- ለምግብ እህል ግዥ ከ740 ሚሊዮን ዶላር በላይ ያስፈልጋል ተብሏል
በበግልና በመኸር ወቅት በተከሰቱት የዝናብ እጥረት እንዲሁም በውርጭ፣ በበረዶና ባልተጠበቀ የጎርፍ አደጋ ሳቢያ በሦስት ክልሎች በደረሰው ጉዳት፣ የዕለት ደራሽ ዕርዳታ ፈላጊዎች ቁጥር ቀድሞ ከነበረው 5.6 ሚሊዮን በላይ በማሻቀብ ከ7.8 ሚሊዮን በላይ መንግሥት ይፋ አደረገ፡፡
የብሔራዊ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ደበበ ዘውዱ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በበልግና በመኸር ወቅት በተደረገ የሰብል ምርት ዳሰሳ ጥናት መሠረት ከዚህ ቀደም በነበሩት የ5.6 ሚሊዮን ተጎጂዎች በተጨማሪ ከሁለት ሚሊዮን በላይ ተጨማሪ ዜጎች ዕለት ደራሽ የምግብ ዕርዳታ እንደሚያፈልጋቸው ተረጋግጧል፡፡ በመሆኑም በኦሮሚያ ከ1.5 ሚሊዮን በላይ፣ በአማራ ክልል ከ304 ሺሕ በላይ፣ እንዲሁም በደቡብ ክልል ከ203 ሺሕ በላይ፣ በድምሩ ከ2.06 ሚሊዮን በላይ ሰዎች ተጋላጭ መሆናቸው ተረጋግጧል፡፡
ተጨማሪው ጉዳት የደረሰው በቆላማዎቹ የኢትዮጵያ አካባቢዎች በተለይም በደቡብና በምሥራቅ ኢትዮጵያ ክፍሎች ካለፈው ዓመት ጀምሮ የተከሰተው ድርቅ ዘንድሮም ተራዝሞ ከመቀጠሉም በላይ፣ በአማራ ክልል የተከሰተው የውርጭ፣ የበረዶና የጎርፍ አደጋ በቋሚ ሰብሎችና በአትክልት ምርቶች ላይ ጉዳት ማድረሱ ተገልጿል፡፡ በመሆኑም መንግሥት ለተጎጂዎቹ የምግብ ዕርዳታ ለማቅረብ የሚያስፈልገው የገንዘብ መጠንም ከ740 ሚሊዮን ዶላር በላይ መደረሱን አቶ ደበበ አስታውቀዋል፡፡
በዚህ ዓመት የተከሰተው ድርቅ 5.6 ሚሊዮን ሕዝብ ለዕለት ደራሽ ዕርዳታ ያስፈልጋል የተባለው የገንዘብ መጠን 948 ሚሊዮን ዶላር እንደነበር፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በቅርቡ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ባቀረቡት ሪፖርት አስታውቀው ነበር፡፡ ከዚህ ገንዘብ ውስጥ ለምግብና ለነፍስ አድን ተጨማሪ ምግቦች ከ715 ሚሊዮን ዶላር በላይ ያስፈልግ እንደነበር መግለጻቸው ይታወሳል፡፡ ሆኖም በአሁኑ ወቅት ቁጥራቸው ከ7.8 ሚሊዮን በላይ ለደረሱት ተጎጂዎች የሚያስፈልገውን የምግብ ነክ ዕርዳታ ለማሟላት ከ740 ሚሊዮን ዶላር በላይ አስፈልጓል፡፡ በመሆኑም ተጨማሪ 25 ሚሊዮን ዶላር ለምግብ እህል መግዣ ይፈለጋል፡፡
ዓምና በኤልኒኖ ሳቢያ ተከስቶ የነበረው ድርቅ 10.2 ሚሊዮን ሕዝብ ለምግብ ዕርዳታ አጋልጦ እንደበነበር አይዘነጋም፡፡ ይሁንና መንግሥት የሚጠበቀውን ያህል ዕርዳታ ከዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ማግኘት እንዳልቻለና በራሱ እንደሚወጣው አስታውቆ ነበር፡፡ ከዚህ ድርቅ ጉዳት ያላገገመው የቆላማው አካባቢ ሕዝብ ዳግም በበልግ ዝናብ መዘግየት፣ እንዲሁም በውርጭና ዝናብ ሳቢያ በመጎዳቱ በአሁኑ ወቅት የተጠቀሰውን ያህል ሕዝብ ለምግብ ዕርዳታ ፈላጊነት ተዳርጓል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለፓርላማው ገልጸው እንደነበረው ከለጋሽ አገሮችና ተቋማት የሚፈለገውን ያህል ዕርዳታ አሁን ማግኘት አልተቻለም፡፡ በምሥራቅና በምዕራብ አፍሪካ የተንሰራፋው የድርቅና የጦርነት ትኩሳት፣ እንዲሁም የመንን ጨምሮ በመካከለኛው ምሥራቅ የሚነደው የጦርነት እሳት የለጋሽ አገሮችን ትኩረት በመሳቡ ለኢትዮጵያ ድርቅ የሚፈለገውን ዕርዳታ ማግኘት ሳይቻል ቆይቷል፡፡
የዓለም የእርሻና የምግብ ድርጅት፣ እንዲሁም በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሥር የሰብዓዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት በዚህ ዓመት በጥርና በመጋቢት ወር ባወጡት ሪፖርት፣ ኢትዮጵያ ለአስቸኳይ ሰብዓዊ ዕርዳታ የምታውለው 948 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልጋት አስታውቀው እንደነበር ይታወሳል፡፡
ከምግብ ዕርዳታው ጎን ለጎን በሰብዓዊ ጉዳይ ድጋፍ የሚሰጡ አጋሮችና የኢትዮጵያ መንግሥት የመጠጥ ውኃ አቅርቦት በማሻሻል በሰዎች ላይ የሚደርሰውን ጉዳት ለመቀነስ፣ ብሎም የእንስሳትን እልቂት ለመግታት የመኖ አቅርቦት ላይ እየተረባረቡ እንደሚገኙ አስታውቀዋል፡፡ በዚህም መሠረት ከአራት ሚሊዮን በላይ ሰዎች ውኃ በተለያየ መንገድ እንዲያገኙ ሲደረግ፣ ከ200 ሺሕ ኩንታል በላይ መኖ ለአርብቶ አደር አካባቢዎች መከፋፈሉን የተመድ የሰብዓዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ይፋ አድርጓል፡፡