የሥርዓተ ምግብ አገልግሎትን አስመልክቶ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በተደረገ የዳሰሳ ጥናት 192 ወረዳዎች በአስከፊ መልኩ መጎዳታቸውን ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
ሚኒስቴሩ የጤናው ሴክተር የ2009 በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት ዕቅድ አፈጻጸሙን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረበበት ወቅት እንዳስታወቀው፣ 174 ወረዳዎች በከፍተኛ ደረጃ፣ 88 ወረዳዎች በመካከለኛ ደረጃ ባጠቃላይም 454 ወረዳዎች የተጎዱ ተብለው ተለይተዋል፡፡
በወረዳዎቹ የተከሰቱና ሊከሰቱ የሚችሉ የጤናና የሥርዓተ ምግብ ችግሮች የተለዩ ሲሆን፣ ከፍተኛ የምግብ እጥረት በተለይም በዝቅተኛ የሥርዓተ ምግብ ሁኔታ ላይ የነበሩ ሕፃናት፣ ነፍሰ ጡሮችና የሚያጠቡ እናቶች የችግሩ ዋነኛ ተጋላጭ በመሆናቸው፣ ይህንን ለመታደግ ቅንጅታዊ ሥራ ተከናውኗል፡፡
እንደ ሪፖርቱ፣ በአርብቶ አደር አካባቢዎች ድርቅ መከሰቱ የሥርዓተ ምግብ እጥረትና የጤና ችግሮች ተጋላጭነትን ጨምሮታል፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ በአማራ 19,023፣ በአፋር 10,919፣ በኦሮሚያ 60,793፣ በደቡብ 27,438፣ በኢትዮጵያ ሶማሌ 18,333፣ በትግራይ 6,118፣ በቤንሻንጉል ጉሙዝ 950 እና በጋምቤላ 797 ሕፃናት ሕክምና አግኝተዋል፡፡
ዘንድሮ በተከሰተው የአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት (አተት) ወረርሽኝ በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል የነበረው ከፍተኛ ሥርጭት እየቀነሰ መሆኑም ተገልጿል፡፡ በኦሮሚያ ክልል ውስጥ በሚገኙ ጥቂት ወረዳዎችም ወረርሽኙ ታይቷል፡፡
ኢትዮጵያ የሦስትዮሽ በሽታ ጫና ውስጥ መግባቷን ሪፖርቱ አስታውሶ፣ ለዚህም ተላላፊ በሽታዎች አለመቀነሳቸው፣ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችና መንስኤዎቻቸው፣ የትራፊክ አደጋና አካላዊ ጉዳት እየጨመረ መምጣቱ እንደምክንያት እንደሚወሰዱ ተገልጿል፡፡