የሳዑዲ ዓረቢያ መንግሥት ባወጣው የምሕረት አዋጅ መሠረት ተጠቅመው ወደ አገራቸው ለሚመለሱ ስደተኞች፣ አንዳንድ የመገልገያ ዕቃዎቻቸውን ከቀረጥ ነፃ ይዘው እንዲገቡ መንግሥት ፈቀደ::
የሳዑዲ ዓረቢያ መንግሥት በቅርቡ ያወጣው የምሕረት አዋጅ በአገሪቱ የሚገኙ ሕገወጥ ስደተኞች እስካሁን ያፈሩትን ንብረት ይዘው በሕጋዊ መንገድና አሻራ መስጠት ሳያስፈልጋቸው ወደየመጡበት አገር እንዲመለሱ የሚፈቅድ ሲሆን፣ የሦስት ወራት ቀነ ገደብ አስቀምጧል::
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በቅርቡ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ መሠረት፣ በአካባቢው የሚገኙ በመቶ ሺሕ የሚቆጠሩ በሕገወጥ መንገድ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ወደ አገራቸው እንዲመለሱ የተለያ ጥረቶች እያደረገ ነው:: በዚህም የጉዞ ሰነዶቻቸውን እንዲያገኙ የተለያዩ ጽሕፈት ቤቶችን ከፍቶ እየተንቀሳቀሰ ቢሆንም፣ እስካሁን በቂ ቁጥር ያላቸው ስደተኞች የምሕረት አዋጁን እየተጠቀሙ ባለመሆናቸው ሥጋት እንደገባው መዘገባችን ይታወሳል::
የኢትዮጵያ መንግሥት ተመላሾቹ ያለምንም መንገላታት ወደ አገራቸው እንዲመለሱ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሥር ግብረ ኃይል በማቋቋም እየተንቀሳቀሰ ሲሆን፣ ስደተኞቹ ለረጅም ጊዜያት ይኖሩበት ከነበረው ከሳዑዲ ዓረቢያ ሲመለሱ 21 ዓይነት የግል መገልገያ ቁሳቁሶች ከታክስ ነፃ ይዘው እንዲገቡ ፈቅዷል:: ከታክስ ነፃ እንዲገቡ የተፈቀደላቸው ቁሳቁሶች ዝርዝር፣ ጅዳና ሪያድ በሚገኙ የኤምባሲው ቢሮዎች ማግኘት እንደሚችሉ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል::
ከሁለቱ ቢሮዎች ውጪ ተመሳሳይ የጉዞ ሰነድ አገልግሎት የሚሰጡ ማዕከላት መቋቋማቸው ተገልጿል:: ከእነዚህም ውስጥ በሪያድ ሚሲዮን ደማም፣ ቡረይዳና ዋዲ ደዋስር (ሪያድ አካባቢ)፣ እንዲሁም ደግሞ በጅዳ ሚሲዮን በመካ፣ ከሚስሸጥ፣ ጄዛንና መዲና የሚገኙት ተጠቃሽ ናቸው::