በዋጋዬ ብርሃኑ
የሕዋ ሳይንስ ፕሮግራም በኢትዮጵያ ከተጀመረ ጥቂት ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እንዲሁም የተፈጥሮ አደጋ ለመከላከል የቅድመ ትንበያ ግብዓት የሚሆን ጠቃሚ መረጃ በማቅረብ፣ ወዘተ በኩል የሕዋ ጥናት ቴክኖሎጂ ከፍተኛ ጥቅም ይሰጣል ተብሎ ይታመናል፡፡
በኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩትና ዓለም አቀፍ ተባባሪዎች ድጋፍ የተዘጋጀና ለሁለት ሳምንታት የሚቆይ 39ኛው ዓለም አቀፍ የሥነ ፈለክ ዐውደ ጥናት ሚያዝያ 30 ቀን 2009 ዓ.ም. በአክሱም ሆቴል ተከፍቷል፡፡ ከኢትዮጵያና ከሌሎች የአፍሪካ አገሮች የተውጣጡ በሥነ ፈለክና አስትሮፊዚክስ የትምህርት ዘርፎች በድኅረ ምረቃ ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ የሚገኙ ሠላሳ ወጣቶችን የዕውቀት አድማስ ለማስፋት ታስቦ የተዘጋጀው ዐውደ ጥናት ከንድፈ ሐሳብ በተጨማሪ ተግባራዊ የሕዋ ምልከታንም ያካተተ እንደሚሆን ተገልጿል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ ዐውደ ጥናቱ በሥነ ፈለክና የሕዋ ሳይንስ ዘርፎች ትስስር ለመፍጠር፣ በሥነ ፈለክና አስትሮፊዚክስ ወደፊት ጥናትና ምርምር የማድረግ ዓላማ ላላቸው ተማሪዎች አቅጣጫ ለማመላከት፣ በአፍሪካ በተለይም በምሥራቅ አፍሪካ የሥነ ፈለክ ጥናትን ለማሳደግና በዘርፉ ቀጣናዊና ዓለም አቀፍ ትብብር ለመመሥረት ብሎም ለማጠናከር ይረዳል ተብሎ ይጠበቃል፡፡