Saturday, December 2, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜናየቤቶች ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤትና የመተሐራ ስኳር ፋብሪካ ከፍተኛ ኃላፊዎች ተከሰሱ

የቤቶች ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤትና የመተሐራ ስኳር ፋብሪካ ከፍተኛ ኃላፊዎች ተከሰሱ

ቀን:

  • በሁለቱ ተቋማት ከ74.9 ሚሊዮን ብር በላይ ጉዳት ደርሷል ተብሏል

የአዲስ አበባ ቤቶች ልማት ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት ወ/ሮ ፀዳለ ማሞን ጨምሮ 13 የተለያየ ኃላፊነት በነበራቸው ግለሰቦች፣ በኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን የመተሐራ ስኳር ፋብሪካ ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት አቶ ዘነበ ይማምን ጨምሮ ሦስት የተለያየ ኃላፊነት በነበራቸው ግለሰቦች ላይ፣ ዓርብ መስከረም 5 ቀን 2010 ዓ.ም. ክስ ተመሠረተ፡፡

የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ በሁለቱም ተቋማት ኃላፊዎች ላይ ክስ የመሠረተው በተለያየ የክስ መዝገብ ሲሆን፣ በሁለቱም ተቋማት በኃላፊነት ተመድበው ይሠሩ የነበሩት ግለሰቦች በድምሩ ከ74.9 ሚሊዮን ብር በላይ በመንግሥት ላይ ጉዳት ማድረሳቸውን፣ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ተረኛ ችሎት ያቀረበው ክስ ያስረዳል፡፡

ዓቃቤ ሕግ በአዲስ አበባ ቤቶች ልማት ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት ኃላፊዎች ላይ ያቀረበው ክስ እንደሚያስረዳው፣ ሰባቱ ተከሳሾች ማለትም ዋና ሥራ አስኪያጇ ወ/ሮ ፀዳለ ማሞ፣ የሎጂስቲክስ አስተዳደርና ፋይናንስ መምርያ ኃላፊ አቶ የማነ ፀጋዬ፣ የመሬት ዝግጅት የመሠረተ ልማትና ዲዛይን ረዳት መምርያ ኃላፊ ወ/ሮ ሳባ ገብረ መድኅን፣ የፕላንና ዶክመንቴሽን አገልግሎት ኃላፊ አቶ ሽመልስ ዓለማየሁ፣ የኮንስትራክሽንና ሱፐርቪዥን መምርያ ኃላፊ አቶ የማነ አብርሃ ተስፋ ሥላሴ (የአሰር ኮንስትራክሽን ባለድርሻ ሲሆኑ ያልተያዙ ናቸው)፣ የመሬት ዝግጅት መሠረተ ልማትና ዲዛይን መምርያ ኃላፊ አቶ ወንድወሰን ደምረው (ያልተያዙ) እና የውስጥ ኦዲትና ኢንስፔክሽንና አገልግሎት መምርያ ኃላፊ አቶ ሲሳይ በቀለ (ያልተያዙ)፣ የጽሕፈት ቤቱ የማኔጅመንት ኮሚቴ አባል ናቸው፡፡ ተከሳሾቹ የመንግሥትን የግዥ ሥርዓት ይበልጥ ግልጽ ለማድረግ፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የዕቃና የአገልግሎት ግዥ መምርያ ቁጥር 4/1991 አንቀጽ 6(2)ን በመተላለፍና የተጣለባቸውን አገራዊ ኃላፊነት ወደ ጎን በመተው ሕገወጥ ክፍያ መፈጸማቸውን ዓቃቤ ሕግ በክሱ ገልጿል፡፡

ተከሳሾቹ የጥቅም ግንኙነት በመፍጠር የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለሥልጣን ያወጣውን ጨረታ በመጠቀምና አሸናፊ የሆኑትን ለማሠራት በመወሰን አፈር ቆርጦ ለመጣል፣ ለማጓጓዝና ገረጋንቲ ለመሙላት የ33,384,526 ብር ግዢ ከየማነ ግርማይ ኮንስትራክሽን መሣሪያዎች አከራይ ድርጅት እንዲፈጸም ማድረጋቸውን ዓቃቤ ሕግ በክሱ አብራርቷል፡፡ ይህም ሕገወጥ ግዥ መሆኑን አክሏል፡፡

ማክሼብ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር፣ ቢኤ ኦሜጋ ቢዝነስ ግሩፕና ፍትዊ ወልዳይ የደረቅ ጭነት ማመላለሻ ድርጅቶች አፈር ቆርጦ ለመጣል፣ ገረጋንቲ ሞልቶ ለመጠቅጠቅና ለማጓጓዝ ካሸነፉበት የጨረታ ዋጋ በላይ ከ80 እስከ 120 በመቶ የሚሆን ከፍተኛ ዋጋ ላቀረበው የማነ ግርማይ ኮንስትራክሽን መሣሪያዎች አከራይ ድርጅት በመስጠት፣ በመንግሥት ላይ 11,979,848 ብር ጉዳት እንዲደርስ ማድረጋቸውን ዓቃቤ ሕግ በክሱ ዘርዝሯል፡፡

ተከሳሾቹ የአስተዳደሩን የግዥ መመርያ በማክበር የሚፈለገውን ዕቃ ይገኝባቸዋል ተብሎ የሚታመንባቸውን ተጫራቾች በአቅራቢዎች ዝርዝር ውስጥ የተመዘገቡትን በማሳተፍ ሦስቱን መርጠው ማወዳደር ሲገባቸው፣ ሥልጠናቸውን አላግባብ በመገልገል የሎደር ኪራይ አገልግሎት ግዥ ከመመርያው በተቃራኒ ሁለት ድርጅቶችን ብቻ ማወዳደራቸውን ዓቃቤ ሕግ በክሱ ገልጿል፡፡ የሎደር ኪራይ አገልግሎቱንም ለየማነ ግርማይ ኮንስትራክሽን መሣሪያዎች አከራይ ድርጅት በመስጠት 950,246 ብር እንዲከፈለው ማድረጋቸው አግባብ እንዳልሆነም አክሏል፡፡ ለገረጋንቲ ግዥና ለማጓጓዣያ ያላግባብ 206,638 ብር፣ እንዲሁም ገረጋንቲ ለመጠቅጠቅ 6,007 ብር፣ አፈር ቆርጦ ለመጣል 2,893 ብር በድምሩ 185,242 ብር ያላግባብ ክፍያ እንዲፈጸም በማድረግ በመንግሥት ላይ ጉዳት ማድረሳቸውን ዓቃቤ ሕግ በክሱ በዝርዝር አስረድቷል፡፡

ዓቃቤ ሕግ በሌላ ክስ የመሠረተባቸው የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን የመተሐራ ስኳር ፋብሪካ ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት አቶ ዘነበ ይማም (ሁለት ክስ ቀርቦባቸዋል) እና የጠቅላላ ሒሳብ ቡድን መሪ አቶ በለጠ ዘለለው ናቸው፡፡ በሁለቱ ተከሳሾች ላይ የቀረበው ክስ እንደሚያስረዳው በ2005 ዓ.ም. መጨረሻና በ2006 በጀት ዓመት መጀመርያ ላይ ፋብሪካውን ለማስጠገን በማሰብ፣ የህንድ ኩባንያ ከሆነው ስሪ ስታር ጋር ውል ይፈጽማሉ፡፡

ውሉን ሲዋዋሉ በድርጅቱ ውስጥ ቀደም ብሎ የተገዙ ለፋብሪካው ጥገና ሊውሉ የሚችሉ መለዋወጫዎች በፋብሪካው መደርደርያ ላይ እንዳለ እያወቁ፣ የዕቃ አቅርቦት፣ ጥገናና ሙከራ በማለት የ1,293,850 ዶላር ውል መፈጸማቸውን ዓቃቤ ሕግ በክሱ አብራርቷል፡፡ በመሆኑም ፋብሪካው ዕቃው እያለው 861,850 ዶላር ወይም 16,289,180 ብር ያላግባብ ክፍያ እንዲፈጸም ማድረጋቸውንም አክሏል፡፡

የፋብሪካው ጥገና የተፈለገው የማምረት አቅሙን ለማሻሻል ቢሆንም፣ ፋብሪካው በአግባቡ አለመጠገኑን በማየት በውሉ መሠረት ኃላፊዎቹ ውሉን ማቋረጥ ሲገባቸው፣ የውሉን 90 በመቶ 22,296,865 ብር ክፍያ በመፈጸማቸውና በፋብሪካው ላይ የምርት ብክነትና የ36,363,600 ብር ጉዳት መድረሱን ዓቃቤ ሕግ በክሱ ገልጿል፡፡ በተጨማሪም ለሠራተኞች የተከፈለውን 97,325 ብር ባለመቀነሳቸው ጉዳት መድረሱን ዓቃቤ ሕግ አክሏል፡፡ በድምሩ በፋብሪካው ላይ የ54.6 ሚሊዮን ብር ጉዳት መድረሱንም አስታውቋል፡፡

አቶ ዘነበ ይማም የፋብሪካው የአገር ውስጥና የውጭ ግዥ ቡድን አስተባባሪ አቶ እንዳልካቸው ግርማና የውጭ አገር ግዥ ሲኒየር ኦፊሰር ከሆኑት አቶ ኃየሎም ከበደ ጋር ሌላ ክስ ቀርቦባቸዋል፡፡ እንደ ዓቃቤ ሕግ ክስ ሦስቱም የፋብሪካው ኃላፊዎች በድምሩ ከ7.1 ሚሊዮን ብር በላይ ጉዳት ማድረሳቸውን ዓቃቤ ሕግ በክሱ አብራርቷል፡፡

ኃላፊዎቹ በመንግሥት ላይ ጉዳት አድርሰዋል የተባለው ከተለያዩ የውጭ ኩባንያዎች ጋር ከፈጸሟቸው አምስት የተለያዩ ግዢዎች ጋር በተያያዘ መሆኑን ዓቃቤ ሕግ አስረድቷል፡፡

ለፋብሪካው የሚሆኑ መለዋወጫዎችን ሞካር ኢንተርፕራይዝ ከሚባል የህንድ ኩባንያ፣ ፋንታነ ቢቪ ከተባለ የኔዘርላንድ ኩባንያ፣ ዩኒንግ ሆላንድ ከተባለ የኔዘርላንድ ኩባንያ (ሁለት ጊዜ) እና ኤስኤኤፍ ሰልፈር ይክታሪ ከተባለ የሳዑዲ ዓረቢያ ኩባንያ በድምሩ በ13,104,049 ብር ግዥ መፈጸማቸውን ዓቃቤ ሕግ በክሱ አብራርቷል፡፡ ግዥ የተፈጸመው ግን ከኩባንያዎቹ ጋር ውል ሳይፈጸም በመሆኑ አቅራቢዎቹ በተቀመጠው የጊዜ ገደብ ዕቃውን ባያቀርቡ፣ በዕቃ ግዥ ዋጋ ላይ በየቀኑ ዜሮ ነጥብ አንድ በመቶ ይከፈላል የሚለውን የስኳር ኮርፖሬሽን መመርያን የማያከብርና የሚጥስ መሆኑን ዓቃቤ ሕግ አብራርቷል፡፡ በመሆኑም ኃላፊዎቹ በተለያዩ ጊዜያትት በድምሩ 7,151,146 ብር በመክፈል ጉዳት ማድረሳቸውን ዓቃቤ ሕግ በክሱ በዝርዝር ጠቅሷል፡፡

የአዲስ አበባ ቤቶች ልማት ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት ኃላፊዎች የወንጀል ሕግ አንቀጽ 32(1ሀ)፣ 33 እና 411(2እና3) 407(1ሀ)ን በመተላለፍና ሥልጣናቸውን ያላግባብ በመጠቀም፣ 13,162,161 ብር በመንግሥት ላይ ጉዳት ማድረሳቸውን የዓቃቤ ሕግ ክስ ያስረዳል፡፡ የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽንም ኃላፊዎች ተመሳሳይ የወንጀል ሕግ ድንጋጌን በመተላለፍ በድምሩ 20,313,307 ብር ጉዳት በመንግሥት ላይ ማድረሳቸውንም የዓቃቤ ሕግ ክስ ያሳያል፡፡ በሁለቱ ተቋማት በድምሩ ከ74.9 ሚሊዮን ብር በላይ በመንግሥት ላይ ጉዳት መድረሱን የዓቃቤ ሕግ ክስ ያብራራል፡፡

ፍርድ ቤቱ በችሎት እንደተናገረው በሁለቱም ተቋማት ኃላፊዎች ላይ የተጠቀሰው የሕግ አንቀጽ ከአሥር ዓመታት በላይ የሚያስቀጣና ዋስትናም የሚከለክል ነው፡፡ በመሆኑም ተከሳሾቹ በማረሚያ ቤት ሆነው ክሳቸውን እንዲከታተሉ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡ የክስ መቃወሚያ ለመጠባበቅ ለጥቅምት 2 ቀን 2010 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ የመተሐራ ስኳር ፋብሪካ የውጭ ግዢ ሲኒየር ኦፊሰር አቶ ኃየሎም ከበደ አቅም ስለሌላቸው ጠበቃ ማቆም እንደማይችሉ በመግለጻቸው ቃለ መሀላ እንዲፈጽሙ ተደርጎ፣ የተከላካይ ጠበቆች ጽሕፈት ቤት ተከላካይ ጠበቃ እንዲያቆምላቸው ትዕዛዝ ተሰጥቷል፡፡ ከአዲስ አበባ ቤቶች ልማት ጽሕፍት ቤት የፋይናንስ አስተዳደር መምርያ ኃላፊ ወ/ሮ አልማዝ አይናለምና የግዢ አቅርቦት መምርያ ኃላፊ አቶ ወንድሙ መንግሥቱ የተጠቀሰባቸው የወንጀል ሕግ አንቀጽ ዋስትና ስለማይከለክል፣ ፍርድ ቤቱ እያንዳንዳቸው 15 ሺሕ ብር ዋስ በማስያዝ ከእስር እንዲፈቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የመቃወም ነፃነት ውዝግብ በኢትዮጵያ

ስሟ እንዳይገለጽ የጠየቀችው በአዲስ አበባ ከተማ በተለምዶ የሾላ አካባቢ...

የሲሚንቶን እጥረትና ችግር ታሪክ ለማድረግ የተጀመረው አጓጊ ጥረት

በኢትዮጵያ በገበያ ውስጥ ለዓመታት ከፍተኛ ተግዳሮት በመሆን ከሚጠቀሱ ምርቶች...

የብሔር ፖለቲካው ጡዘት የእርስ በርስ ግጭት እንዳያባብስ ጥንቃቄ ይደረግ

በያሲን ባህሩ በሪፖርተር የኅዳር 9 ቀን 2016 ዓ.ም. ዕትም “እኔ...