የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ‹‹በካይ›› ያላቸውን ስስ ፌስታል የሚያመርቱ ሦስት የፕላስቲክ ፋብሪካዎች፣ ሐሙስ ሚያዝያ 5 ቀን 2009 ዓ.ም. ዘጋ፡፡ ለአንድ ፋብሪካ የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል፡፡
የተዘጉት ፋብሪካዎች የማምኮ ወረቀት ፋብሪካ እህት ኩባንያ ማምኮ ፕላስቲክ፣ የሸዋ ዳቦ እህት ኩባንያ ሸዋ ፕላስቲክና ፎም ፕላስቲክ ፋብሪካዎች ናቸው፡፡ ማስጠንቀቂያ የተሰጠው ደግሞ ደብሊውኤጂ ፕላስቲክ ፋብሪካ ነው፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ፀጋዬ ገብረ ማርያም ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ከ0.03 ሚሊ ሜትር ውፍረት በታች ፕላስቲክ ማምረት በአገሪቱ በሕግ የተከለከለ ነው፡፡
‹‹እነዚህ ሦስት ፋብሪካዎች ከዓመት በፊት ማስጠንቀቂያ ቢሰጣቸውም፣ ሊያስተካክሉ ስላልቻሉ እንዲታሸጉ ተወስኗል፤›› ሲሉ አቶ ፀጋዬ አረጋግጠዋል፡፡
ስስ ፌስታሎች በኢትዮጵያ ከፍተኛ ብክለት እየፈጠሩ መሆኑ በጥናት መረጋገጡን የጠቆሙት አቶ ፀጋዬ፣ በተለይ ስስ ፌስታሎች ከ100 ዓመት በላይ ሳይበሰብሱ የሚቆዩ በመሆናቸው በአካባቢ ላይ ተፅዕኖ ያሳድራሉ፡፡
‹‹ከብቶች እየተመገቧቸው ለሞትና ለበሽታ እየተዳረጉ ነው፡፡ ከዚያም አልፎ ለዕይታ እጅግ ደስ የማይል ሁኔታ ፈጥረዋል፤›› በማለት አቶ ፀጋዬ አስረድተዋል፡፡
ፋብሪካዎቹ ከተዘጉባቸው መካከል ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ አንድ ባለሀብት ቅሬታቸውን ገልጸዋል፡፡ የእሳቸው ፋብሪካ ምርታቸውን ወደ ውጭ የሚልኩ ኩባንያዎች በሚሰጧቸው መሥፈርት መሠረት የሚያመርት ነው፡፡ በዚህም ፋብሪካቸው ሊዘጋ አይገባም ብለዋል፡፡
ነገር ግን አቶ ፀጋዬ ሲመልሱ፣ ‹‹የአካባቢ ችግር ድንበር ተሻጋሪ ነው፡፡ እኛ አገር ውስጥ የሚመረት ምርት ድንበር ተሻግሮ እንዲበክል አይፈቀድም፤›› ብለዋል፡፡
ማስጠንቀቂያ የተሰጠው ኩባንያ በሁለት ሳምንት ጊዜ ውስጥ ምርቱን ካላስተካከለ፣ ዕጣ ፈንታው እስከ ወዲያኛው መዘጋት እንደሚሆን የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን አስታውቋል፡፡