ከሐምሌ 2008 ዓ.ም. ጀምሮ እስካሁን የ369 አትሌቶች የደምና የሽንት ናሙና እንዲሰጡ መደረጉንና ከነዚህ ውስጥ 97 አትሌቶች ከአበረታች ቅምሞች ነፃ መሆናቸው መረጋገጡን የኢትዮጵያ ፀረ አበረታች ቅመሞች ጽሕፈት ቤት አስታወቀ፡፡
የጽሕፈት ቤት ዳይሬክተሩ አቶ መኰንን ይደርሳል ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ከዘጠኝ ወራት በፊት ጀምሮ ውድድር ዓመቱ አሁን እስከሚገኝበት ጊዜ ድረስ፣ የደምና የሽንት ናሙና የሰጡት አትሌቶች አሥር የብስክሌት፣ አምስት የፓራሊምፒክ፣ አምስት የቦክስና 339 ከሩጫ የውድድር ዓይነቶች በድምሩ 369 አትሌቶች ሲሆኑ፣ ከነዚህ ውስጥ ደግሞ የዓለም አቀፍ የፀረ አበረታች ቅመሞች ኤጀንሲ (ዋዳ) የ97 ስፖርተኞች ውጤት ከአበረታች ቅመሞች ነፃ መሆናቸውን አረጋግጦ አስታውቋል፡፡
ኃላፊው፣ ይህ ማለት የተቀሩት አትሌቶች ውጤት ገና በመጣራት ላይ እንደሆነ ግንዛቤ ሊወስድ እንደሚገባውም ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም ኢትዮጵያ በአበረታች ቅመሞች ላይ እያደረገች ያለውን የቁጥጥርና የክትትል እንዲሁም ግንዛቤ በማስጨበጡ ረገድ ያረገችውን እንቅስቃሴ የሚያሳይ የዘጠኝ ወራት ሪፖርት ለዋዳ መላኩንና የዋዳ ግብረ መልስም ‹‹ጥሩ›› እንደሆነ መግለጹን ጭምር አቶ መኰንን አስረድተዋል፡፡
የዓለም አቀፍ አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማኅበር (አይኤኤኤፍ) የፀረ አበረታች ቅመሞች ኤጀንሲ (ዋዳ) ኢትዮጵያ በዚህ ችግር ውስጥ ከሚገኙ አምስት አገሮች አንዷ እንደነበረችና ለዚያም አስፈላጊውን ክትትልና ቁጥጥር ማድረግ እንዳለባት ጭምር ማስጠንቀቁ አይዘነጋም፡፡