የፌዴራል መንግሥት ለወጣቶች የሥራ ዕድል ከበጀተው አሥር ቢሊዮን ብር ተዘዋዋሪ ፈንድ ተጠቃሚ እንዲሆኑ የ3.3 ሚሊዮን ሥራ አጥ ወጣቶች ምዝገባ ተካሄደ፡፡ ቤት ለቤት በአገር አቀፍ ደረጃ ወጣቶቹን መመዝገቡን፣ የወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር ይፋ አድርጓል፡፡ ሚኒስትሩ አቶ ርስቱ ይርዳው የስምንት ወራት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረቡበት ወቅት እንደተናገሩት፣ በአገር አቀፍ ደረጃ ሥራ ፈላጊ ወጣቶችን የመለየት ሥራ በየክልሉ የቤት ለቤት ቅስቀሳና ግብረ ኃይል በማደራጀት እየተከናወነ ነው፡፡ እስከ መጋቢት ወር 2009 ዓ.ም. ድረስ በተካሄደው ሥራ ፈላጊዎችን የመለየት ተግባር 3,337,983 ሥራ ፈላጊ ወጣቶች መመዝገባቸውን ሚኒስትሩ ገልጸዋል፡፡ ከተመዝጋቢዎቹ ውስጥም 80,552 ያህሉ የዩኒቨርሲቲ ምሩቆች ሲሆኑ፣ 211,788 የሚሆኑት ደግሞ ከቴክኒክና ሙያ ተቋማት የተመረቁ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡ ይሁን እንጂ የተጠቀሰው አጠቃላይ የሥራ ፈላጊዎች ቁጥር ላይ እርግጠኛ መሆን አልተቻለም፡፡ ‹‹ሥራ ፈላጊዎችን የመለየቱ ተግባር የተደራጀ የመረጃ ሥርዓት ባለመኖሩ ምክንያት በየጊዜው የቁጥር መለዋወጥና የጥራት ችግር እያጋጠመ በመሆኑ፣ በቀጣይነት ማጣራት የሚጠይቅ ነው፤›› ሲሉ ሚኒስትሩ አስረድተዋል፡፡ ሥራ ፈላጊ ወጣቶቹን ከመለየቱ ተግባር ጎን ለጎን የወጣቶች የልማትና የለውጥ ስትራቴጂ ሰነድ ተዘጋጅቶ በየደረጃው ለሚገኙ የመንግሥት አደረጃጀቶችና አመራሮች፣ እንዲሁም ለወጣት አደረጃጀቶች ሥልጠና ሲሰጥ መቆየቱን ጠቁመዋል፡፡ ይህንን ስትራቴጂ ሥራ ላይ ለማዋልም የተለያዩ የአሠራር ማዕቀፎች ማለትም የወጣቶች የልማት ቡድን አደረጃጀትና ሥምሪት ማኑዋል፣ የወጣቶችና የመንግሥት ፎረም ማደራጃ ማኑዋልና የወጣት አደረጃጀቶች ድጋፍ አሰጣጥ ሥርዓት ማኑዋል መዘጋጀታቸውን ሚኒስትሩ ጠቁመዋል፡፡ ‹‹የወጣቶች ጥያቄ የሥራ ዕድል ፈጠራ መሆኑ ቢታወቅም፣ በርካታ የተዛቡ አስተሳሰቦች በወጣቶችም ሆነ በየደረጃው በሚገኘው የአመራር ኃይላችን የሚታይ ነው፤›› ያሉት ሚኒስትሩ፣ ሥልጠናው ያስፈለገበት ምክንያትም ይህንን ችግር ለማረም መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ወጣቶቹ ሊሰማሩባቸው የሚገቡ የሥራ መስኮችን ለመለየት እንዲያስችል፣ የፌዴራል መንግሥት አስፈጻሚ ተቋማት የቢዝነስ ፕላን አዘጋጅተው ማቅረባቸውን ገልጸዋል፡፡ ወጣቶቹ ወደ ሥራ እንዲገቡ በመሬት አቅርቦት ረገድ የከተማ አስተዳደሮች በፍጥነት ዝግጅት እንዲያደርጉ እየተሠራ መሆኑን አክለዋል፡፡ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለፀደቀው የወጣቶች ተዘዋዋሪ ፈንድ በሥራ ፈጠራ መርሐ ግብሩ የሚታቀፉ ወጣቶች ዕድሜ ከ18 እስከ 34 ዓመት መሆን አለበት፡፡