የውኃ፣ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስቴር በ257 ሚሊዮን ዶላር 120 ሜጋ ዋት የንፋስ ኃይል ማመንጫ በሶማሌ ክልል ሊገነባ መሆኑን አስታወቀ፡፡ ‹‹አይሻ ሁለት የንፋስ ኃይል ማመንጫ›› የሚባል መጠሪያ ያለው ፕሮጀክት ግንባታ የሚጀምረው፣ በሐምሌ ወር 2009 ዓ.ም. መሆኑም ታውቋል፡፡
የውኃ፣ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነትና ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ብዙነህ ቶልቻ ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ በሶማሌ ክልል የሚገነባው የንፋስ ኃይል ማመንጫ አራተኛው ፕሮጀክት ነው፡፡
የፕሮጀክቱ ግንባታ በ18 ወራት የሚጠናቀቅ ሲሆን፣ ግንባታውን የሚያከናውነው ገንዘቡን አፈላልጎ ያገኘው ዶንግፋንግ የሚባለው የቻይና ኩባንያ መሆኑን አቶ ብዙነህ ገልጸዋል፡፡
የፕሮጀክቱ 85 በመቶ ወጪ ከቻይና ኤግዚም ባንክ በዝቅተኛ ወለድ በተገኘ ብድርና 15 በመቶው ደግሞ በኢትዮጵያ መንግሥት የሚሸፈን መሆኑን ዳይሬክተሩ አክለዋል፡፡
መቐለ ከተገነባው አሻጎዳ የንፋስ ኃይል ማመንጫ፣ በአዳማ አንድና ሁለት ከተገነቡት የንፋስ ኃይል ማመንጫዎች በድምሩ 324 ሜጋ ዋት ኃይል እየመነጨ መሆኑን አቶ ብዙነህ አስታውሰው፣ በሶማሌ ክልል የሚገነባው የንፋስ ኃይል ማመንጫ ሲጠናቀቅ በድምሩ ከ440 ሜጋ ዋት በላይ የንፋስ ኃይል ማመንጨት እንደሚቻል አስረድተዋል፡፡