አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በኢትዮጵያ ፕሬስ ኤጀንሲ (አዲስ ዘመን ጋዜጣ) እና የሐበሻ ወግ የተሰኘው የግል መጽሔትና አዘጋጆቻቸው ላይ መሥርቶት የነበረውን ክስ አቋረጠ፡፡
ዩኒቨርሲቲው በአዲስ ዘመንና በሐበሻ ወግ መጽሔት ላይ በ2009 ዓ.ም. እና በ2007 ዓ.ም. ከኦዲት ሒሳብ አለመዘጋት ጋር በተገናኘ ባወጧቸው ጽሑፎች የስም ማጥፋት ተደርጎብኛል በማለት፣ ጥር 15 ቀን 2009 ዓ.ም. በፌዴራል የመጀመርያ ፍርድ ቤት በአራዳ ምድብ ፍትሐ ብሔር ምድብ ችሎት ክስ መመሥረቱን መዘገባችን ይታወሳል፡፡ በዚሁ ክስም ከሁለቱም የኅትመት ተቋማት የ200 ሺሕ ብር ካሳ መጠየቁ አይዘነጋም፡፡
ነገር ግን ተከሳሾቹ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ዩኒቨርሲቲው ባለፈው ሳምንት ክሱን አቋርጧል፡፡ ለክሱ መቋረጥ ምክንያቱ ምን እንደሆነ ግን ከመናገር ተቆጥበዋል፡፡
ሁለቱ የኅትመት ተቋማትን ጨምሮ አምስት ተከሳሾች በሐሰት የኅትመት ሥራ የዩኒቨርሲቲውን ስምና ዝና፣ እንዲሁም በሕዝብ ዘንድ ያለውን ተቀባይነት ሆነ ብለው አስበው ያደረጉትን ድርጊት ለማሳረምና ከሳሽ ላይ ለደረሰው የሞራል ጉዳት ካሳ ለመጠየቅ አዋጅ ቁጥር 590/2000 አንቀጽ 41(2) መሠረት አድርጎ ነበር ክስ የመሠረተው፡፡
በተጠቀሰው የአዋጁ አንቀጽ መሠረት ከአንደኛ እስከ አምስተኛ የዘረዘራቸው ተከሳሾች በጠቅላላ 200 ሺሕ ብር የሆነ የሞራል ካሳ እንዲከፍሉት ፍርድ ቤቱን ስለመጠየቁ መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ክስ ተመሥርቶባቸው የነበሩትም አንደኛ ተከሳሽ ቴዲ አብ መልቲ ሚዲያና ኢንተርቴይንመንት (የሐበሻ ወግ መጽሔት) ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር፣ ሁለተኛ ተከሳሽ ከፍተኛ አዘጋጅ አቶ ዮናስ ወልደ ሰንበት፣ ሦስተኛ ተከሳሽ ዋና አዘጋጅ ወ/ሮ ጽጌሬዳ ገብረ ማርያም፣ አራተኛ ተከሳሽ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት (አዲስ ዘመን ጋዜጣ)፣ አምስተኛ ተከሳሽ አቶ አጎናፍር ገዛኸኝ የአዲስ ዘመን ጋዜጣ አዘጋጅ ናቸው፡፡
አዲስ ዘመን ጋዜጣ ነሐሴ 9 ቀን 2007 ዓ.ም. ዩኒቨርሲቲውን አስመልክቶ፣ ‹‹ለአምስት ዓመታት ኦዲት ያልተደረገ ተቋም››፣ እንዲሁም ኅዳር 7 ቀን 2009 ዓ.ም. ‹‹የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የስድስት ዓመታት የኦዲት ሪፖርት አይታወቅም›› የሚሉ ዘገባዎችን ለኅትመት በማብቃቱ ምክንያት ክስ ተመሥርቶበት ነበር፡፡
ሪፖርተር በጉዳዩ ላይ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ኃላፊዎችና ከሚመለከታቸው አካላት አስተያየት ለማግኘት ያደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡