Sunday, June 4, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ስፖርትግዴለሽነት የታየበት የታዳጊዎች አትሌቲክስ ሻምፒዮና

ግዴለሽነት የታየበት የታዳጊዎች አትሌቲክስ ሻምፒዮና

ቀን:

የኢትዮጵያ አትሌቲከስ ፌዴሬሽን ከሚያከናውናቸው ዓመታዊ ውድድሮች መካከል የታዳጊዎች ሻምፒዮና ዋነኛው ነው፡፡ የታዳጊዎች፣ የወጣቶች እንዲሁም የአዋቂዎች ውድድር በመርሐ ግብሩ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ በተለይ ደግሞ የታዳጊዎች ሻምፒዮና ትልቅ  ትኩረትን የሚሻ፣ የተተኪዎች መገኛ እንደመሆኑና በዓለም አቀፍ ውድድሮች ላይ የሚታየውን የውጤት መዋዠቅ ተከትሎ ከሚሰነዘሩ አስተያየቶች በስተቀር ሥራው ላይ አስፈላጊው ጥንቃቄ ሲደረግ አይስተዋልም፡፡

የዓለም አቀፍ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ማኅበር (አይኤኤኤፍ) ከ18 ዓመት በታች በኬንያ በሚያደርገው አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ የሚሳተፉ አትሌቶችን ለመመልመል ከሰኔ 7 እስከ 11 ቀን 2009 ዓ.ም. ድረስ በአሰላ አረንጓዴው ስታዲየም የታዳጊዎች ውድድር አከናውኗል፡፡ ለአራተኛ ጊዜ በተካሄደው በዚህ ውድድር ላይ ክለቦች፣ ክልሎችንና የከተማ አስተዳደሮችን ተሳታፊ ነበሩ፡፡

ፌዴሬሽኑ በቅድመ ዝግጅት ወቅት ክለቦችና የከተማ አስተዳደሮችን እንዲሁም ለሌሎች ተሳታፊዎች ለሻምፒዮናው የሚያስፈልጉትን መስፈርቶች አሟልተው እንዲመጡ ማሳወቅ የዘወትር ሥራው ቢሆንም፣ ተሳታፊዎች ግን ችላ ያሉት ይመስላል፡፡

ችግሩን አስመልክቶ ፌዴሬሽኑ፣ የተወዳዳሪዎች ዕድሜ ተመጣጣኝ  አለመሆንና ሁሉም ተሳታፊዎች ለውጤት ብቻ ትኩረት ሰጥተው መምጣታቸው ሁኔታውን አዳጋችና አስቸጋሪ ስለማድረጉ ጭምር አስታውቋል፡፡

ሻምፒዮናው ምንም እንኳ ቀድሞ ከነበረው የተወሰነ ማሻሻያ ቢደረግበትም፣  በዘንድሮ ሻምፒዮና ላይ 30 አትሌቶች ታግደው ቅጣት እንዲጣልባቸው መደረጉም ታውቋል፡፡ ታዳጊዎች መሳተፍ ሲገባቸው በተለያዩ ውድድሮች ላይ ሲሳተፉ የነበሩ አትሌቶችን በታዳጊዎች ውድድር ላይ እየተሳተፉ መምጣታቸው እየተለመደ መምጣቱ ሲነገር ቆይቷል፡፡

በተገቢው መንገድ አትሌቶችን ማወዳደር ባለመቻሉና በዘርፉ ላይ ውጤታማ የሆኑ ተወዳዳሪዎችን ማግኘት ስላልተቻለ አይኤኤኤፍ ሳይቀር ችግሩ መፍትሔ ከሌለው ከዚህ ዓመት በኋላ ሻምፒዮናውን ለመሰረዝ እንደሚገደድ ማስታወቁም ይታወሳል፡፡ በኬኒያ በሚካሄደው አሥረኛው የዓለም ከ18 ዓመት በታች ውድድር የመጨረሻ እንደሚሆን ጭምር አስታውቋል፡፡ ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ ችግሮችን ለመቅረፍ አዲስ አሠራር በመቅረጽ ወደ ሥራው ለመግባት ማቀዱን የገለጸ ሲሆን፣ ከዕድሜ ማጭበርበሩ በተጨማሪ የሀሰት ስም በማውጣት አትሌቶችን ለውድድር ማቅረብ ‹‹ስግብግብነት ነው›› በማለት የፌዴሬሽኑ ቴክኒካል ዳይሬክተር አቶ ዱቤ ጂሎ የችግሩን መባባስ አብራርተዋል፡፡

አይኤኤኤፍ የዓለም የታዳጊዎች ሻምፒዮናውን እንደሚያቋርጥ ቢገልጽም፣ ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ በአገር ውስጥ በታዳጊዎች የሚያደርገውን ውድድር የበለጠ በማሻሻል አጠናክሮ የሚቀጥልበት ስለመሆኑ ግን አቶ ዱቤ አልተሸሸጉም፡፡

ለዚህም ይረዳ ዘንድ የዕድሜ ማጭበርበሩን ለመቀነስ በመረጃ መረብ በመታገዝ በየዓመቱ ክለቦች ሁሉንም አትሌቶቻቸውን መመዘረገብና ቁጥጥር ማድረግ የሁሉም አካል የቤት ሥራ ሊሆን እንደሚገባም ባለሙያው ተናግረዋል፡፡

በሻምፒዮናው ከ720 በላይ አትሌቶችና 23 ክለቦች እንዲሁም ዘጠኙ ክልሎችና ሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች ተሳታፊ ነበሩ፡፡ ከዚህ በተጓዳኝ ግን በበጀት ዕጥረት ምክንያት በሻምፒዮናው ላይ መካፈል ያልቻሉም አልጠፉም፡፡

በኢትዮጵያ ውስጥ ከሚገኙት አራቱ የአትሌቲክስ ማዕከላት አንዱ የሆነ የበቆጂ አትሌቶች ማሰልጠኛ ካልተሳተፉት ይጠቀሳል፡፡ ማሠልጠኛ ተቋሙ ከ17 ዓመት በታች  ከኦሮሚያ አካባቢ የተውጣጡ ታዳጊዎች በተለያዩ ርቀቶች ላይ ሥልጠና የሚሰጥ  ሲሆን፣ በሻምፒዮናው ላይ ለመሳተፍ በጀትና የዕድሜ ተመጣጣኝ አለመሆን ከውድድሩ እንዲቀር እንዳደረገው ተነግሯል፡፡

በዚህም ምክንያት የማሰልጠኛ ማዕከሉ የአትሌቶዎቹን አቅም ለማወቅ የክልል ውድድሮች ላይ ለመሳተፍ እንደተገደደም ተነግሯል፡፡ የበጀት ዕጥረትን በተመለከተ ክልሎች አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረግ እንዳለባቸው የተገለጸ ሲሆን፣ በውድድሩ ላይ መሳተፍ እንዲችሉ ፌዴሬሽኑ አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ እንደሚንቀሳቀስም አቶ ዱቤ አስረድተዋል፡፡

የተተኪ አትሌቶች መፍለቂያ የሆኑ አካባቢዎችን ለይቶ ማወቁን ያሳወቀው ፌዴሬሽኑ፣ ዓመታዊ የታዳጊ ውድድሮችን ወደ ፕሮጀክትና ትምህርት ቤቶች እንደሚያስፋፋ ዕቅድ መያዙን ገልጿል፡፡ የሱር ኮንስትራክሽን አትሌቲክስ ቡድን ሥራ አስኪያጅ አቶ ጌታቸው ተካ ለሪፖርተር እንዳስረዱት ከሆነ፣ ‹‹የታዳጊ ወጣቶች ሻምፒዮና ራሳቸው ታዳጊዎች ዕድሉን መጠቀም ይገባቸዋል፣ በማለት ያለውን ክፍተት በማመላከት ጠቁመዋል፡፡

ክለቦችም በተገቢው መንገድ ታዳጊዎችን በማሳተፍ ውጤታማ አትሌቶችን ለማፍራት አስፈላጊውን ጥረት ማድረግ እንደሚገባቸው አቶ ጌታቸው አስተያየታቸውን ሰንዝረዋል፡፡

ለተከታታይ አምስት ቀናት የተከናወነው ሻምፒዮናው የሜዳ ተግባራትን ጨምሮ የአጭርና የረጅም ርቀቶች ላይ ከፍተኛ ፉክክሮች ተደርገዋል፡፡ የጥሩነሽ ዲባባ እና የወጣቶች አካዴሚ ተስፋ ሰጪ ፉክክር ማድረግ የቻሉ ሲሆን ከክልል አማራና ሲዳማ እንዲሁም ኦሮሚያ ተሽለው የተገኙ ነበሩ፡፡

በዚሁ የታዳጊዎች አትሌቲክስ ሻምፒዮና አጠቃላይ አሸናፊዎች በሴቶች ሲዳማ ቡና በ90 ነጥብ፣ አማራ ክልል 87.5 ነጥብ፣ ኦሮሚያ ክልል 72 ነጥብ በማግኘት ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ያለውን ደረጃ ይዘው አጠናቀዋል፡፡ በወንዶች አማራ በ100.5 ነጥብ፣ ሲዳማ ቡና 87 ነጥብ እና ኦሮሚያ 86 ነጥብ የወርቅ የብርና የነሐስ ሜዳሊያ ተሸላሚዎች ሆነዋል፡፡

በአጠቃላይ ውጤት አማራ በ188 ነጥብ፣ ሲዳማ ቡና 177 ነጥብ እና ኦሮሚያ 158 ነጥብ የዋንጫ ተሸላሚዎች ሆነው ውድድሩን አጠናቀዋል፡፡ በሻምፒዮናው የተሻለ ውጤት ያላቸው አትሌቶች ለብሔራዊ ቡድን ዝግጅት ሆቴል እንደሚገቡም ፌዴሬሽኑ አስታውቋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

አወዛጋቢው የሕገ መንግሥት ማሻሻያ ጉዳይ

በኢትዮጵያ የሕገ መንግሥት ማሻሻል ጉዳይ ከፍተኛ የፖለቲካ ውዝግብ የሚቀሰቀስበት...

 መፍትሔ  ያላዘለው  የጎዳና  መደብሮችን  ማፍረስ

በአበበ ፍቅር ያለፉት ስድስት ዓመታት በርካቶች በግጭቶችና በመፈናቀሎች በከፍተኛ ሁኔታ...

የተናደው ከቀደምቱ አንዱ የነበረው የአዲስ አበባ ታሪካዊ ሕንፃ

ዳግማዊ አፄ ምኒልክ በ19ኛው ክፍለ ዘመን መገባደጃ መናገሻ ከተማቸውን...

የአከርካሪ አጥንት ሕክምናን ከፍ ያደረገው ‘ካይሮፕራክቲክ’

በአፍሪካ ከጀርባ ሕመም ጋር በተያያዘ በርካታ ሰዎች ለከፍተኛ የአካል...