Sunday, September 24, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

የክቡር ሚኒስትሩ ሾፌር በጠዋት ከቤት ሊወስዳቸው መጣ

  • ደህና አደርክ?
  • ሰላም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ምነው ፊትህ ጠቁሯል?
  • እንዴት አይጠቁር?
  • ምነው ቁጣ ቁጣ አለህ?
  • መሮኛል ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ጣፋጭ ነገር ውሰዳ፡፡
  • እኛማ አንድ የነበረንን ጣፋጭ ነገር ወሰዳችሁብን፡፡
  • የምን ጣፋጭ ነው የወሰድንብህ?
  • መቼም እንደ እርስዎ ኬክ ምናምን አልበላ? ስኳራችንን ካጠፋችሁብን ሰነባበታችሁ፡፡
  • ስኳር እኮ አይጠቅምም፣ እንደውም ለበርካታ በሽታዎች ያጋልጣል፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር የሚያሳዝነኝ መጥፎ መሆናችሁ አይደለም፡፡
  • ምን እያልክ ነው?
  • አሪፍ መጥፎ እንኳን አይደላችሁም፡፡
  • ምን ይዘባርቃል ይኼ?
  • ለማንኛውም ያኔ ትግል እንዴት ነበር የገቡት?
  • ምን እያልከኝ ነው?
  • ማለቴ ለመታገል ያነሳሳዎት ምንድን ነበር?
  • ያው ሕዝቡ ተበድሏል፡፡ ተጨቁኗል ብዬ አስብ ነበር፡፡
  • እሱ ነበር ምክንያትዎ?
  • በወቅቱ የነበረው መንግሥት አፋኝና ጨቋኝ ስለነበር ያንን ሥርዓት ለመጣል ነው የታገልኩት፡፡
  • ስለዚህ መንገዱን ጨርቅ ያድርግልህ እያሉኝ ነው?
  • ወዴት ልትሄድ ነው ደግሞ?
  • እኔም ልታገል ነዋ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • እኔ ጠፋሁ፣ ዋናውን ፀረ ልማት በጉያችን ታቅፈነው ነበር በለኛ?
  • ክቡር ሚኒስትር ፀረ ልማት ምናምን እያላችሁ የምታታልሉበት ጊዜ አልፏል፡፡
  • የምን ትግል ነው ታዲያ የምታወራው?
  • በቃ ትግል ያለበት ቦታ ሄጄ እታገላለሁ፡፡
  • እኛ ልማትና ሰላም አስፍነን አገሪቷን በለውጥ ጎዳና እያስጓዝናት ባለንበት ወቅት፣ በጉያችን ሆነህ ጦር ልትሰብቅብን?
  • ክቡር ሚኒስትር ዝም ብለው ልማት ልማት አይበሉኝ፡፡
  • ከዚህ በላይ ልማት ከየት ይምጣ?
  • የለሙት እኮ እርስዎ ነዎት ክቡር ሚኒስትር?
  • ምን?
  • ከእርስዎም በላይ ጓደኛዎና ዘመዶችዎ ናቸው የለሙት፡፡
  • አሁን አንተ ምን ጎደለብህ?
  • እስቲ የሞላልኝን ይንገሩኝ ክቡር ሚኒስትር?
  • ይኸው እንደ ባለሀብት በቪ8 ከተማው ላይ ትንቀባረራለህ፡፡
  • ዶሮን ሲያታልሏት በመጫኛ ጣሏት አሉ፡፡
  • ምን እያልከኝ ነው?
  • ክቡር ሚኒስትር እርስዎ ከፎቅ ፎቅ ሲዘሉ፣ እኔ እኮ ከመኪና መኪና ነው የተገላበጥኩት?
  • እሱንስ ማን አየበት?
  • አሁን ግን መሮኛል ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ምን ሆነህ?
  • ይኸው በጠራራ ፀሐይ እኮ ነው የተሰረቅነው፡፡
  • ቤትህ ሌባ ገባ እንዴ?
  • ቢገባስ ከእኔ ውጪ ምን ያገኛል ብለው ነው?
  • ታዲያ ማን ነው የሰረቀህ?
  • መንግሥት ነዋ የሰረቀኝ፡፡
  • እንዴት አድርጎ?
  • ባለፈው ሳምንት የነበረኝ 100 ብር በዚህ ሳምንት 85 ብር ሆኗል፡፡ ከዚህ በላይ ስርቆት አለ እንዴ?
  • የብር ተመን ስለመቀነሱ ነው የምታወራው?
  • እህሳ ክቡር ሚኒስትር?
  • ለዚህ እኮ ነው ትንሽም ቢሆን አንብብ የምልህ፡፡ ሌላው ቢቀር ሳወራ ብትሰማኝ እንኳን ትንሽ ዕውቀት ትገበይ ነበር፡፡
  • የብር የመግዛት አቅም ተዳክሟል ማለቴ ነው ዕውቀት የለህም ያስባለኝ?
  • በሚገባ እንጂ፡፡
  • እስቲ እርስዎ ያለዎትን ዕውቀት ያስጨብጡኝ?
  • የብር ተመን እንዲቀንስ የተደረገው እኮ ለአገሪቷ ዕድገት ታስቦ ነው፡፡
  • ምን?
  • ስማ ተመኑ በመቀነሱ ምክንያት የአገሪቷ ኤክስፖርት ይጨምራል፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር የሚጨምረው የአገሪቷ ኤክስፖርት ሳይሆን. . .
  • እ. . .
  • የእርስዎ ኪስ ነው!

 

[ክቡር ሚኒስትሩ ለምሳ ከቢሮ ሲወጡ ጸሐፊያቸውን አገኟት]

  • ምንድነው የያዝሽው ደግሞ?
  • የምሳ ዕቃ ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ትናትና ቤትሽ ድግስ ነበር እንዴ?
  • የምን ድግስ?
  • ማለቴ በጣም ልማታዊ ስለሆንሽ ለባንዲራ ቀን ደግሰሽ ከሆነ ብዬ ነው፡፡
  • ፅድቁ ቀርቶብኝ በቅጡ በኮነነኝ አሉ?
  • ምን እያልሽ ነው?
  • ክቡር ሚኒስትር በአሁኑ ወቅት እንኳን ልደግስ፣ ድግስ የሚጠራ
     ዘመድ ካገኘሁም ዕድለኛ ነኝ፡፡
  • ሰው ድግስ መደገስ ትቷል እያልሽኝ ነው?
  • ክቡር ሚኒስትር በቀን ሦስቴ መብላት ራሱ አስቸጋሪ እየሆነ መጥቷል ስልዎት?
  • ዝም ብለሽ አታማሪ ባክሽ?
  • ከዚህ በላይ ምን እስኪመጣ ልጠብቅ ታዲያ?
  • ምን መጥቶብሽ ነው እንደዚህ የምታማርሪው?
  • ትናንትና አስቤዛ ልገዛ ወጥቼ ነበር፡፡
  • እሺ?
  • በቅርቡ በችጋር እንደምመታ ነው የተረዳሁት፡፡
  • እንዴት?
  • ክቡር ሚኒስትር አንድ ፌስታል የሚሞላ ነገር መግዛት አልቻልኩም፡፡
  • ጨምረሽ አትገዥም ነበር?
  • ከየት አምጥቼ ክቡር ሚኒስትር?
  • በፊት ከየት ነበር የምታመጪው?
  • ገንዘቡን እኮ ዓረፋ አደረጋችሁት፡፡
  • ለምንድነው ዓረፋ የሆነው?
  • ገበያው እኮ ተበጥብጧል፡፡
  • ማን ነው የበጠበጠው?
  • መንግሥት ነዋ፡፡
  • ምን አድርጎ ነው የበጠበጠው?
  • ይኸው የብር የመግዛት አቅም ቀንሷል ተብሎ ሁሉም ዋጋ ላይ ጭማሪ ተደርጓል፡፡
  • ምን?
  • ክቡር ሚኒስትር በፊት ይዤ በምወጣው ብር ሦስትም አራትም ፌስታል እገዛ ነበር፡፡
  • እሺ፡፡
  • አሁን ግን አንድ ፌስታል እንኳን መግዛት አልቻልኩም፡፡
  • ማን ጨምሩ አላቸው?
  • የሚገርመው እኮ ከዶላር ጋር ግንኙነት የሌላቸው ነገሮች ራሳቸው ጨምረዋል፡፡
  • ለምሳሌ?
  • ከታክሲ ቤት ድረስ ለሚሸከምልኝ ልጅ የተለመደውን ስሰጠው አልቀበልም አለኝ፡፡
  • ለምን ተብሎ?
  • ዶላር ጨምሯል ብሎ ጨምሪ አለኝ፡፡
  • ይኼ እንዳይሆን እኮ አስፈላጊው ጥናት ተደርጎ ነበር፡፡
  • የምን ጥናት?
  • በዶላር ጭማሪ ምክንያት ዕቃ እንዳይንር ነዋ፡፡
  • የማይገናኙ ነገሮች ራሳቸው እየጨመሩ ናቸው ስልዎት?
  • መንግሥት እኮ አስፈላጊውን ቁጥጥር አደርጋለሁ ብሏል፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር የሸማቾችን ጥቅም አስጠብቃለሁ የሚለው ተቋም ምን እንደሚመስለኝ ያውቃሉ?
  • ምን?
  • ጥርስ የሌለው አንበሳ!

 

[የክቡር ሚኒስትሩ አማካሪ ቢሯቸው ገባ]

  • ክቡር ሚኒስትር ይኼን ደብዳቤ ይዩት፡፡
  • የምን ደብዳቤ ነው?
  • መጀመሪያ ይዩትና ምላሽዎትን ይሰጡኛል፡፡
  • ከውጭ አገር ግብዣ ተላከልኝ እንዴ?
  • ክቡር ሚኒስትር ደብዳቤውን የጻፍኩት እኔ ነኝ፡፡
  • ባለፈው አዘጋጅ ያልኩህን ሪፖርት አዘጋጀህ እንዴ?
  • ኧረ ለየት ያለ ጉዳይ ነው፡፡
  • ለየት ያለ ጉዳይ ስትል?
  • የሥራ መልቀቂያ ነው፡፡
  • ምን?
  • ክቡር ሚኒስትር ከዚህ በላይ በዚህ ሥራ ላይ መቆየት አልፈልግም፡፡
  • ምን ሆንኩ ብለህ ነው የምትለቀው?
  • ክቡር ሚኒስትር እኔ አሁን የምፈልገው መልቀቂያዬን እንዲቀበሉኝ ነው፡፡
  • አንተ ስትፈልግ እኮ አይደለም ከዚህ ሥራ የምትለቀው?
  • ምን እያሉ ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • የፓርቲያችንን ፖሊሲ ረሳኸው እንዴ?
  • የምን ፖሊሲ ነው?
  • ፓርቲው ጥበቃ አድርጎ ቢሾምህ እንኳን መሥራት አለብህ፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ከዚህ በኋላ በዚህ ኃላፊነት መቀጠል የማልችልበት በርካታ ምክንያቶች አሉኝ፡፡
  • ምን ዓይነት ምክንያቶች?
  • የማያቸው ነገሮች ሁሉ ደስ እያሉኝ አይደለም፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • የሕዝቡን ጥያቄ በተገቢው መሠረት ምላሽ መስጠት አልቻልንም፡፡
  • የምን ጥያቄ ነው?
  • በቃ አገሪቷ ላይ ሙሰኛ በዝቷል፡፡
  • ሙሰኛ በዝቷል ነው ያልከኝ?
  • ታዲያ ክቡር ሚኒስትር የዚህን የሙስና ጉዳይ ብንለው ብንለው ሊጠራ አልቻለም፡፡
  • ዋናው ሙሰኛ አንተ አይደለህ እንዴ?
  • ክቡር ሚኒስትር አይሳሳቱ፡፡
  • እንዴት?
  • በኪራይ ሰብሳቢነት ልጠረጠር እችላለሁ እንጂ ሙስናው ላይ የለሁበትም፡፡
  • ምን እያልህ ነው?
  • ይኸው ሦስት አራት ድርጅቶችን ከፍቼ እየተንቀሳቀስኩ እኮ ነው፣ እንዲያው ልማታዊ ባለሀብት ቢሉኝ ይቀላል፡፡
  • ታዲያ ሞስነህ አይደል እንዴ ባለሀብት የሆንከው?
  • እኔ ዕውቀቴን ተጠቅሜ ነው ባለሀብት የሆንኩት፡፡
  • እኔ እኮ የሚገርመኝ እንደዚህ ዓይነት ዓይን ያወጣ ውሸት ስትዋሽ ነው፡፡
  • እንዴት?
  • አንተ አይደለህ እንዴት በሾፌርህና በጋርድህ ሳይቀር የከተማውን ቦታ ስታሸነሽነው የነበርከው?
  • ማስረጃው አለዎት ክቡር ሚኒስትር?
  • ማስረጃ ተብለን ባንጠያየቅ ጥሩ ይመስለኛል፡፡
  • እንዴት?
  • ሰነድ መውጣት ከጀመረ እስር ቤቱ ላይበቃችሁ ነው፡፡ ዞሮ ዞሮ መልቀቂያዬን ይቀበሉኝ፡፡
  • ለምንድነው የምትለቀው?
  • ስለተነቃብኝ!

 

[ክቡር ሚኒስትሩ የፓርቲ ስብሰባ ላይ ተራቸው ደርሶ ከሰብሳቢው ጋር እያወሩ ነው]

  • እኔ የተባለውን ነገር ሰምቻለሁ፡፡
  • ምንድነው ታዲያ አስተያየትዎ ክቡር ሚኒስትር?
  • አንድ ግልጽ እንዲደረግልኝ የምፈልገው ነገር አለ፡፡
  • ምንድነው እሱ ክቡር ሚኒስትር?
  • ሕዝቡ በቃኝ እያለ ነው፡፡
  • በቃኝ ማለት?
  • አልፈልጋችሁም እያለን ነዋ፡፡
  • ምን እያሉ ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • ሕዝብን ማዳመጥ የለብንም ትላላችሁ?
  • ክቡር ሚኒስትር ሕዝቡ ምን እንደሚያስፈልገው እኮ የምናውቅለት እኛ ነን፡፡
  • እዚህ ጋ ግን አንድ ነገር መታየት አለበት እላለሁ፡፡
  • ምን ክቡር ሚኒስትር?
  • ሕዝቡ እኮ እምቢ እያለ ነው፡፡
  • ይኼን ነገር እኮ በተደጋጋሚ የተነጋገርንበት መሰለኝ፡፡
  • ምኑን?
  • የሕዝቡ ጥያቄ የሚያሳየው የአገሪቷ ኢኮኖሚ እያደገ መምጣቱን ነው፡፡
  • ለዛ ነው በየቀኑ የተቃውሞ ሠልፍ ያለው?
  • እሱማ ሰላማዊ ሠልፍ ስለተከለከለ ነው፡፡
  • ግራ የሚያጋባ ነገር ነው እኮ ነው የምታወሩት፡፡
  • ምኑ ነው ግራ የገባዎት?
  • ሕዝቡ አልፈልግም ይላል፣ እኛ ደግሞ ለሕዝብ እናውቃለን እያልን ነው፡፡
  • እርስዎ ይኼን ያህል ዓመት ፖለቲካ ውስጥ ቆይተው የምን መልፈስፈስ ነው?
  • ተልፈስፍሼ አይደለም፡፡
  • ለመሆኑ እርስዎ በልተው ጠግበዋል እንዴ?
  • ቆይ ቆይ እኔ ስለመብላቴ ማስረጃ አለህ?
  • ይኼን በሌላ ስብሰባችን እናየዋለን፡፡
  • በየትኛው ስብሰባ?
  • ሂስና ግለ ሂስ በምንውጥበት፡፡ ለማንኛውም ሕዝቡ ልቀቁ እያለን ነው፡፡
  • እኛ ለቃቂዎች አይደለንም፡፡
  • እና ምንድን ነን?
  • አስለቃቂዎች!

 

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

በቀይ ባህር ፖለቲካ ላይ በመከረው የመጀመሪያ ጉባዔ ለዲፕሎማቲክና ለትብብር አማራጮች ትኩረት እንዲሰጥ ጥሪ ቀረበ

ሰሞኑን በአዲስ አበባ ለመጀመርያ ጊዜ በቀይ ባህር ቀጣና የፀጥታ...

የቤት ባለንብረቶች የሚከፍሉትን ዓመታዊ የንብረት ታክስ የሚተምን ረቂቅ አዋጅ ተዘጋጀ

በአዋጁ መሥፈርት መሠረት የክልልና የከተማ አስተዳደሮች የንብረት ታክስ መጠን...

እንደ ንብረት ታክስ ያሉ ወጪን የሚያስከትሉ አዋጆች ከማኅበረሰብ ጋር ምክክርን ይሻሉ!

የመንግሥትን ገቢ በማሳደግ ረገድ አስተዋጽኦ እንዳላቸው የሚታመኑት የተጨማሪ እሴት...

ለዓለምም ለኢትዮጵያም ሰላም እንታገል

በበቀለ ሹሜ ያለፉት ሁለት የዓለም ጦርነቶች በአያሌው የኃያል ነን ባይ...

የመጀመርያ ምዕራፉ የተጠናቀቀው አዲስ አበባ ስታዲየም የሳር ተከላው እንደገና ሊከናወን መሆኑ ተሰማ

እስካሁን የሳር ተከላውን ጨምሮ 43 ሚሊዮን ብር ወጪ ተደርጓል ዕድሳቱ...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ ለሁለት ቀናት የተካሄደውን የፓርቲያቸውን የሥራ አስፈጻሚ ስብሰባ አጠናቀው ወደ ቢሯቸው ሲመለሱ ቢሯቸው ውስጥ አማካሪያቸው አንድ ጽሑፍ በተመስጦ እያነበበ አገኙት]

ምንድነው እንደዚህ መስጦ የያዘህ ጉዳይ? መጡ እንዴ ክቡር ሚኒስትር፣ የፓርቲው ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ያወጣውን መግለጫ እያነበብኩ ነው፡፡ ግን እኮ ፊትህ ላይ የመገረም ስሜት ይነበባል፡፡ አዎ፣ መግለጫው ላይ...

[ክቡር ሚኒስትሩ እየጠራ ያለውን ሞባይል ስልካቸውን ተመለከቱ፣ የህዳሴ ግድቡ ተደራዳሪ መሆናቸውን ሲያውቁ ስልኩን አነሱት]

ሃሎ... ጤና ይስልጥኝ ክቡር ሚኒስትር? ጤና ይስልጥልኝ ክቡር ተደራዳሪ... የጥረትዎን ፍሬ በማየትዎ እንኳን ደስ አለዎት፡፡ እንኳን አብሮ ደስ አለን፣ ምን ልታዘዝ ታዲያ? የውኃ ሙሌቱንና አጠቃላይ የግድቡን የግንባታ ሁኔታ...

[የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሩ ክቡር ሚኒስትር ሌሊቱን በእንቅልፍ ልባቸው በህልም እየተወራጩ ሳለ የሞባይል ስልካቸው ጥሪ አነቃቸው። አለቃቸው ስለነበሩ ስልኩን በፍጥነት አነሱት]

በሌሊት ስለደወልኩኝ ይቅርታ፡፡ ችግር የለውም ክቡር ሚኒስትር፣ ምን ልታዘዝ? አንድ የአውሮፓ ባለሥልጣን ነገ በጠዋት ወደ አዲስ አበባ ይገባል። እሺ። ሌሎች የመንግሥት አመራሮች ስላልቻሉ እርስዎ መንግሥትን ወክለው ቦሌ ኤርፖርት...