- በሚኒስቴሩና በባለሥልጣኑ ከፍተኛ ኃላፊዎች ላይ ምርመራ ተጠናቀቀ
የኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን ከ32 ሚሊዮን ብር በላይ ያላግባብ ክፍያ እንዲፈጸም በማድረግ የተጠረጠሩና በፓን አፍሪካ ድርጅት ውስጥ አማካሪ የሆኑ ግለሰብ፣ በቁጥጥር ሥር ውለው ፍርድ ቤት ቀረቡ፡፡
ተጠርጣሪው አቶ እስክንድር ሰይድ የሚባሉ ሲሆኑ፣ በባለሥልጣኑ ላይ የተጠቀሰውን ጉዳት ያደረሱት ከሌላ ተቋማት ጋር በማገናኘት መሆኑን የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቡድን ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ተረኛ ችሎት አስረድቷል፡፡ የተቋሙን ማንነትና በምን ሁኔታ ግንኙነት ፈጥረው የተጠቀሰውን ከ32 ሚሊዮን ብር በላይ ክፍያ እንዲፈጸም እንዳደረጉ ለማወቅ ገና በምርመራ ላይ መሆኑን የገለጸው መርማሪ ቡድኑ፣ ለተጨማሪ ምርመራ 14 ቀናት እንዲፈቀዱለት ፍርድ ቤቱን ጠይቋል፡፡
የተጠርጣሪው ጠበቃ ደንበኛቸው ባለሥልጣኑን ከየትኛው ተቋም ጋር እንዳገናኙና ክፍያ እንደተፈጸመ መርማሪ ቡድኑ ሳያስረዳ፣ ደንበኛቸውን አስሮ ማስረጃና መረጃ ሊፈልግ ስለማይገባ የዋስትና መብታቸው እንዲከበር ጠይቀዋል፡፡
መርማሪ ቡድኑ የዋስትና ጥያቄውን በመቃወም ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዳው፣ ተጠርጣሪው ከተያዙ ገና አንድ ቀናቸው ነው፡፡ የጉዳቱ መጠን የተገኘው ቀደም ብሎ በተጠረጠሩበት ከባድ የሙስና ወንጀል በቁጥጥር ሥር ከሚገኙት ተጠርጣሪዎች ምርመራ መሆኑን አስረድቷል፡፡ ግለሰቡ አሁን በማማከር ከሚሠሩበት ፓን አፍሪካ ከሚባል ድርጅት ጋር ግንኙነት እንዳለው በማስረዳት ለተጨማሪ ምርመራ የጠየቀው ጊዜ እንዲፈቀድለት በድጋሚ ጠይቋል፡፡
ፍርድ ቤቱ ተጠርጣሪው የጠየቁትን የዋስትና መብት ውድቅ በማድረግ መርማሪ ቡድኑ ከጠየቀው 14 ቀናት አሥር ቀናትን ፈቅዷል፡፡ ለመስከረም 12 ቀን 2010 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
መርማሪ ቡድኑ ከሐምሌ 18 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ በተለያዩ ቀናቶች በቁጥጥር ሥር በማዋል ሲመረምራቸው በከረሙት፣ በኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር በነበሩት አቶ ዛይድ ወልደ ገብርኤል የምርመራ መዝገብ የተካተቱ 12 ተጠርጣሪዎችን የምርመራ ሒደት ማጠናቀቁንና ለዓቃቤ ሕግ ማስረከቡን ለፍርድ ቤቱ አስታውቋል፡፡
በተመሳሳይ ሁኔታ በገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ዓለማየሁ ጉጆ የምርመራ መዝገብ 19 ተጠርጣሪዎችም ላይ ምርመራ ጨርሶ መዝገቡን ለዓቃቤ ሕግ ማስረከቡን ገልጿል፡፡ ዓቃቤ ሕግም መቀበሉን በማረጋገጡ ክስ መሥርቶ መስከረም 12 ቀን 2010 ዓ.ም. እንዲቀርብ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
አቶ ዛኪር አህመድ በእነ አቶ ዛይድ ወልደ ገብርኤል የምርመራ መዝገብ ምርመራቸው የተጠናቀቀ መሆኑን መርማሪ ቡድኑ ለፍርድ ቤቱ ገልጾ፣ በኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን በኩል የተጠረጠሩበትን የወንጀል ጉዳይ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኦዲተር ቢሮ ሒሳብ እያሠራ በመሆኑ ተጨማሪ ጊዜ እንዲሰጠው ጠይቋል፡፡ የአቶ ዛኪር ጠበቃ ግን የመርማሪ ቡድኑን ጥያቄ በመቃወም እንደገለጹት፣ ደንበኛቸው ከነሐሴ 11 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ በእስር ላይ ናቸው፡፡ እስካሁን መጨረስ ነበረበት፡፡ አሁንም ቢሆን ኦዲት የሚሠራው የመንግሥት ተቋም በመሆኑ ከእሳቸው ጋር የሚያገናኘው ነገር እንደሌለ አስረድተዋል፡፡ በመሆኑም መርማሪ ቡድኑ ተጨማሪ ጊዜ ሊፈቀድለት እንደማይገባ በመግለጽ ተቃውመዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ግን መርማሪ ቡድኑ ምርመራውን በማፋጠን እንዲያጠናቅቅና ከሌሎቹ ተጠርጣሪዎች ጋር ጎን ለጎን በመሥራት ክሱን እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
በሌላ የምርመራ መዝገብ ስማቸው የተካተተው በስኳር ኮርፖሬሽን የተንዳሆ ስኳር ፋብሪካ የአገዳ ተክልና ፋብሪካ ግንባታ ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ አበበ ተስፋዬን ጨምሮ፣ ስምንት ተጠርጣሪዎችና የኦሞ ኩራዝ አምስት ስኳር ፋብሪካ ሥራ አስኪያጅ አቶ መስፍን መልካሙን ጨምሮ ሰባት ተጠርጣሪዎችን የምርመራ ሒደት ማጠናቀቁንና ለዓቃቤ ሕግ ማስተላለፉን መርማሪ ቡድኑ ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡ ፍርድ ቤቱም የምርመራ መዝገቡ ለዓቃቤ ሕግ መድረሱን ካረጋገጠ በኋላ፣ ለመስከረም 11 ቀን 2010 ዓ.ም. ዓቃቤ ሕግ ክስ መሥርቶ እንዲቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡