በኢትዮጵያ በ1960ዎቹ የፖለቲካ ትግል ውስጥ ከተሳተፉት አንዱ ነበሩ፡፡ የሕግ ባለሙያው አቶ አሰፋ ጫቦ፡፡ የንጉሠ ነገሥት መንግሥት በ1967 ዓ.ም. ከተወገደ በኋላ ከተቋቋሙት የፖለቲካ ፓርቲዎች አንዱ የነበረው ኢጭአት (የኢትዮጵያ ጭቁን አብዮታዊ ትብብር) መሥራችና ሊቀመንበር የነበሩት አቶ አሰፋ በዘመነ ደርግ የታወቁ ፖለቲከኛ ነበሩ፡፡
ፓርቲያቸው በኢማሌድኅ (የኢትዮጵያ ማርክሲስት ሌኒኒስት ድርጅቶች ኅብረት) አካል ሆኖ ቢቆይም በነበራቸው አቋም ምክንያት በኅብረተሰብአዊት ኢትዮጵያ ጊዜያዊ ወታደራዊ መንግሥት ለ11 ዓመታት በእስር ቆይተዋል፡፡
በ1983 ዓ.ም. የመንግሥት ለውጥ ከተደረገ በኋላ በኢትዮጵያ ሽግግር መንግሥት ምክር ቤት ውስጥ የኦሞቲክ ፓርቲን በመወከል ሠርተዋል፡፡
በ1984 ዓ.ም. ወደ አሜሪካ በማቅናት ለሩብ ምእት ዓመት በስደት ያሳለፉት አቶ አሰፋ፣ ለበርካት ዓመታት ድምፃቸው ሳይሰማ ቆይቶ ከሦስት ዓመት ወዲህ በማኅበራዊና በኅትመት ሚዲያዎች በአገራዊ ጉዳይ የተለያዩ ጽሑፎችን ያቀርቡ ነበር፡፡
አንደበተ ርቱዕና ዕሙሩ (ታዋቂው) ብዕረኛ አቶ አሰፋ በተለያዩ መገናኛዎች ቀደም ሲል ያወጧቸውን መጣጥፎች ‹‹የትዝታ ፈለግ›› በሚል ርዕስ በቅርቡ አሳትመዋል፡፡
ከአባታቸው ከአቶ ጫቦ ሰዴ እና ከእናታቸው ከወ/ሮ ማቱኬ አቾ፣ በቀድሞ አጠራር በጋሞ ጎፋ ጠቅላይ ግዛት ጨንቻ ከተማ የተወለዱት አቶ አሰፋ፣ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን በጨንቻ ከተማ ተምረዋል፡፡ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸው ካጠናቀቁ በኋላ በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዩኒቨርሲቲ በሕግ ተመርቀዋል፡፡
ከንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት ጀምሮ በአጥቢያ ፍርድ ቤትና በጅሮንድ ጽሕፈት ቤት ጸሐፊ፣ በኢትዮጵያ ሜትሮሎጂ አገልግሎት የሕግ አማካሪ በመሆን አገልግለዋል፡፡
ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በአሜሪካ በሕክምና ሲረዱ ቆይተው በተወለዱ በ75 ዓመታቸው ሚያዝያ 15 ቀን 2009 ዓ.ም. አርፈው፣ ሥርዓተ ቀብራቸው ሚያዝያ 27 ቀን በመንበረ ጸባâት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል፡፡
አንድ ገጣሚ በማኅበራዊ ድረ ገጽ ለአቶ አሰፋ ካንጎራጐረው አንዱ
አንጓ፣
‹‹አንደበተ ርቱዕ ቀዝቃዛ
ባለ ብዕር ባለ ለዛ፤
አማርኛን በአማርኛ የምትቃኝ፣
በውስጠ ወይራ ቅኔ አሳማኝ፤››
የሚል ነው፡፡