በመገናኛ አካባቢ የተገነባው በአንድ ጊዜ 90 ተሽከርካሪዎችን የሚያስተናግድ ባለ 15 ደረጃ ያለው ስማርት የመኪና ማቆሚያና 50 መኪናዎችን የመያዝ አቅም ያለው የመሬት ላይ የተሽከርካሪ ማቆሚያ ሐሙስ ሚያዝያ 12 ቀን 2009 ዓ.ም. የሙከራ ሥራውን መጀመሩ ተገለጸ፡፡ መንግሥት በመደበው ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ የተገነባው ዘመናዊ የመኪና ማቆሚያው በጥቂት ቀናት ውስጥ የሙከራ ሥራውን አጠናቆ ወደ ሙሉ አገልግሎት እንደሚገባ ተጠቁሟል፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ የትራንስፖርት ፕሮግራሞች ማስተባበርያ ጽሕፈጽ ቤት የመሠረተ ልማት ሥራ ክፍል ተወካይ አቶ ትንሳዔ ወልደ ገብርኤል እንደገለጹት፣ የመሬትና ስማርት የተሽከርካሪ ማቆሚያዎቹ በመገናኛ አካባቢ የሚታየውን የትራፊክ ፍሰት ችግር ፈር ለማስያዝ የተገነቡ ናቸው፡፡ ባለ 15 ደረጃ ያለው ስማርት የተሽከርካሪ ማቆሚያው በተገጠመለት አሳንሰር፣ ኤሌክትሪክና መካኒካል ቴክኖሎጂ ሥርዓት በመጠቀም ተሽከርካሪዎችን ራሱ አንስቶ ባለው ክፍት ቦታ የሚያቆምና የሚያወርድ ሲሆን፣ የመኪናውን ቁመት፣ ርዝመትና ክብደቱን በማገናዘብ አገልግሎት ይሰጣል ብለዋል፡፡ አያይዘውም የመኪና ማቆሚያው በ170 ካሬ ሜትር መሬት ላይ ያረፈ መሆኑን፣ ከዚህ ቀደም በነበረው የመኪና ማቆሚያ ሥርዓት ዘጠኝ መኪና የሚሸፍነውን ቦታ በአሁኑ ጊዜ በዘመናዊ መንገድ በመገንባቱ በአንድ ጊዜ 90 መኪናዎች ለማስተናገድ ማስቻሉን ተናግረዋል፡፡ የተሽከርካሪ ማቆሚያዎቹ ሙሉ አገልግሎት መስጠት ሲጀምሩ በዋና ዋና መንገዶች ላይ ተሽከርካሪዎች በመቆማቸው ምክንያት ይፈጠር የነበረው የትራፊክ መጨናነቅ የሚያስቀር እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ ፕሮጀክቱ የሙከራ ሥራውን አጠናቆ ወደ ተግባር ሲሸጋገር መንግሥት በተመነው ተመጣጣኝ ክፍያ በሁለት ሽፍት አገልግሎት የሚሰጥ እንደሆነና ከ20 ለማያንሱ ሰዎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል የሚፈጥር መሆኑንም አስረድተዋል፡፡ በአሁኑ ጊዜ ቅድሚያ በተሰጣቸው በአንዋር መስጊድ፣ በቸርችል ጎዳናና በወሎ ሠፈር አካባቢዎች የመሬትና ስማርት የተሽከርካሪ ማቆሚያ ግንባታ በመካሄድ ላይ መሆኑን ጠቁመው፣ በቀጣይነትም በመዲናዋ በተመረጡ 60 ቦታዎች የተሽከርካሪ ማቆሚያ ግንባታ የሚከናወን መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል፡፡ ይኼ ፕሮጀክት የከተማውን ውስን መሬት በአግባቡ በመጠቀም የመዲናዋን ትራንስፖርት ፈጣንና ቀልጣፋ፣ እንዲሁም ፍሰቱንና ደኅንነቱን የተስተካከለ እንዲሆን ያደርገዋል ብለዋል፡፡ ፕሮጀክቱ ለባለሀብቶች አዋጭ የኢንቨስትመንት አማራጭ መሆኑን ለማሳየትና በቀጣይ ባለሀብቶች በዘርፉ እንዲሰማሩ ታስቢ የተደረገ መሆኑንም አቶ ትንሳዔ አስረድተዋል፡፡ በቂ የፓርኪንግ ቦታ ያለመኖር የትራፊክ ፍሰቱን በማስተጓጎል ረገድ ዋነኛ ምክንያት እንደሆነ ኅብረተሰቡ ተገንዝቦ፣ የመኪና ማቆሚያዎቹ በተሠሩበት አካባቢ ተገቢውን አገልግሎት እንዲሰጡ በማስቻል የራሳቸውን አስተዋጽኦ ማበርከት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡ በምሥሉ ላይ 90 ተሽከርካሪዎችን የሚያስተናግደው ባለ 15 ደረጃ ስማርት የመኪና ማቆሚያና 50 ተሽከርካሪዎችን የመያዝ አቅም ያለው የመሬት ላይ ማቆሚያ ይታያሉ፡፡ ፎቶ፡- የትራንስፖርት ፕሮግራምስ ማኔጅመንት ጽሕፈት ቤት