የደቡብ ክልል ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን የክልሉ ቤቶች ልማት ኢንተርፕራይዝ የቀድሞ ዋና ሥራ አስኪያጅን ጨምሮ በ13 ኃላፊዎችና ነጋዴዎች ላይ በሙስና ወንጀል ክስ መሠረተ፡፡
የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ በሐዋሳ ከተማ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመሠረተው ክስ ተከሳሾቹ በዋና ወንጀል አድራጊነትና በልዩ ተካፋይነት በ2005 ዓ.ም. ሕገወጥ የግንባታ ዕቃዎች ግዥ በመፈጸም በአጠቃላይ 9,057,961.62 ብር በመንግሥት ላይ ጉዳት እንዲደርስ በማድረጋቸው፣ የመንግሥት ሥራን በማያመች አኳኋን በመምራት የሙስና ወንጀል መከሰሳቸውን አመልክቷል፡፡
ከተከሳሾቹ ውስጥ አምስተኛው ተከሳሽ የክልሉ የቤቶች ልማት ኢንተርፕራይዝ ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት፣ ባለፉት ሁለት ዓመታት በኮንስትራክሽን ሚኒስቴር ውስጥ በከፍተኛ ኃላፊነት ተመድበው እየሠሩ የቆዩት አቶ ጥላሁን ደነቀ ይገኙበታል፡፡
የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ በክሱ ያካተታቸው ተከሳሾች አቶ ገብረ እግዚአብሔር ንርኤ የኢንተርፕራይዙ የሳኒተሪ መሐንዲስ፣ አቶ አብዱራህማን ሲራጅ የግዥ ክፍል ኃላፊና የግዢ ሎጂስቲክስና ንብረት አስተዳደር ተወካይ፣ አቶ አየለ ሀሚጦ የኢንተርፕራይዙ የፋናንስ መምርያ ኃላፊና የሥራ አስኪያጅ ተወካይ፣ አቶ ጥላሁን ደነቀ የኢንተርፕራይዙ የቀድሞ ሥራ አስኪያጅ፣ አቶ ምትኩ ባዩ የኢንተርፕራይዙ መሐንዲስ፣ አቶ መስፍን ኃይለ ማርያም የኢንተርፕራይዙ መሐንዲስ፣ አቶ ቢኒያም ሙላቱ መሐንዲስ፣ አቶ ቢንያም ደምሴ መሐንዲስ፣ አቶ ስሻው አየለ የሮክ የግንባታ ዕቃዎች አቅራቢ ድርጀት ሥራ አስኪያጅ፣ ሰለሞን ቢረዳ የኬር የግንባታ ዕቃዎች አቅራቢ ድርጀት ሥራ አስኪያጅና አቶ መሰለ ጌታሁን የመሰለ ጌታሁን ጠቅላላ ንግድ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ባለቤት ናቸው፡፡
ዓቃቤ ሕግ ተከሳሾቹ በ1996 ዓ.ም. የወጣውን የወንጀል ሕግ አንቀጽ 32(1) 33 እና 441 (2) ላይ የተመለከተውን በመተላለፍ፣ የመንግሥት ሥራን በማያመች አኳኋን በመምራት የሙስና ወንጀል መፈጸማቸውን በክሱ አቅርቧል፡፡
በተለይ በወንጀል ድርጊት አንድና ድርጊት ሁለት እንዳስቀመጠው፣ ተከሳሾቹ ጥራቱን ያልጠበቀ የወለል ንጣፍ (ቴራዞ) ግዥንና ከአቅራቢዎች ጋር በመመሳጠር፣ የሴራሚክስና የሸክላ ውጤቶችን ጨምሮ ያለ ጨረታና ከግዢ አዋጁ ጋር በሚጣረስ መንገድ ኃላፊዎቹና አቅራቢዎቹ በመመሳጠር ወንጀሉን መፈጸማቸውን ጨምሮ ያስረዳል፡፡
ተከሳሾቹ ዓርብ መስከረም 19 ቀን 2010 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ቀርበው የተመሠረባቸውን ክስ አዳምጠዋል፡፡ ከተከሳሾቹ ዘጠኙ በቁጥጥር ሥር ውለው ክሱን እየተከታተሉ ሲሆን፣ አራቱ ተከሳሾች በመሰወራቸው ክሱ በሌሉበት ተደምጧል፡፡ ተከሳሾቹ ቀደም ሲል ጳጉሜን 2 ቀን 2009 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ሲቀርቡ የዋስትና መብት ቢጠይቁም፣ ፍርድ ቤቱ ዓቃቤ ሕግ ያቀረበውን ጥያቄ በመቀበል አልፏቸው ነበር፡፡
ፍርድ ቤቱም ተከሳሾቹ ለማክሰኞ መስከረም 23 ቀን 2010 ዓ.ም. መቃወሚያቸውን እንዲያቀርቡና ዓቃቤ ሕግም መልስ እንዲሰጥበት ቀጠሮ በመስጠት ችሎቱ ተዘግቷል፡፡