተገኙ ዳኞች ዜጎች የመዳኘት መብታቸው ሊነፈግ አይገባም በማለት የግል አቋም ማንፀባረቃቸውን፣ ነገር ግን ያሉትን የፍርድ ቤት ጉዳዮች በየባህሪያቸው በመመርመር ለሚቀጥለው ወር መጀመሪያ ላይ በድጋሚ ለመወያየት መስማማታቸው ተገልጿል፡፡