[ለክቡር ሚኒስትር በጠዋቱ አንድ ወዳጃቸው ደወለላቸው]
- ሰላም ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እንዴት ነህ ወዳጄ?
- እንኳን ደስ አለዎት፡፡
- ደግሞ ለምኑ ነው?
- ሥራ ጀመረ አይደል እንዴ?
- ኧረ ገና የፊንሺንግ ሥራ እየሠራሁ ነው፡፡
- የምኑን ክቡር ሚኒስትር?
- ስለ ሕንፃዬ አይደል እንዴ የምታወራው?
- እኔ እንኳን ስለሕንፃዎት አልነበረም ያወራሁት፡፡
- ታዲያ ስለምንድን ነው የምታወራው?
- ፓርላማውን ማለቴ ነው፡፡
- እ… ተከፈተ አይደል?
- ክቡር ሚኒስትር ሙሉ ለሙሉ ዞሩ እንዴ?
- ወዴት ነው የምዞረው?
- ማለቴ የፓርላማውን ሥራ ትተው ወደ ንግዱ ዓለም ሙሉ ለሙሉ ገቡበት ወይ?
- የፖለቲካ ሥራዬንማ ሙሉ ለሙሉ አልተውኩትም፡፡
- እንደው ችላ ያሉት ስለመሰለኝ ነው?
- ፖለቲካውንማ እንዴት እተወዋለሁ? ለንግዱ መሠረት የሆነኝ ሥራ እኮ ነው?
- ታዲያ የፓርላማውን መከፈት አስመልክቼ እንኳን ደስ አለዎት ስልዎት ምንም አላስታወሱትም ብዬ ነው?
- የደወልከው እንኳን ደስ አለህ ለማለት ነው?
- የደወልኩት እንኳን በጣም ስለናፈቁኝ ነው፡፡
- አልገባኝም?
- እርስዎ እኮ አባቴ ማለት ነዎት፡፡
- ምን?
- ያው ልጅ አባቱ ጋ ቢደውል ምን አለበት?
- ምነው እንደዚህ ቀባባኸኝ?
- ኧረ እየቀባባሁዎት አይደለም፣ ከልቤ ነው፡፡
- አሁንም አስፈለገህ እንዴ?
- ምን ክቡር ሚኒስትር?
- ሌላ ብድር ነዋ፡፡
- ኧረ በፍጹም ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ታዲያ ምን ፈልገህ ነው?
- ክቡር ሚኒስትር ወዳጆች መሆናችንን ረሱት እንዴ?
- ወዳጅ መሆናችንንማ አውቃለሁ፣ ለዛ ከሆነ የደወልከው ደህና፡፡
- ግን እርስዎ ደስተኛ ነዎት?
- በምኑ?
- ማለቴ በሥራዎትም ብቻ በሁሉም ነገር፡፡
- ምንም እየገባኸኝ አይደለም፡፡
- ክቡር ሚኒስትር የእርስዎ ጤንነት እኮ ያሳስበኛል፡፡
- ከመቼ ጀምሮ?
- ምን ነካዎት ክቡር ሚኒስትር ከእርስዎ በላይ ለእኔ ማን አለ?
- ዛሬ በእርግጥ የፈለካት ነገር አለች ማለት ነው?
- ኧረ በእውነት ሰላም ለማለት ነው የደወልኩት፡፡
- ብቻ እንዳታስቀኝ?
- ምን ብዬ ክቡር ሚኒስትር?
- ይሰረዝልኝ ብለህ ነዋ፡፡
- ምኑ ክቡር ሚኒስትር?
- ብድሩ፡፡
- ክቡር ሚኒስትር እርስዎ እኮ በክፉ ቀኔ የደረሱልኝ ወዳጄ ነዎት፡፡
- እሱስ ትክክል ነህ፡፡
- እንደዚህ ዓይነት ነገር ላደርግም አልችልም፣ ላስብም አልችልም፡፡
- እንግዲያው ፓርላማው ሥራ ጀመረ ብለህ ከደወልክልኝ ደግሞ ሥራ ፈተሃል ማለት ነው?
- ክቡር ሚኒስትር የደወልኩት እንኳን አዘጋጅቼያለሁ ለማለት ነው፡፡
- ምኑን ነው ያዘጋጀኸው?
- ያው ከቅድም ጀምሮ ሲሉኝ አልነበረ?
- ብድሩን?
- አዎ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ምን ያህሉን ነው ያዘጋጀኸው?
- ሙሉውን ነው ያዘጋጀሁት ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ሁሉም እንዳንተ ቢሆን ደስ ይለኝ ነበር፡፡
- ክቡር ሚኒስትር እኔ እኮ ገና ለሕንፃዬ ያበድሩኛል ብዬ ስለማስብ በቃሌ ነው የምገኘው፡፡
- በዚህ እንኳን አትታማም፡፡
- እውነት ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ያው የብር ተመን ላይ ማሻሻያ መደረጉን ሰምተሃል፡፡
- እሱን ሰምቻለሁ፣ ከእኔ ብድር ጋር ምን አገናኘው ክቡር ሚኒስትር?
- መቼም በድሮ ተመን ልትከፍለኝ አልመጣህም?
- አልገባኝም ክቡር ሚኒስትር?
- መንግሥት ያወጣውን መመርያ ማክበር አለብህ፡፡
- ምን እያሉ ነው ክቡር ሚኒስትር?
- ብድሩን የምቀበልህ…
- እ…
- በአዲሱ ተመን ነው!
[ክቡር ሚኒስትሩ ከቤት ሊወጡ ሲሉ ልጃቸውን አገኙት]
- አንተ ትምህርት ቤት አትሄድም እንዴ?
- ዛሬ አልሄድም ዳዲ፡፡
- ለምን? የለም እንዴ?
- አለ ግን ሰስፔንድ ተደርጌ ነው፡፡
- ምን?
- ሰስፔንድ ተደርጌያለሁ፡፡
- ምንድነው የምትለው አንተ ልጅ?
- አስተማሪዬ ትናንትና ግቢ ውስጥ ረብሸሃል ብሎ ሰስፔንድ አደረገኝ፡፡
- እና ምንድን ነው የሚደረገው?
- ዛሬ ቤት ነው የምውለው ዳዲ፡፡
- ተበላሽተህልኛላ?
- ኧረ ምንም አልተበላሸሁም ዳዲ፡፡
- እኔ እንደውም ስለአንተ ብዙ ነገር ነው የምሰማው፡፡
- ምን ሰማህ ዳዲ?
- ተቆጣጣሪ የሌለው ዱርዬ ልጅ መሆንህን ሰምቻለሁ፡፡
- ኧረ ውሸት ነው ዳዲ፡፡
- ትምህርት ቤት አትገባም፣ መጠጥ ትጠጣለህ አሉ፣ ሲጋራም ጀምረሃል ሲሉ ሰምቻለሁ፡፡
- አሁን ይኼ ወሬ ተብሎ ለአንተ ተነግሮህ ነው?
- በጣም ጋጠወጥ ሆነሃል ማለት ነው፡፡
- ኧረ ዳዲ ፋራ አትሁን?
- ምን አልከኝ አንተ?
- ዳዲ እሱን ተወውና አንድ ጥያቄ አለኝ፡፡
- የምን ጥያቄ?
- መኪና ግዛልኝ፡፡
- ገና ከመሬት ሳትነሳ መኪና ግዛልኝ?
- ዳዲ በጣም ስለሚያስፈልገኝ መኪና ግዛልኝ?
- ለምንድን ነው የሚያስፈልግህ?
- ምክንያቴን የምናገረው አንድ ነገር ሲሆን ነው፡፡
- ምን ሲሆን?
- ጥያቄዬ ተቀባይነት ሲያገኝ!
[ክቡር ሚኒስትሩ ከሾፌራቸው ጋር ወደ ቢሮ እየሄዱ ነው]
- ምነው ዛሬ በጠዋት ፊትህ ጠቋቁሯል?
- ደብሮኝ ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ምን ሆነህ ነው የደበረህ?
- አየሩን ራሱ አይመለከቱትም? ፀሐይ ወጣ ስንል ዝናብ እየሆነ ያስደብረናል፡፡
- አንተ በሜትሮሎጂ ነው እንዴ ፊትህ የሚበራውና የሚጨልመው?
- ምን ክቡር ሚኒስትር ኑሮ ራሱ ከፍ ዝቅ እያለ ያሰቃየናል፡፡
- ይኼኔ ማታ አረቄህን ልፈህ ነው ጠዋት ደበረኝ የምትለው፡፡
- ክቡር ሚኒስትር ወድጄ እኮ አይደለም አረቄ የምጠጣው?
- ታዲያ ምን ሆነህ ነው?
- የኑሮ ውድነቱን ለመርሳት፡፡
- አረቄ ያስረሳል ብለህ ነው?
- ቢሳካልኝማ ውስኪ ነበር የምጠጣው?
- ስማ አረቄ በመጠጣትህ ደስ ነው ሊልህ የሚገባህ፡፡
- ለምን ክቡር ሚኒስትር?
- የአገር ውስጥ ምርትን እያበረታታህ ነዋ፡፡
- ኧረ አይቀልዱብኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ለማንኛውም የመንግሥት ፖሊሲ ትደግፋለህ ማለት ነው?
- ክቡር ሚኒስትር አንድ ጥያቄ ግን ነበረኝ፡፡
- የምን ጥያቄ?
- ደመወዝ ይጨመርልኝ፡፡
- ለምን?
- ምክንያቴን የምናገረው በአንድ ነገር ነው፡፡
- በምን?
- ጥያቄዬ ተቀባይነት ሲያገኝ!
[ክቡር ሚኒስትሩ ቢሮ ሲገቡ ጸሐፊያቸው ተከትላቸው ገባች]
- ደህና አደሩ ክቡር ሚኒስትር?
- እንዴት አደርሽ?
- ዛሬ ለአንድ ጉዳይ ነው የመጣሁት፡፡
- እንግዳ አለኝ እንዴ?
- እንግዳ እንኳን የለዎትም፡፡
- እሺ ምን ፈለግሽ?
- ይቺን ወረቀት ይመልከቷት፡፡
- የምን ወረቀት?
- እንኩ ይመልከቷት፡፡
- የሥራ መልቀቂያ ደብዳቤ?
- አዎን ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ምነው የተሻለ ሥራ አግኝተሽ ነው?
- አይ ክቡር ሚኒስትር የተሻለ ሥራ ከየት ይመጣል?
- ማለት?
- ያው በትምህርቴም ብዙ ስላልገፋሁ፣ የተሻለ ሥራ ከየት አመጣለሁ ብለው ነው?
- ታዲያ ሥራውን ጠልተሽው ነው?
- ክቡር ሚኒስትር እኔ የምፈልገው መልቀቅ ነው፡፡
- ባለፈው ለሠራሽው ሥራ የተከፈለሽ ኮሚሽን አንሶሽ ነው?
- ክቡር ሚኒስትር እኔ ይኼን ደብዳቤ ተቀብለውኝ ከሥራ ያሰናብቱኝ፡፡
- ለምንድን ነው የማሰናብትሽ?
- በቃ ከዚህ በኋላ ሥራውን መሥራት አልፈልግም፡፡
- እኮ ምክንያትሽ ምንድን ነው?
- እሱን የምናገረው አንድ ነገር ሲሟላ ነው፡፡
- ምን ሲሟላ?
- ጥያቄዬ ተቀባይነት ሲያገኝ!
[ክቡር ሚኒስትሩ ለምሳ ቤት ሲሄዱ ሚስታቸውን አገኟቸው]
- አንተ ምንድነው የሚወራው?
- ምን ሲወራ ደግሞ ሰማሽ?
- ያልደወለልኝ ሰው እኮ የለም፡፡
- እኮ ለምን?
- ሊለቅ ነው ወይ እያሉኝ ነዋ፡፡
- ምንድነው የምለቀው?
- ሥራህን ነዋ፡፡
- በቃ ቡና ላይ የሚወራውን ጐሲፕ እዚህ እንደ ቁምነገር ከእኔ ጋር ታወሪያለሽ አይደል?
- የቡና ጐሲፕ አይደለም፣ ብዙ ሰው ነው የደወለልኝ፡፡
- ፌስቡክ ላይ ተጥደሽ መዋል ጀመርሽ እንዴ?
- ተደውሎልኝ ነው አልኩህ እኮ?
- ለነገሩ ሥራ ስለሌለሽ ፌስቡክ ላይ ብትውይም አይገርመኝም፡፡
- ምን ላድርግ ሥራ እንደሆነ ከቀዘቀዘ ቆየ?
- አገሪቷ ላይም ሁሉ ነገር ተቀዛቅዟል፡፡
- በነገራችን ላይ ፌስቡክ ላይ የመመለሱን ዜና ሰምቼ ነበር፡፡
- ማን ነው የተመለሰው?
- ኤክስፖርት የተደረገው ስኳር፡፡
- አዎ ተመልሷል፡፡
- ታዲያ እናንተ መሸጥ ካልቻላችሁ ለእኔ ለምን አትሰጡኝም?
- ምን ሆነሻል ሴትዮ?
- ስማ እዚህ እኮ ኪሎ 50 ብር ደርሷል፡፡
- ስኳሩ የመንግሥት ዓይኑ ውስጥ ስለገባ እንደዛ ማድረግ ከባድ ነው፡፡
- አገር ውስጥ ብሸጠው ጥሩ ገንዘብ አገኝበታለሁ ብዬ ነው፡፡
- ይልቁኑ አንድ ሥራ እሰጥሻለሁ፡፡
- የምን ሥራ?
- ኮፍያና ቲሸርት እንድታትሚ አስደርጋለሁ፡፡
- ለምኑ?
- ለአቀባበል ፕሮግራሙ!
[ክቡር ሚኒስትሩ ቢሮ ሲገቡ አማካሪያቸውን አስጠሩት]
- አቤት ክቡር ሚኒስትር፡፡
- በአፋጣኝ ኮሚቴ ይቋቋም፡፡
- የምን ኮሚቴ?
- አንድ እንግዳ ወደ አገራችን እየመጣ ነው፡፡
- የምን እንግዳ?
- እሱን ተወውና አሁን መሥራት ያለብህን እነግርሃለሁ፡፡
- እሺ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- መጀመርያ ለአቀባበሉ ቲሸርትና ኮፍያ መታተም አለበት፡፡
- እሺ፡፡
- ለአቀባበሉ ፕሮግራም የሚጠሩ ሰዎች መመረጥ አለባቸው፡፡
- እሺ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ስለዚህ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት በአቀባበሉ ላይ መገኘት አለባቸው፡፡
- ማን ነው የሚጠራው?
- ሁሉም የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ አርቲስቶችና ታዋቂ ግለሰቦች መገኘት አለባቸው፡፡
- ሌላስ?
- ከሕዝብ ክንፍ፣ ከወጣቶች ፎረም፣ ከደጋፊ ነጋዴዎች ብቻ በአጠቃላይ ከተለያዩ አደረጃጀቶች እንግዶች ይጠራሉ፡፡
- ግን ይኼን ሁሉ ሰው የት ነው የምናስተናግደው?
- ስነግርህ ፕሮግራሙ ቀላል አይደለም፡፡
- መልካም ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ለእያንዳንዱ ተሳታፊ ኮፍያና ቲሸርት መዘጋጀት አለበት፡፡
- መቼ ጨረታ ልናወጣ?
- ጊዜ ስለሌለ እሱን ለእኔ ተወው፡፡
- አያስጠይቀንም ክቡር ሚኒስትር?
- ትልቅ እንግዳ እኮ ነው የሚመጣው?
- ለመሆኑ በቲሸርትና በኮፍያው ላይ ምንድነው የሚጻፈው?
- እንኳን ለአገርህ አበቃህ፡፡
- እንግዳው ኢትዮጵያዊ ነው እንዴ?
- እህሳ?
- ይኼን ያህል ክብር የተሰጠው እንግዳ ማን ነው?
- ስኳሩ!