- Advertisement -

ክቡር ሚኒስትሩ ከሚስታቸው ጋር በስልክ እያወሩ ነው

[ክቡር ሚኒስትሩ ከቤት ሊወጡ ሲሉ ከልጃቸው ጋር እያወሩ ነው]

  • አንተ ትምህርት ቤት አትሄድም እንዴ?
  • ሙድ የለኝም ባክህ ዳዲ፡፡
  • ምንድነው ያልከው?
  • ሙዴ ተከንቷል አልኩህ እኮ ዳዲ፡፡
  • ምንድነው የምታወራው?
  • ምነው ዳዲ?
  • ሙድ መከነት ምንድነው?
  • የአራዳ ቋንቋ አታርፍም አይደል ዳዲ?
  • ስማ አንተ ልጅ ከፀረ ልማት ኃይሎች ጋር መዋልህን አልተውክም ማለት ነው?
  • ጀመረህ ደግሞ ዳዲ?
  • ትምህርት ተጀምሯል አይደል እንዴ?
  • በቃ ደብሮኛል ዳዲ፡፡
  • ምን ሆነህ ነው የደበረህ?
  • ሁሉም ነገር ነዋ ዳዲ፡፡
  • ለትምህርትህ የሚያስፈልገው ነገር ሁሉ ተደርጎልሃል አይደል እንዴ?
  • አልተደረገልኝም ዳዲ፡፡
  • ምን ጎደለህ ደግሞ?
  • ብዙ ነገር ዳዲ፡፡
  • እስቲ አንዱን ንገረኝ?
  • በጣም የሚያሳፍር ነገር ነው የተደረገብኝ፡፡
  • እኮ ምን?
  • ክረምቱን እንዴት እንዳሳለፍኩት ረሳኸው?
  • ክረምቱ ምን ሆነ?
  • ያለፈውን ክረምት አስታውሰው እስኪ?
  • ያለፈው ክረምት ምን ሆነ?
  • ቫኬሽን የት ነበር የላከኝ?
  • አውሮፓ ነበር አይደል የሄድከው?
  • ምን ቫኬሽን ብቻ ሾፒንግ የት ነበር የላከኝ?
  • ዱባይ ነዋ፡፡
  • እሺ በዚህ ዓመት ቫኬሽን የት ነበረ?
  • ገጠር ነዋ፣ አገርህንም ማወቅ አለብህ?
  • ሾፒንግስ የት ነበር?
  • ቦሌ ነዋ ያደረከው፣ ምን ችግር አለው?
  • እኔ ይኼ መመርያ ምናምን የተባለው ነገር ከወጣ በኋላ ተቀያይረህብኛል፡፡
  • ምን ሆኜ ነው የተቀያየርኩት?
  • ባለፈው ዓመት ትምህርት ቤት በምንድን ነበር የምሄደው?
  • በምንድን ነበር የምትሄደው?
  • ሰኞ በነጭ ቪ8 ከሄድኩ፣ ማክሰኞ በጥቁሩ ነበር የምሄደው፡፡
  • እሺ፡፡
  • ረቡዕ በሲልቨር ቪ8 ከሄድኩ፣ ሐሙስ በመርሴዲስ ነበር፡፡
  • እሺ…
  • ዓርብ ደግሞ በሀመሩ ነበር፡፡
  • አሁንስ?
  • አሁንማ ከሰኞ እስከ ዓርብ በስኩል ባስ ነው የምመላለሰው፡፡
  • ለመሆኑ አንተ ተማሪ ነህ የመኪና ነጋዴ?
  • አንተው እኮ ነው ያስለመድከኝ?
  • ምን ላድርግህ ታዲያ?
  • እኔ እኮ ሳይኮሎጂካሊም ተጎዳሁ፤ እንዴት ብዬ ነው ከሌሎቹ ተማሪዎች ጋር አብሬ የምሄደው?
  • ከሌሎቹ ተማሪዎች ጋር አብረህ ብትሄድ ምን ችግር አለው?
  • እኔ የሚኒስትር ልጅ አይደለሁም እንዴ?
  • እኔ እኮ ሚኒስትር የሆንኩት ሕዝብ ለማገልገል ነው፡፡
  • ሕዝብ አገልግለህ ነው ፎቅ የሠራኸው?
  • እ…
  • ይኼን ሁሉ ቤት የሠራኸው ሕዝብ በማገልገል ነው?
  • ምን አልክ አንተ?
  • ለነገሩ አንተ ሕዝብ ማገልገል ሳይሆን የምትወደው…
  • እ…
  • በሕዝብ መገልገል ነው!

 

[ክቡር ሚኒስትሩ ከሚስታቸው ጋር በስልክ እያወሩ ነው]

  • በቃ እኔ እኮ ታገትኩ?
  • ቤት ውስጥ አሸባሪዎች ገቡ እንዴ?
  • ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ ማድረግ እኮ አልቻልኩም?
  • የምን እንቅስቃሴ ነው?
  • ስማ በዓል በመጣ ቁጥር የምሠራውን ሥራ ረሳኸው እንዴ?
  • ሴትዮ አሁን ጊዜው ጥሩ አይደለም፡፡
  • እና እጅና እግሬን አጣምሬ ቁጭ ልበል?
  • እንደዚያማ መሆን የለበትም፡፡
  • ለምንድን ነው ግራ የምታጋባኝ?
  • ግራ መጋባትን ምን አመጣው?
  • ልንቀሳቀስ ስልህ ጊዜው ጥሩ አይደለም ትለኛለህ፤ ልቀመጥ ስልህ ደግሞ እንደዛ መሆን የለበትም ትለኛለህ፡፡
  • እንደዚያ ያልኩሽ እኮ ዓይኖች ሁሉ እኛ ላይ ስለሆኑ ነው፡፡
  • ምን ተሻለ ታዲያ?
  • መጠንቀቅ አለብን፡፡
  • ታዲያ ተጠንቅቀን መሥራት አንችልም?
  • ተጠንቅቀን መሥራት ማለት ምን ማለት ነው?
  • የማያስታውቅ ሥራ መሥራት ነዋ፡፡
  • ስሚ እንደ እኔ እንደ እኔ አንቺ ዝም ብለሽ ብትሄጂ ይሻላል፡፡
  • የት?
  • ዱባይም ምናምን ቢሆን ነዋ፡፡
  • ስማ ሰውዬ እኔ ልጆቼን ጥዬ የትም መሄድ አልፈልግም፡፡
  • እሱን እንኳ ተይው፡፡
  • እንዴት ማለት?
  • ቂሊንጦ ስትገቢ ልጆችሽን ጥለሽ አይደል እንዴ?
  • እውነቱን እናውራ ከተባለማ ከእኔ ይልቅ አንተ ነህ ለቂሊንጦ ቅርብ፡፡
  • አብዛኛው ነገር በአንቺ ስም መሆኑን ረሳሽው እንዴ?
  • ታዲያ እኔ ባለሥልጣን አይደለሁ፤ ግፋ ቢል ንብረቴን ያግዳሉ እንጂ አያስሩኝም፡፡ ባለሥልጣን ስላልሆንኩ፣ ቢዝነስ መሥራት መብቴ መስሎኝ?
  • ሙስና የግል ሴክተሩም እንደሚነካ መቼም ታውቂያለሽ፡፡
  • እኔን አይመለከተኝም አልኩህ፡፡
  • አሁን ደግሞ ዋና ትኩረትቸው በባለሥልጣናት ዙሪያ ያሉ ሰዎች ላይ ነው፡፡
  • እያስፈራራኸኝ ነው?
  • ለማንኛውም ወደ ዱባይ ብትሄጂ ጥሩ ነው፡፡
  • ስማ እኔ የመጣብኝን እቀበላለሁ፡፡
  • እስርም ቢሆን?
  • ለምን እታሰራለሁ?
  • ያልተገባ ሀብት አካብተሻል ተብለሽ ነዋ፡፡
  • በቃ እንደሌሎቹ በስሜ ያለን ሀብት ሸጣችሁ ውሰዱት ብሎ መገላገል ነዋ፡፡
  • አሁን አንቺን በዛ ይምሩሻል ብለሽ ነው፡፡
  • እኔ የኢትዮጵያን ሕዝብ ሳውቀው ምስኪንና መሃሪ ሕዝብ ነው፡፡
  • ለዚያ ነው እንደዚህ ያለ ይሉንታ የምትበይው?
  • አንተም ከመቼ ጀምሮ ነው ለሕዝቡ ተሟጋች የሆንከው?
  • ሕዝብ ከተነሳብሽ ጥሩ አይደለም ብዬ ነው፡፡
  • ምን አድርጊ እያልከኝ ነው?
  • በቃ ለጊዜው ከአገር ውጪ፡፡
  • ከዱባይ ግን ለምን ወደ ቻይና አልሄድም?
  • ለምን?
  • በዛው ዕቃ አስጭናለኋ፡፡
  • ምን ዓይነት ዕቃ?
  • በቃ ብዙ ዓይን ውስጥ የማይከት ዕቃ፡፡
  • እኮ ምንድነው?
  • ለምሳሌ ርችት፡፡
  • ርችት ምን ያደርግልሻል?
  • በቃ ሰው በየልደቱም፣ በየበዓሉም ይተኩሰዋላ፡፡
  • ጥሩ ዕቃ አይመስለኝም፡፡
  • ለምን?
  • ሰው እንደድሮው ለርችት ቦታ መስጠት አቁሟል፡፡
  • ለምን ተብሎ?
  • መንግሥት በየቦታው እንደ ርችት የሚያፈነዳው ነገር ስላለ፡፡
  • ምንድነው እሱ?
  • ትራንስፎርመር!

 

[ለክቡር ሚኒስትሩ አንድ ዳያስፖራ ወዳጃቸው ይደውልላቸዋል]

  • ሄሎ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ማን ልበል?
  • ወዳጅዎት ነኝ ከአሜሪካ፡፡
  • ዛሬ ከየት ተገኘህ?
  • ሁሌም ሲናፍቁኝ እኮ እደውላለሁ፡፡
  • ለመስቀል በግ መግዣ ልከህልኝ ነው?
  • ባለሥልጣን ስጦታ መቀበል ይችላል እንዴ?
  • ምን ችግር አለው?
  • ያው እዚህ አሜሪካ ባለሥልጣናት ስጦታ መቀበል ስለማይችሉ ነው፡፡
  • አሁን በግ ስጦታ መሆኗ ነው?
  • ለነገሩ እርስዎ ፎቅ ለምደው በግ ምንም ናት፡፡
  • ስማ እርሱ ድሮ ቀረ፡፡
  • እንዴት?
  • አሁን እንኳን ፎቅ በግ የሚሰጥ የለም፡፡
  • ዛሬ እንኳን የደወልኩት የዚህች አገር ጉድ ማለቂያው መቼ ይሆን ለማለት ነው፡፡
  • እንዴት ማለት?
  • ክቡር ሚኒስትር የሰማሁትን ነገር ከእርስዎ ለማጣራት ነው የደወልኩት፡፡
  • እኮ ምን ሰምተህ ነው?
  • ሚዲያ ላይ የሚወራው እውነት ነው?
  • ስለግጭቱ ነው?
  • እሱማ እውነት መሆኑን እናንተም ተናግራችኋል፡፡
  • ታዲያ ምን ሰምተህ ነው?
  • ስለስኳር የሚወራው ወሬ፡፡
  • ምን አወሩ ደግሞ?
  • ኢትዮጵያ ወደ ጎረቤት አገር ስኳር ኤክስፖርት አድርጋ ነበር አሉ፡፡
  • ታዲያ ኤክስፖርት ማድረግ ምን ችግር አለው?
  • የራሷ አሮባት የጎረቤቷን ታማስላለች አሉ፡፡
  • ምን ለማለት ፈልገህ ነው?
  • አገሪቷ ውስጥ ስኳር የሚባል ነገር ጠፍቶ በብቸኝነት የሚገኘው ስኳር በሽታ ነው ይባላል፡፡
  • ስማ አሁንም ከእነዚያ ፀረ ልማት ኃይሎች ጋር ነው አይደል የምትውለው?
  • እኔ የምለው ክቡር ሚኒስትር፣ ኢምፖርት የተደረገውን ነው መልሳችሁ ኤክስፖርት የምታደርጉት?
  • ኢምፖርት ኤክስፖርት ሲባል አልሰማህም?
  • ኪኪኪ…
  • ምን ያስቅሃል?
  • ለነገሩ አገሪቷን በግምት እንደምትመሯት ይታወቃል፡፡
  • ምን?
  • አገሪቷ በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ሆና እናንተ ለጎረቤት አገሮች ኃይል ትልካላችሁ፡፡
  • ሰውዬ ከአገሪቷ የኤክስፖርት ፖሊሲ ጋር ችግር አለብህ?
  • እውነት አንዳንዴ ሳስባችሁ እንኳን አገር ቤተሰብም በቅጡ መምራት የምትችሉ አይመስለኝም፡፡
  • ለመሳደብ ነው እንዴ የደወልከው?
  • ለነገሩ የደወልኩት ስኳሩ ጠረፍ ላይ መያዙ አስገርሞኝ ነው፡፡
  • ምኑ ነው የሚያስገርመው?
  • ስኳሩን አስይዛችሁ…
  • እ…
  • የላሱትን ማስመለጣችሁ!

 

- Advertisement -

[ክቡር ሚኒስትሩ ማታ ቤታቸው ደመራ እየተበራ አማካሪያቸው መጣ]

  • እንዴት መጣህ አንተ?
  • ክቡር ሚኒስትር ደመራ እኮ ከዓመት ዓመት እርስዎ ቤት ነው የማበራው?
  • ዘንድሮ መቼ ጠራሁህ ታዲያ?
  • ልማዴን ለማድረስ ነበር፣ ግን አንድ ነገር ግር ብሎኛል፡፡
  • ምንድነው እሱ?
  • በር ላይ ብዙ መኪናም የለም፤ በዛ ላይ እንደ ድሮው ሰውም የለም፤ እርስዎ ፈቃድ ያስፈልግዎታል እንዴ?
  • የምን ፈቃድ?
  • አይ አሁን አሁን ለአልበም ምርቃት፣ ለሠልፍ ምናምን ፈቃድ ስለሚያስፈልግ፣ እርስዎ ቤት ያነሰው ስላላስፈቀዱ ነው ብዬ ነው፡፡
  • ስማ እንደ ድሮው ድግስ መደገስ እንደማልችል ታውቃለህ?
  • ለነገሩ ሰው እኮ ክቡር ሚኒስትሩ ደመራ የሚያበሩት እስር ቤት ነው እያለ ነው የሚያወራው፡፡
  • ታዲያ አንተ እዚህ ምን ልታደርግ መጣህ?
  • ልተነብይ ነዋ፡፡
  • ምንድነው የምትተነብየው?
  • ወደ ምሥራቅ ከወደቀ ቂሊንጦ፣ ወደ ምዕራብ ከሆነ ደዴሳ፣ ወደ ሰሜን ከሆነ ደግሞ ሸዋሮቢት፣ ወደ ደቡብ ከሆነ ደግሞ ዝዋይ ነው የሚገቡት የሚለውን ነዋ፡፡
  • እኔ ጠፋሁ?
  • የሚሻለው መፀለይ ነው፡፡
  • ለምኑ?
  • ቅርቡ እንዲደርስዎት!

 

[ደመራው ወደ ምሥራቅ ወደቀ]

  • በእውነት ክቡር ሚኒስትር ፀሎትዎ ተሰምቷል፡፡
  • እንዴት?
  • የወደቀው ወዴት እንደሆነ አዩት?
  • ወዴት ነው?
  • ወደ ቂሊንጦ!
- Advertisement -

በማህበራዊ ሚዲያዎች ይከታተሉን

ከ ተመሳሳይ አምዶች

[ክቡር ሚኒስትሩ የካቢኔ አባል የሆነ አንድ የተቃዋሚ ፓርቲ ተወካይ ስልክ ደውሎላቸው ሰሞኑን በተካሄደው ድርጅታዊ ጉባዔ ዙሪያ እያወሩ ነው]

ሰላም ክቡር ሚኒስትር፡፡ ሰላም ሰላም፣ እንዴት ነህ? ቢዘገይም እንኳን አደረስዎት ክቡር ሚኒስትር። ለምኑ? ለፓርቲዎ ሁለተኛ መደበኛ ጉባዔ እንኳን አደረስዎት ማለቴ ነው። ቆየ እኮ ከተጠናቀቀ? አስቀድሜ ቢዘገይም ያልኩት እኮ ለዚያ ነው...

[ክቡር ሚኒስትሩ የሹፌራቸው ሁኔታ አላምር ብሏቸው ምን እንደሆነ እየጠየቁት ነው]

ዛሬ አነዳድህ አላማረኝም። ምን አሉኝ ክቡር ሚኒስትር? አነዳድህ አላማረኝም! የሆንከው ነገር አለ? ጤንነት እየተሰማኝ አይደለም ክቡር ሚኒስትር። እስኪ ዳር ያዝና አቁመው። እሺ ክቡር ሚኒስትር ...ይኸው። ምን ሆነሃል? ምን ያልሆንኩት አለ ብለው...

[አንድ የመንግሥት ሹም በመንግሥት በኩል የተሰጠ መግለጫ እንዳለ ለማወቅ ክቡር ሚኒስትሩ ጋ ደወሉ]

ሰላም ክቡር ሚኒስትር? ሰላም… ሰላም... እንዴት አለህ? ወዳጆቻችን ደጋግመው እየደወሉ ነው። የትኞቹ? ሰሞኑን ብድር ያፀደቁልን። ምን ፈልገው ነው? ስምምነት ከደረስንበት ጉዳይ ጋር የሚጣረስ መረጃ በመንግሥት መሠራጨቱን ሰምተናል ነው የሚሉት። ምንን በተመለከተ...

[ክቡር ሚኒስትሩ የእጅ ስልካቸው እየጠራ ነው፣ ደዋዩ የታችኛው ክልል ገዥ ፓርቲ ሊቀመንበር መሆናቸው ተመልክተው አነሱት]

ሃሎ! እንዴት አሉ ክቡር ሚኒስትር። ደህና ነኝ። ክቡር ሚኒስትር ባለፈው ወደ አዲስ አበባ የመጣሁ ጊዜ በተመለከትኩት ሳላደንቅዎ ማለፌ ፀፅቶኝ ነው የደወልኩት። ምን አይተህ ነው? እያስገነቡት ያለውን የኮሪደር ልማት። ኦ...ዞር ዞር…...

[ክቡር ሚኒስትሩ ቀኑን ሙሉ ከዋሉበት የሥራ አስፈጻሚ ስብሰባ ወደ መኖሪያ ቤታቸው ተመልሰው ከባለቤታቸው ጋር እያወጉ ነው]

የምን ስብሰባ ላይ ዋልኩ ነበር ያልከኝ? የሥራ አስፈጻሚ። የምን ሥራ አስፈጻሚ? የገዥው ሥራ አስፈጻሚ። ምን ገጥሟችሁ ነው የተሰበሰባችሁት? ለመረጠን ሕዝብ ቃል የገባናቸውን ተግባራት አፈጻጸም የምንገመግምበት የተለመደ ስብሰባ ነው። የገባችሁት ቃል...

[ክቡር ሚኒስትሩ በመኖሪያ ቤታቸው ቁጭ ብለው ከባለቤታቸው ጋር እራት እየበሉ ሳለ የመሬት መንቀጥቀጥ ያሉበትን ሕንፃ አርገበገበው]

ይሄ ነገር አሳስቦኛል። የቱ? ንዝረቱ ነዋ? የምን ንዝረት? የመሬት መንቀጥቀጡ? እ... እሱን እንዴት? ከዚህ በላይ ጠንከር ብሎ ቢመጣ አዲስ አበባ ላይ ምን ሊፈጠር እንደሚችል ሳስበው ይዘገንነኛል። ምን ይፈጠራል? አብዛኛው ነዋሪ ኮንዶሚኒየም ላይ...

አዳዲስ ጽሁፎች

የጤናው ዘርፍ ባለፉት ስድሥት ወራት

የወባ በሽታ ከሰሃራ በታች በሚገኙ የአፍሪካ አገሮች ዋነኛ የጤናና የማኅበራዊ ቀውስ መንስዔ ነው፡፡ የዓለም ጤና ድርጅት እ.ኤ.አ. በ2024 ያወጣው መረጃም 263 ሚሊዮን ሰዎች የወባ...

የአዲስ አበባ የኮሪደር ልማት በባለሙያ ዓይን

(በጎ ጎኖችና እርምት የሚፈልጉ ጉዳዮች) በዮሐንስ መኮንን በጥር ወር 2016 ዓ.ም. የአዲስ አበባ ዋና ዋና ኮሪደሮችን በማዘመን ከተማዋን ለነዋሪዎቿና ለጎብኚዎቿ ምቹ ያደርጋታል የተባለ ፕሮጀክት በ43 ቢሊዮን...

በልዩነት ውስጥ ሆነንም እስኪ እንነጋገር

በገነት ዓለሙ ዴሞክራሲ መብቶችና ነፃነቶች የሚሠሩበት የሕዝብ አስተዳደር ነው፡፡ ሰብዓዊ መብቶችንና ነፃነቶችን መኗኗሪ ያደረገ ሥርዓት ነው፡፡ እነዚህ መሠረታዊ መብቶችና ነፃነቶች በተፈጥሮ የተገኙ፣ ሰው በመሆናችን ብቻ...

ለጤናማ የትራፊክ ፍሰትና ለመንገድ ደኅንነት ቅጣት መጣል ብቻውን መፍትሔ አይሆንም!

በአዲስ አበባ ከተማ ለተሽከርካሪዎች ምቹ የሆኑ መንገዶችን እየተመለከትን ነው፡፡ ከአዳዲሶቹ መንገዶች ባሻገር አንዳንድ ነባር መንገዶች የማስፋፊያ ሥራ ታክሎባቸው አገልግሎት ላይ ውለዋል፡፡ ከኮሪደር ልማቱ ጋር...

የግጭት አዙሪት ውስጥ ሆኖ የአፍሪካ ማዕከል መሆን ያዳግታል!

የአፍሪካ ኅብረት 38ኛው የመሪዎች ጉባዔ በአዲስ አበባ ሲካሄድ ብዙ ትዝ የሚሉ ጉዳዮች አሉ፡፡ እጅግ በጣም አሰልቺ፣ ውጣ ውረድ የበዛበትና ታላቅ ተጋድሎ ተደርጎበት ከከፍተኛ ዲፕሎማሲያዊ...

አገሬ ምንተባልሽ – ልብ ያለው ልብ ይበል

በቶማስ በቀለ ይቺ አገራችን ብዙ ተብሎላታልም፣ ብዙ ተወርቶባታልም፣ አገሪቱ በቅኝ ያልተገዛች ብቸኛ አገር (ላይቤሪያን ጨምሮ) ከመሆኗ አኳያ የሚነገርላት ብዙ ጥሩና የሚገርሙ ነገሮች ያሉትን ያህል፣ ከረሃብ...
[the_ad id="124766"]

በማህበራዊ ሚዲያዎች ይከታተሉን