በዘመኑ ተናኘና ሳሙኤል ጌታቸው
እ.ኤ.አ. ከሐምሌ 2014 ዓ.ም. ጀምሮ በኢትዮጵያና በአፍሪካ ኅብረት የጀርመን አምባሳደር ሆነው ያገለገሉት ጆአሺም ሽቺሚት (ዶ/ር) ማረፋቸው ተገለጸ፡፡
በኢትዮጵያ የጀርመን ኤምባሲ ይፋ ባደረገው መረጃ መሠረት፣ ዶ/ር ጆአሺም ሰኞ ሰኔ 5 ቀን 2009 ዓ.ም. እንዳረፉ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ዶ/ር ጆአሺም በኢትዮጵያ የጀርመን አምባሳደር ከመሆናቸው በፊት፣ በቦስኒያና ሔርዚጎቪኒያ እንዲሁም ሰርቢያ የጀርመን አምባደር ሆነው እንዳገለገሉ ለማወቅ ተችሏል፡፡ የጀርመን አምባሳደር ሆነው ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣታቸው በፊት፣ በአምባሳደር ማዕረግ የጀርመን የውጭ አገልግሎት አካዳሚ ዋና ዳይሬክተር ሆነው ሲያገለግሉ እንደነበር ከሕይወት ማህደራቸው የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
ዶ/ር ጆአሺም በኢትዮጵያ ውስጥ በነበራቸው ቆይታ የኢትዮጵያንና የጀርመንን የሁለትዮሽ ግንኙነት ወደ ተሻለ ደረጃ ማሳደግ እንደቻሉ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡ ከአንድ ወር በፊትም የአዲስ አበባ እህት ከተማ የሆነችው የጀርመኗ ላይፒዚሽ ከተማ ከንቲባ በአዲስ አበባ ተገኝተው በነበረበት ወቅት፣ ዶ/ር ጆአሺምም በመገኘት ስለሁለቱ ከተሞች የሁለትዮሽ ግንኙነት ንግግር ማድረጋቸው ይታወሳል፡፡ በወቅቱም ጀርመን በመሠረተ ልማት በተለይም በመንገድና በእንስሳት ሕክምና ለኢትዮጵያ ድጋፍ እያደረገች መሆኑን ጠቁመው፣ የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ንብረት የሆነችው አንድ ባቡር በላይፒዚሽ ከተማ ስም መሰየሟ የሁለቱን አገሮች ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ከፍ እንደሚያደርገው ገልጸው ነበር፡፡ ከዚህ ባለፈም ጀርመንና ኢትዮጵያ ከዚህ በፊት በባህል ትስስር ያላቸው በመሆኑ ከያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት የተመረጡ ባለሙያዎች ወደ ጀርመን ሄደው የትምህርት ዕድል ማግኘት ስለሚችሉበት ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር እየተነጋገሩ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡
ለብዙ ዓመታት የቆየውን የጀርመንና የኢትዮጵያ የሁለትዮሽ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ እንዳሸጋገሩና ብዙ ኢትዮጵያዊያን ወደ ጀርመን አገር ሄደው የትምህርት ዕድል እንዲያገኙ የተጫወቱት ሚና ከፍተኛ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በኢትዮጵያ የጀርመን ኤምባሲ መረጃ መሠረት፣ ዶ/ር ጆአሺም የ62 ዓመት ዕድሜ ባለፀጋ ሲሆኑ የአብራካቸው ክፋይ የሆኑ ልጆች እንደሌላቸውም ለማወቅ ተችሏል፡፡
ከወራት በፊት ጀምሮ ለሞት በሚዳርግ ራስን በሚያስትና በልብ ሕመም ተይዘው ሲሰቃዩ እንደነበር ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
ዶ/ር ጆአሺም የአውሮፓ ኅብረት ከአፍሪካ ኅብረት ጋር ያለውን ግንኙነት የበለጠ እንዲያጠናክርና አፍሪካ ካለባት የመሠረት ልማት ችግሮች እንድትላቀቅ ሰፊ ሥራ ሲያከናውኑ መቆየታቸውን፣ በአሜሪካ ኤምባሲ የሥራ ኃላፊ የሆኑ ሚስተር ፒተር ቬሮማን ተናግረዋል፡፡
እ.ኤ.ኤ. የካቲት 27 ቀን 1955 በጀርመኗ ውፐርታል ከተማ የተወለዱት ዶ/ር ጆአሺም፣ የዶክትሬት ዲግሪያቸውን በኢኮኖሚክስ፣ በታሪክና በዓለም አቀፍ ግንኙነት ከአሜሪካ እንዳገኙ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ዶ/ር ጆአሺም ከማረፋቸው በፊት ሕመማቸው ሲጠና ወደ አገራቸው እንደሄዱና ሕይወታቸውም በአገራቸው ማለፉን የጀርመን ኤምባሲ አስታውቋል፡፡
ከማክሰኞ ሰኔ 6 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ ለተከታታይ ሦስት ቀናት በኢትዮጵያ የሚገኙ የዲፕሎማቲክ ማኅበረሰብ አባላት በዶ/ር ጆአሺም ሞት የተሰማቸውን ሐዘን በኤምባሲው እየተገኙ መግለጽ እንደሚችሉ የጀርመን ኤምባሲ አስታውቋል፡፡