የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ለታዋቂና ለወጣት አትሌቶች አበረታች መድኃኒቶችን (ዶፒንግ) አስመልክቶ ሰሞኑን የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ በማዘጋጀት ምክክር አድርጓል፡፡
ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ ሚያዝያ 22 ቀን 2009 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ሆቴል ባዘጋጀው መድረክ ላይ የወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር የፀረ ዶፒንግ ዳይሬክተር (ዶ/ር) አያሌው ጥላሁን እንደተናገሩት፣ ማንኛውም አትሌት ለሕመም የሚወስደውን መድኃኒት ተጠንቅቆ ማወቅ እንደሚጠበቅበትና በባለሙያ ትዕዛዝ ብቻ መውሰድ አለበት፡፡
አትሌቶች ወደ ሕክምና ተቋም በሚሄዱበት ወቅት አትሌት መሆናቸውን በቅድሚያ መግለጽ እንደሚገባቸውም አስገንዝበዋል፡፡ ለአስም በሽታ ተብለው የሚወሰዱ መድኃኒቶች፣ በተለይ ሜልዶንየም የሚባለው ንጥረ ነገር ላይ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባም አብራርተዋል፡፡
አትሌቶች ከልምምድ በፊት፣ ከልምምድ በኋላና ከውድድር በፊት መመገብ ያለባቸውን ምግብ ጠንቅቀው በማወቅ ትክክለኛውን የአመጋገብ ሥርዓት መከተል ይገባቸዋልም ተብሏል፡፡
አትሌቶች ክስ ከቀረበባቸው አካላት ጋር መገናኘት፣ ልምምድ ማድረግና የሥልጠና ምክር ማግኘት ወንጀለኛ እንደሚያስብላቸው የተናገሩት የፌዴሬሽኑ ባለሙያ ወይዘሪት ቅድስት ታደሰ ናቸው፡፡
በመድረኩ የአትሌቶች መገኛ አድራሻ ቅጽ አሞላል ግንዛቤ የሚያስጨብጥ ሥልጠና የተሰጠ ሲሆን፣ አትሌቶች በዘመናዊ ተንቀሳቃሽ ስልካቸው (ስማርት ፎን) በመታገዝ ልምምድ ሲያደርጉና ወደ ውጭ አገር ለውድድር ሲያመሩ አስፈላጊውን መረጃ መስጠት እንዳለባቸውም ተብራርቶላቸዋል፡፡ በውይይቱ ቀነኒሳ በቀለ፣ ገንዘቤ ዲባባ፣ ጥሩነሽ ዲባባ፣ መሠረት ደፋር፣ መሰለች መልካሙ፣ ሶፍያ አሰፋና ሌሎች አትሌቶችም ተገኝተዋል፡፡