Friday, December 1, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

ክቡር ሚኒስትሩ ወደ ሥራ ለመሄድ እየተዘገጃጁ ከባለቤታቸው ጋር እየተነጋገሩ ነው

  • የተከበሩ ሚኒስትር በዓል እየተቃረበ እኮ ነው፡፡
  • ያው እንደተመለደው እናከብረዋለን፡፡
  • እንደተለመደው ምን ማለት ነው?
  • ፋሲካ አይደል?
  • እና?
  • ዶሮና በግ ይበቃናል፡፡
  • ይበቃናል?
  • ምነው?
  • የደላቸውማ በምን እንደሚያከብሩ ልንገርህ?
  • እሺ፡፡
  • የደላቸውማ ሙሉ የቤት ዕቃ ይለውጣሉ፡፡
  • እ. . .
  • አዲሱን ኤልጂ ቲቪ ያስገባሉ፡፡
  • እ. . .
  • ከጎልድ እስከ ብሉ ሌብል ድረስ በካርቶኖች ያስመጣሉ፡፡
  • ህም. . .
  • የዶሮውን ብዛት ትተህ ቢያንስ ሦስት የፍየል ሙክቶች ያርዳሉ፡፡
  • ሦስት የፍየል ሙክቶች?
  • አዎ!
  • ምን ሊያደርጉላቸው?
  • ወይ የእኛ ሞኝ?
  • አልገባኝም፡፡
  • አንዱ ፍየል ቁርጥ፣ ሁለተኛው ጥብስ፣ ሦስተኛው ደግሞ ወጥ ይሆናል፡፡
  • ይህንን ሁሉ ፍየል ማን ነው የሚበላው?
  • ዘመድ አዝማድና ወዳጆቻችን፡፡
  • እሺ ለዚህ ሁሉ ወጪው ከየት ይመጣል?
  • ወይ አንተ ሞኝ?
  • እንዴት?
  • ሌሎቹ ከየት እንደሚያመጡት አታውቅም?
  • ከየት ያመጡታል?
  • በስጦታ ይመጣላቸዋል፡፡
  • እኔ የሚሰጠኝ ከሌለስ?
  • ሥልጣንህን ተጠቀም፡፡
  • ምን ማለትሽ ነው?
  • ጓደኛህ ቤት እኮ ሄጄ ስንቱን ጉድ አየሁ?
  • ምን አየሽ?
  • አንድ የጭነት ተሽከርካሪ የማይበቃው የስጦታ ክምር ነዋ፡፡
  • እነ ማን ናቸው የሚሰጡት?
  • ተጠቅመው የሚጠቅሙ ልማታዊ ባለሀብቶች፡፡
  • ሥልጣኔን ለዚህ እንድጠቀም ነው የምትመክሪኝ?
  • ከዚያም በላይ ነው፡፡
  • ለምሳሌ?
  • በትንሹ የራሳችን የመኖሪያ ቪላ ከነመዋኛው፣ የምናከራያቸው ሕንፃዎች፣ የኮንስትራክሽን ማሽኖችና ተሽከርካሪዎች ያስፈልጉናል፡፡
  • እነዚህ ሁሉ ከየት ይገኛሉ?
  • ሌሎቹ ተሿሚዎች ከየት እንደሚያመጧቸው አታውቅም?
  • ከየት ያመጣሉ?
  • ሥልጣናቸውን በአግባቡ ተጠቅመውበት ነዋ፡፡
  • ይኼማ ሥልጣንን ያላግባብ መጠቀም ነው የሚባለው?
  • የአንተ ሞኝነት እያበሳጨኝ ነው፡፡
  • ቀዝቃዛ ውኃ ጠጪበት፡፡
  • ውኃ ከምጠጣ አንተን ጥፊ ባልስህ ይሻለኛል፡፡
  • ለምን ትናደጃለሽ?
  • ኑሮህና ሥልጣንህ አይመጣጠኑም፡፡
  • አንቺ ሴትዮ ምን አድርግ ነው የምትይኝ፡፡
  • ኑሮህ ሥልጣንህን እንዲመስል ተጠቀምበት፡፡
  • የምትይው ከእኔ መርህ ጋር አይሄድም፡፡
  • የአንተ አጉል የድርቅና መርህ ይቀየራል፡፡
  • በምንድነው የሚቀየረው?
  • በሰጥቶ መቀበል መርህ፡፡
  • ወይ ዕዳ?

[ክቡር ሚኒስትሩን ሾፌራቸው ወደ ቢሮአቸው እየወሰዳቸው ነው]

  • ምነው ዛሬ ሙዚቃ አልከፈትክም?
  • ክቡር ሚኒስትር ደብሮኛል፡፡
  • ለምን ደበረህ?
  • በዓሉ ቀዘቀዘብኝ፡፡
  • ያለህን አብቃቅተህ በዓሉን ማሳለፍ ትችላለህ፡፡
  • የድሮ ክቡር ሚኒስትር ሾፌር እኮ የነገረኝ ሌላ ነው፡፡
  • ምን አለህ?
  • በዓል ሲመጣ በሽበሽ ነው ነበር ያለኝ፡፡
  • የአሁኑ ምን የተለየ ነገር አለው?
  • ድርቅ ነው፡፡
  • የምን ድርቅ?
  • ሸጎጥ የሚያደርግ የለ፣ በግል የለ፣ ውስኪ የለ፣ ብቻ ምን አለፋዎት ደርቄያለሁ፡፡
  • ማን ነው ለሾፌር ይህንን ሁሉ የሚያደርገው?
  • ባለጉዳዮች ናቸዋ፡፡
  • የማን ባለጉዳዮች?
  • የክቡር ሚኒስትሩ፡፡
  • ምን ለማግኘት?
  • ለመጠቃቀም፡፡
  • በምን ምክንያት?
  • የሆነ ፕሮጀክት ይሰጣቸዋል በምትኩ ወረታውን ይከፍላሉ፡፡
  • ለማን?
  • ለክቡር ሚኒስትሩ፡፡
  • አንተ ምን ቤት ነህ ታዲያ?
  • የመረጃ ልውውጡ ከሾፌር እኮ ነው የሚጀምረው፡፡
  • እና ምን ይሁን ነው የምትለው?
  • ክቡር ሚኒስትር ለስለስ ይበሉ፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • ትንሽ ደረቅ ስለሚሉ ሰው ተቸግሯል፡፡
  • በእናንተ ቤት ኃላፊነትን መወጣት የሚተረጎመው እንዲህ ነው?
  • አይ ክቡር ሚኒስትር?
  • ምነው?
  • ዕድሜ ጠገቡን ተረት ረሱት መሰለኝ?
  • ምንድነው የሚባለው?
  • ‹‹ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል›› ነዋ፡፡
  • በአንተ ቤት ተርተህ ሞተሃል፡፡
  • እኔማ በበዓሉ ፈንጥዤ ብሞት ነበር ደስ የሚለኝ፡፡
  • ሆሆ. . .

[ክቡር ሚኒስትሩ ቢሮአቸው ሲገቡ ጸሐፊያቸው ተከትላቸው ገባች]

  • ክቡር ሚኒስትር የእንኳን አደረስዎት ፖስት ካርዶች ይቀበሉኝ፡፡
  • ማን ነው የላከልኝ፡፡
  • ከመንግሥታዊ መሥሪያ ቤቶችና ከኤምባሲዎች የተላኩ ናቸው፡፡
  • ጥሩ፡፡
  • በጣም ያሳዝናል፡፡
  • ምን ተፈጠረ?
  • የአንድ ክቡር ሚኒስትር ቢሮ የፖስት ካርድ መጋዘን በመሆኑ ነዋ፡፡
  • ምን?
  • የድሮ ክቡር ሚኒስትር የሚመጡላቸው የበዓል ስጦታዎች እኔ ነኝ ያለ አይሱዙ አይበቃቸውም ነበር፡፡
  • ማን ነገረሽ?
  • ጸሐፊያቸው፡፡
  • አመንሻት?
  • ምን ማመን ብቻ? ኑሮዋ እኮ ያስታውቃል፡፡
  • እንዴት?
  • እሷን ጸሐፊ ከማለት ሚኒስትር ማለት ይቀላል፡፡
  • የእውነት?
  • ለበዓል ከምታገኛቸው ስጦታዎች በተጨማሪ የራሷ ቤት፣ መኪና፣ ቡቲክና የሽቶ መሸጫዎች አሉዋት፡፡
  • ምን ሠርታ አገኘች?
  • የክቡር ሚኒስትሩ ቀኝ እጅ ነበረች፡፡
  • ይገርማል፡፡
  • እርስዎ ነዎት የሚገርሙት፡፡
  • ምኔ ነው የሚገርመው?
  • ወይ አይበሉ ወይ አያስበሉ፡፡
  • አንቺ ምን አልሽ?
  • ሁሉም ሰው የሚለውን ነው ያልኩት፡፡
  • እንዲህ በቀላሉ ሀብት ማፍራት ይቻላል እንዴ?
  • ሰው የሚነግርዎትን ቢሰሙ ይሻላል፡፡
  • ምንድነው የሚነገረኝ?
  • አዋጭ የሆኑ ምክረ ሐሳቦች፡፡
  • ምንድናቸው እነሱ?
  • መደራደርና ጥቅምን መተሳሰብ፡፡
  • ምን?
  • በድርድር ይሰጣሉ ጥቅምዎትንም ያገኛሉ፡፡
  • ከዚያስ?
  • ሁሉም በየደረጃው ተጠቃሚ ይሆናል፡፡
  • ይኼ ምን የሚሉት መርህ ነው?
  • የጋራ ተጠቃሚነት መርህ ይባላል፡፡
  • እቺን ይወዳል?

[ክቡር ሚኒስትሩ አማካሪያቸውን አስጠርተው እየተነጋገሩ ነው]

  •  ሪፖርቱን ጨረስክ?
  •  አዎን ክቡር ሚኒስትር፡፡
  •  ሁሉም ነገር ተሟልቷል?
  •  አልተሟላም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  •  ለምን?
  •  ትንሽ ሙዴ ልክ አይደለም፡፡
  •  ምን ሆነሃል?
  •  በዓሉ ሲቃረብ ከፍቶኛል፡፡
  •  ለምን?
  •  የአሁኑ በዓል እንደጠበቅኩት አልሆነም፡፡
  •  ምንድነው የጠበቅከው?
  •  አለ አይደል. . .
  •  ምን?
  •  ያንን ፕሮጀክት ለሰዎቹ ብንሰጣቸው እኮ ደህና እንዘጋ ነበር፡፡
  •  ያለ ጨረታ?
  •  በድርድር፡፡
  •  ስማ ሕግ ጣስ ነው የምትለኝ?
  •  ድርድር ሕግ መጣስ ሆነ እንዴ?
  •  እንዴት ነው የምንደራደረው?
  •  ኮሚሽናችንን ይዘን ነዋ፡፡
  •  የምን ኮሚሽን?
  •  የተለመደ አሠራር ነው፡፡
  •  ኮሚሽን መቀበል?
  •  አዎ፡፡
  •  እንዴት እባክህ?
  •  የአገር አሠራር ነው እያልኩኝ ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  •  ለምሳሌ?
  •  የቱን ነግሬ የቱን ልተው?
  •  ማለት?
  •  ኧረ ክቡር ሚኒስትር ነቃ ይበሉ?
  •  ምን ለመሆን?
  •  ይኼኔ እኮ በስጦታና በቼክ ተንበሽብሸን ነበር፡፡
  •  ምን አድርግ ነው የምትለኝ?
  •  በዓሉን እናድምቀው፡፡
  •  ከዚያስ?
  •  በአካባቢያችን ያሉት ሁሉ በደስታ ይጥለቅለቁ፡፡
  •  ደስታ የሚገኘው በዚህ መንገድ ነው?
  •  ክቡር ሚኒስትር እኔ ማዛጋት ሰልችቶኛል፡፡
  •  ምን ትሆን ታዲያ?
  •  ሪፖርቱን አዘግይተን ፕሮጀክቱን በአስቸኳይ እንስጥ ክቡር ሚኒስትር?
  •  ለማን?
  •  አሰፍስፈው ከሚጠበቁት መካከል የተሻለ ይዞ ለቀረበ ይሰጥ፡፡
  •  እንዲህ ነው የምታማክረኝ?
  •  የሚበጀው ይኼው ነው ክቡርነትዎ፡፡
  •  ባለቤቴ፣ ሾፌሬ፣ ጸሐፊዬና አማካሪዬ አንድ ዓይነት ነገር ነው የምታስቡት?
  •  በጭራሽ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  •  ከቤት ጀምሮ አንድ ዓይነት ነገር ነው የምሰማው፡፡
  •  ሐሳቡ አንድ ቢሆንም አቅጣጫው የተለያየ ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  •  እንዴት?
  •  እርስዎ እንደ እግዜአብሔር፣ ባለቤትዎ እንደ ቄሳር፣ እኛ ደግሞ እንደ ዜጋ የሚገባንን ነው መጠየቅ ያለብን ክቡር ሚኒስትር?
  •  ምን ማለት ነው?
  •   በጋራ ተጠቃሚነት ላይ ያተኮረ የሀብት ክፍፍል ለማለት ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  •  እና የሚገኘውን ኮሚሽን ደልድለሃል ማለት ነው?
  •  የመደልደሉ ሥልጣን ባይኖረኝም አሥልቼዋለሁ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  •  ሥሌትህ ምን ይላል?
  •  40/60 ክቡር ሚኒስትር፡፡
  •  ይኼ 40/60 እንዲህ መቀለጃ ይሁን፡፡
  •  የሁሉም ዓይን እዚያ ላይ ነው እኮ ያለው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  •  የ40/60 ሥሌት ይገለጽልኝ እስቲ፡፡
  •  እኛ 40 በመቶውን ስንቧጨቅ እርስዎ ከነቤተሰብዎ 60 በመቶውን ክቡር ሚኒስትር፡፡
  •  እንዴት ነው እባክህ የተሠላው?
  •  በዓሉን ታሳቢ በማድረግ ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  •  አሁን ይኼንን ሰው ቢሰማ ምን ይላል?
  •  ‹‹ጉድ አንድ ሰሞን ነው›› ሲባል አልሰሙም ክቡር ሚኒስትር?
  •  ወይ ጣጣ!

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

የመቃወም ነፃነት ውዝግብ በኢትዮጵያ

ስሟ እንዳይገለጽ የጠየቀችው በአዲስ አበባ ከተማ በተለምዶ የሾላ አካባቢ...

የሲሚንቶን እጥረትና ችግር ታሪክ ለማድረግ የተጀመረው አጓጊ ጥረት

በኢትዮጵያ በገበያ ውስጥ ለዓመታት ከፍተኛ ተግዳሮት በመሆን ከሚጠቀሱ ምርቶች...

የብሔር ፖለቲካው ጡዘት የእርስ በርስ ግጭት እንዳያባብስ ጥንቃቄ ይደረግ

በያሲን ባህሩ በሪፖርተር የኅዳር 9 ቀን 2016 ዓ.ም. ዕትም “እኔ...

ሀብቱንና ትርፉን እያሳደገ የቀጠለው አዋሽ ባንክ

አዋሽ ባንክ በአዲስ አበባ ከተማ አዲስ ዋና መሥሪያ ቤት...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ የሩብ ዓመት የሥራ አፈጻጸማቸውን ለተከበረው ምክር ቤት ካቀረቡ በኋላ ከምክር ቤቱ አባላት የሚነሱ ጥያቄዎችን እየተቀበሉ ማብራሪያ በመስጠት ላይ ናቸው]

ክቡር ሚኒስትር መንግሥት ለሕዝብ ይፋ ያደረገው ነገር ከምን እንደደረሰ ቢያብራሩልን? ምንድነው ይፋ ያደረገው? ጥያቄውን ትንሽ ቢያብራሩት? ከአራት ዓመት በፊት በኦጋዴን አካባቢ ነዳጅ መገኘቱን ለሕዝብ በቴሌቪዥን አብስሮ...

[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ የካቢኔና የማክሮ ኢኮኖሚ ኮሚቴ አባል የሆኑ ከፍተኛ አመራር የሚያቀርቡትን ቅሬታ እያደመጡ ነው] 

ክቡር ሚኒስትር እየሆነ ያለው ነገር በእጅጉ ስላሳሰበኝ ነው በአካል አግኝቼ ላነጋግርዎት የፈለግኩት። ጥሩ አደረግህ፣ ምን አሳሳቢ ነገር ገጥሞህ ነው? ክቡር ሚኒስትር ተወያይተንና ተግባብተን ያስቀመጥናቸው አቅጣጫዎች፣ በተለይም...

[ጉባዔው በወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮች ላይ ክቡር ሚኒስትሩን ለመጠየቅና ምላሽና ማብራሪያቸውን ለማድመጥ ተሰብስቧል። የጉባዔው አባላትም ማብራሪያ የሚሹ ጥያቄዎቻቸውን ለክቡር ሚኒስትሩ እያቀረቡ ነው]

ክቡር ሚኒስትር፣ ይህ ጉባዔ ለሚያነሳቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ለመስጠት በመካከላችን ስለተገኙ አመሰግናለሁ። ክቡር ሚኒስትር፣ ኢትዮጵያ ባለፈው ዓመት የብሪክስ አባል እንድትሆን የሰጡት በሳል አመራር የሚደነቅ ነው። አገራችን...