አገራችን ኢትዮጵያ ከሌሎች አገሮች በተለየ ሁኔታ የሕዝቦች የእርስ በርስ ግንኙነት አላት፡፡ በበዓላት፣ በለቅሶና በሠርግ ያለን ማኅበራዊ ሕይወት እጅግ የሚያስደንቅ ነው፡፡ ለዚህም ነው አንድ ኢትዮጵያዊ ከአገር ሲወጣ የሌሎች አገሮችን ነባራዊ ሁኔታ መልመድ የሚቸገረው፡፡ በተለይ አንዳሁኑ በዓል ሲሆን ይለያል፡፡ ዘመድ አዝማድ ከያለበት መሰባሰቡና የጎረቤት መጠራራቱ ሁሌም እጅግ ልብ ይማርካል፡፡ የጠላው፣ የጠጁ፣ የዶሮው፣ የዳቦውና የቡናው ብቻ ምን አለፋችሁ ሁሉም ልዩ ነው፡፡
ዝግጅቱ ከዕለቱ ብዙ ቀናት አስቀድሞ ይጀመራል፡፡ ገበያው ይደምቃል፣ ግርግሩ፣ ወከባው፣ ጭሱ ሁሉም የበዓሉ አካል ናቸው፡፡ ለበዓሉ ድምቀት የራሳቸው አስተዋጽኦ አላቸው፡፡ አባወራ፣ እማወራ፣ ልጆች ሁሉም ድርሻ ይኖራቸዋል፡፡ ከሁሉም የእማወራዋ ድርሻ ከፍ ቢልም፡፡
ለበዓላት የሬዲዮና የቴሌቪዥን ጣቢያዎች የሚከፈቱት በዓል፣ በዓል የሚሸቱ ሙዚቃና ማስታወቂያዎችም አስተዋጽኦዋቸው ከፍተኛ ነው፡፡ የቅቤ፣ የበርበሬ፣ የዶሮ፣ የእንቁላል፣ የሽንኩርት፣ የዳቦ ዱቄት፣ ጌጣጌጥ፣ የአገር ባህል አልባሳትና ጫማዎች ሁሉም ያስተዋውቃል፡፡ በታላቅ ቅናሽ፣ ሁሉንም በአንድ ቦታ፣ ወዘተ. የተለመዱ ናቸው፡፡ የአዲስ አልበም ማስታወቂያም አይጠፋም፡፡ በነፃ የሚሰጡን ይመስል ልዩ የበዓል ሥጦታ ይሉናል የበዓሉ አንድ አካል ናቸውና ታያለህ ትሰማለህ፡፡
የማይታየው የሌቦች ማስታወቂያ ብቻ ነው፡፡ አሁን ግን በዓሉን ምክንያት በማድረግ አዲስ የአሰራረቅ ዘዴ አምጥተናል ብለው ማስተዋወቅ ሳይጀምሩ አይቀሩም ብዬ እጠብቃለሁ፡፡
የቴሌቪዥን ጣቢያዎቹ ደግሞ የራሳቸው ማስታወቂያ አላቸው፡፡ ‹ልዩ የበዓል ዝግጅት፣ በዓልን ከኛ ጋር ያሳልፉ፣ በዓልን ምክንያት በማድረግ ልዩ የመድረክ ፕሮግራም ከእንትን አገር፣ ኮሜዲያን እከሌና አርቲስት እከሌ የተገኙበት ከ8 ሰዓት ጀምረው ይጠብቁን፣ ፕሮግራሙን ስፖንሰር ያድርጉ፣ ምርትና አገልግሎትዎን ያስተዋውቁ› ይሉናል፡፡ የዝግጅቱን አጓጊ ቀረፃ ቀነጫጭበው እያሳዩን፡፡ እኛም በዕለቱ የሚቀርቡትን ታዋቂ ሰዎች እያወዳደርን ከየትኞቹ ጋር እንደምናሳልፍ እናማርጣለን፡፡
ከሁሉም ግን በዚሁ በበዓል ሰሞን ያልጠበኩትንና ይህንን ጽሑፍ እንድጽፍ ያነሳሳኝን በፀሎተ ሐሙስ ዕለት ዜና ዕወጃ ላይ ተመለከትኩ፡፡ ቴሌቪዥኑን ስከፍት ፓትርያርኩ አቡነ ማትያስ ቴሌቪዥኑን ሞልተው ‹እንኳን ለትንሳዔ በዓል አደረሳችሁ፣ በዓሉ የሰላም የፍቅር ይሁንላችሁ› ይላሉ በብዙ ማይክ ፊት ተቀምጠው፣ በትልቁ መስቀላቸዉ የቴሌቪዥናችንን መስኮት አየባረኩ፡፡ ግራ ገባኝ፡፡ ዛሬ ፀሎተ ሐሙስ ነገ ደግሞ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ስቀለት የምናስብበት ዕለት አይደለም እንዴ?
ገና ቤተ ክርስቲያኗ የኢየሱስ ክርስቶስን ትንሳዔ ማብሰር ሳትጀምር፣ ገና ህማማተ መስቀሉን መከራውን እያሰበች ባለችበት ሰዓት ፓትርያርኩ እንኳን ለትንሳዔ በዓል አደረሳችሁ ማለታቸው ምን ማለታቸው ነው? ወይስ የፓትርያርኩን የእንኳን አደረሳችሁ ንግግር ስፖንሰር ማድረግ ለሚፈልጉ ለማስታወቂያ የተቀነጨበ ይሆን? ፓትርያርኩ ምን ነካቸው? ምንስ አስቸኮላቸው? ፆም ቢፈታስ የመንጋው መሪ ወይስ እኔ የምጠየቀው? ለማንኛውም እንኳን አደረሳችሁ!
(አወቀ፣ ከናዝሬት)