Monday, May 29, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዓለምየዶናልድ ትራምፕና የሪፐብሊካኑ ሴናተር ቦብ ኮርከር ውዝግብ

የዶናልድ ትራምፕና የሪፐብሊካኑ ሴናተር ቦብ ኮርከር ውዝግብ

ቀን:

ሪፐብሊካኑ ሴናተር ሪፐብሊካኑን የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ አካሄድህ ትክክል አይደለም ሲሉ መንቀፍ የጀመሩት፣ ትራምፕ ሥልጣን ይዘው ወራት ያህል ሳይቆዩ ነበር፡፡ የሾሟቸውን ማንሳት፣ በሥራ ላይ የነበሩትም በሥራ ገበታቸው ወር ሳያገለግሉ መልቀቅም የትራምፕን አስተዳደር የፈተነ ጉዳይ ነው፡፡

ትራምፕ ሥልጣን ከያዙ በኋላ ያለው የሁለተኛው ስድስት ወራት ጅማሮ በተለይ ከሰሜን ኮሪያ ጋር እሰጣ ገባ የገቡበት ሲሆን፣ ይህም የኮሪያ ልሳነ ምድር አገሮችን ብቻ ሳይሆን የአሜሪካ ፖለቲከኞችን ጭምር ሥጋት ውስጥ የጣለ ነው፡፡

በዚህም ሳቢያ ሪፐብሊካን ፖለቲከኞች በትራምፕ ላይ ትችት እንዲሰነዝሩ ጋብዟል፡፡ ትችት ከሰነዘሩት ሪፐብሊካን ሴናተሮች መካከል ሰሞኑን የመገናኛ ብዙኃን መነጋገሪያ የሆኑት የቴኒሲ ሴናተር ቦብ ኮርከር ናቸው፡፡

የዶናልድ ትራምፕና የሪፐብሊካኑ ሴናተር ቦብ ኮርከር ውዝግብ

 

የሪፐብሊካኑ የውጭ ግንኙነት ኮሚቴ ሊቀመንበርና ትራምፕን በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ሲደግፉ የነበሩት ሴናተር ቦብ ኮርከር፣ ዋይት ኃውስ ‹‹የጎልማሶች የቀን መዋያ ሆኗል›› ሲሉ ትራምፕን ነቅፈዋል፡፡ ‹‹የትራምፕ ባህሪም አሜሪካን ወደ ሦስተኛ የዓለም ጦርነት ጎዳና እየመራት ነው፤›› ብለዋል፡፡

ኮርከር በትራምፕ ላይ ያላቸውን ቅሬታ በትዊተር ከገለጹ በኋላ ከኒውዮርክ ታይምስ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፣ ለአሜሪካውያን የሚያስብ ሁሉ የትራምፕ ድርጊት ሊመለከተው ይገባል ብለዋል፡፡

ከፖለቲከኞች፣ ከግለሰቦችና ከመገናኛ ብዙኃን ለሚሰነዘርባቸው ነቀፌታ እምብዛም ቦታ የማይሰጡትና ለማንኛውም አጀንዳ ያላቸውን ምላሽ ወዲያው በትዊተር ምላሽ የሚሰጡት ትራምፕ፣ ሴናተሩ በእሳቸው ላይ የሰነዘሩትን ነቀፌታ የመለሱት፣ ‹‹ኮርከር እ.ኤ.አ. በ2018 ለሚደረገው ዳግም አካባቢያዊ ምርጫ ድጋፍ ጠይቆኝ አይሆንም ስላልኩት ነው፤›› በማለት ነበር፡፡

የትራምፕ ስሜት የገነፈለውና ኮርከር ለቀጣዩ ምርጫ ለመሳተፍ አቅም የለውም ብለው እንዲናገሩ ምክንያት የሆነው፣ ኮርከር ባለፈው ሳምንት በትራምፕ ላይ በሰነዘሯቸው ነቀፌታዎች የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃንን ካጨናነቁ በኋላ ነው፡፡ እንደ ኮርከር፣ በትራምፕ አስተዳደር ውስጥ ያሉ ፖለቲከኞች የጎልማሶች መዋያ ያህል ድጋፍና ቁጥጥር እየተደረገባቸው ነው፡፡

የዶናልድ ትራምፕና የሪፐብሊካኑ ሴናተር ቦብ ኮርከር ውዝግብ

 

የሚሰነዘርባቸውን አስተያየትና ነቀፌታ በትዕግሥት የማያልፉትና ለቀረበባቸው ትችትና ለተላለፋቸው ሁሉ የመልስ ምት ለመስጠት ፈጣን የሆኑት ትራምፕ በትዊተራቸው፣ ‹‹ሴናተር ቦብ ኮርከር በ2018 ለሚኖረው የቴኔሲ ዳግም ምርጫ ድጋፍ እንድሰጠው ለምኖኝ ነበር፡፡ እኔም አይሆንም ብያለሁ፡፡ እሱም ያለ እኔ ድጋፍ ሊያሸንፍ እንደማይችል ነግሮኛለ፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መሆን እንደሚፈልግም ነግሮኛል፡፡ አይሆንም አመሰግናለሁ ብያለሁ፤›› ሲሉ አስፍረዋል፡፡

ኮርከር ዋይት ሐውስ ‹‹የጎልማሶች ቀን መዋያ›› ነው ማለታቸውንም ተከትሎ ትራምፕ፣ ‹‹ኮርከር ብቁ ያልሆነ ሴናተር ከመሆኑም በላይ ሥራውን በአግባቡ ያልተወጣ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ከኒውዮርክ ታይምስ ጋር ለ25 ደቂቃ በዘለቀው ቃለ መጠይቃቸው የትራምፕን አገር የመምራት አቅም ጥያቄ ውስጥ ያስገቡት ሴናተር ኮርከር፣ የፕሬዚዳንትነቱ ግዴለሽነት አሜሪካን አደጋ ውስጥ ጥሏታል ብለዋል፡፡ ይህንንም ብዙ ሪፐብሊካኖች እንደሚጋሩ አክለዋል፡፡

ትራምፕ አሜሪካ ከሰሜን ኮሪያ ጋር ስምምነት ለማድረግ በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ሬክስ ትሪልሰን የተጀመረውን ጥረት አቋርጫለሁ ብለው ባለፈው ሳምንት ትዊት ማድረጋቸውን ተከትሎም፣ ‹‹ትራምፕ ጉዳዮችን ትዊተር ላይ እያሰጣ እየጎዳን ነው፤›› ሲሉ ኮርከር ገልጸዋል፡፡

ኮርከር ከዚህ ቀደም በቻርሎትስቪል ነጭ ዘረኞች የፈጸሙትን ተግባር በተመለከተ ትራምፕ የነበራቸውን ምላሽ የነቀፉ ሲሆን፣ ፕሬዚዳንቱ መረጋጋትንም ሆነ የራሱን ብቁነት ማምጣት አልቻለም ብለዋል፡፡

ትራምፕን ከሚያስተቹ ጉዳዮች ቀዳሚውን የሚዲያ አጀንዳ የያዘው ከሰሜን ኮርያ ጋር ያላቸው ውዝግብ ነው፡፡ ኮርከርም የትራምፕ አካሄድ ወደ ሦስተኛው ዓለም ጦርነት ሊከተን ይችላል ሲሉ የገለጹት፣ ትራምፕ ሰሜን ኮሪያን ብልህነት በተሞላበት መንገድ አልያዙም በሚል ነው፡፡

ትራምፕም ሰሜን ኮሪያን በተመለከተ ያላቸውን አቋም በየጊዜው ትዊት እያደረጉ ያሳውቃሉ፡፡ ቢቢሲ እንዳሰፈረው፣ ትራምፕ ሰሞኑን በለቀቁት የትዊተር መልዕክታቸው ‹‹ለሰሜን ኮሪያ የሚሠራው አንድ ነገር ብቻ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ሆኖም ይህ አንድ ነገር ምን እንደሆነ አላብራሩትም፡፡ ባለፈው ሳምንት ትራምፕ ከከፍተኛ ወታደራዊ አዛዦች ጋር በነበራቸው የእራት ግብዣ፣ ‘ከፀጥታ በኋላ ማዕበል ይኖራል’ ማለታቸው መነጋገሪያ ሆኖ ነበር፡፡

የዶናልድ ትራምፕና የሪፐብሊካኑ ሴናተር ቦብ ኮርከር ውዝግብ

 

የአሜሪካ ፕሬዚዳንቶችና አስተዳደሩ ላለፉት 25 ዓመታት ከሰሜን ኮሪያ ጋር ለመነጋገር ቢጥሩም ውጤት አላመጡም የሚሉት ትራምፕ፣ ከዚህ ቀደም ‹‹አሜሪካ አስፈላጊ ከሆነና አሜሪካውያንና የአሜሪካ ወዳጆችን ለመከላከል ስትል ሰሜን ኮሪያን ታወድማታለች›› ማለታቸው ይታወሳል፡፡ ሆኖም እንዲህ ዓይነቱ ንግግራቸው በኮሪያ ልሳነ ምድር ለሚገኙ አገሮችም ሆነ ለሪፐብሊካንና በዴሞክራት የአሜሪካ ፖለቲከኞች የሚዋጥ አልሆነም፡፡ ትራምፕ ሰሜን ኮሪያ ላይ በተደጋጋሚ የሚሰነዝሩትን ዛቻ ከሚቃወሙ ሴናተሮች መሀል አንዱም ኮርከር ናቸው፡፡

የሰሜን ኮሪያ ፕሬዚዳንት ኪም ጆንግ ኡን የትራምፕን ዛቻ ከቁጣ ባለመቁጠር እሳቸውንም ሆነ አገራቸውን እያስጠነቀቁ ነው፡፡ አሜሪካንንም ሆነ አጋሮቿን በተለይ ጃፓንን የጥቃታቸው ዒላማ ማድረጋቸው በብዙዎች ዘንድ ሥጋት ፈጥሯል፡፡ የአሜሪካ የመከላከያ ሚኒስትር ጀምስ ማቲስ ሰሜን ኮሪያ በአሜሪካና በአጋሮቿ ላይ የጀመረችውን ዛቻ ማቆም አለባት በማለት ማስጠንቀቃቸው፣ ለሦስተኛው የዓለም ጦርነት መቀስቀስ ምክንያት እንዳይሆን ብዙዎች እየወተወቱ ነው፡፡

ትራምፕና ኮርከር እንዲህ ከመወዛገባቸውና ወደ ፖለቲካው ዓለም ከመግባታቸው በፊት የንግድ ኃላፊዎችና ባለቤቶች ሆነው ሠርተዋል፡፡ ሁለቱም የሪል ስቴትና የኮንስትራክሽን ኢንቨስትመንት ባለቤቶችም ናቸው፡፡ የመጡበት መንገድ ሁለቱን እንዲግባቡ ያደርጋቸዋል ተብሎ የተገመተና ለጋራ ጥቅም ሊሠሩ ይችላሉ ተብሎ ያስተቸ ቢሆንም፣ ይህ ግን አልሆነም፡፡ ሆኖም ኮርከር ከትራምፕ ቤተሰቦች ጋር ግላዊ ግንኙነት ከፈጠሩ ጥቂት ሴናተሮች አንዱ ናቸው፡፡

የዶናልድ ትራምፕና የሪፐብሊካኑ ሴናተር ቦብ ኮርከር ውዝግብ

 

 

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የመስቀል አደባባይ የመግቢያ ክፍያ ለምን?

ወጣቶች፣ ሕፃናትና አረጋውያን ሳይቀሩ መንፈሳቸውን የሚያድሱበት እንዲሁም ሐሳባቸውን በነፃነት...

በሕገ መንግሥቱ የተዋቀረው ‹‹የብሔር ፖለቲካ›› እና ‹‹ሥርዓቱ›› ያስከተለው መዘዝና መፍትሔው

(ክፍል አራት) በዓቢዩ ብርሌ (ጌራ) ባለፈው ጽሑፌ (በክፍል ሦስት) አሁን ያለው...

የኢትዮጵያ ኅብረተሰብና የመንግሥት መሪ ምሥል

በበቀለ ሹሜ በ2015 ዓ.ም. መጋቢት ወር ውስጥ ይመስለኛል በ‹ሸገር ካፌ›...

ዩኒቨርሲቲዎችን ራስ ገዝ ያደረገው አዋጅ የፍትሐዊነት ጥያቄ አስነሳ

በቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት ስምንት ዩኒቨርሲቲዎችን ራስ ገዝ በማድረግ ተቋማዊና...