በዚህ ወር መጨረሻ በሚካሄደው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ሁለት የቀድሞው አመራሮች በዕጩነት መቅረባቸው ተሰማ፡፡
ጥቅምት 30 ቀን 2010 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ሒልተን እንደሚካሄድ በሚጠበቀው የብሔራዊ ፌዴሬሽኑ መደበኛ ጠቅላላ ጉባዔና ምርጫ፣ ለፕሬዚዳንታዊ ምርጫ በዕጩነት ከቀረቡት መካከል የቀድሞ የፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት አሸብር ወልደጊዮርጊስ (ዶ/ር) ከደቡብ፣ እንዲሁም የቀድሞው ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ተካ አስፋው ከአማራ ይጠቀሳሉ፡፡ አሁን በሥልጣን ላይ የሚገኙት አቶ ጁነዲን ባሻ ከድሬዳዋ፣ አቶ አንተነህ ፈለቀ ከኦሮሚያና አምባሳደር ቶፊቅ አብዱላሂ ከሐረሪ በምርጫው እንደሚሳተፉ ከተጠቀሱት ናቸው፡፡
ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ድረስ ለብሔራዊ ፌዴሬሽኑ ዕጩዎችን በይፋ ያስታወቀው የአማራ ክልል እግር ኳስ ፌዴሬሽን ብቻ እንደሆነ የፌዴሬሽን ምንጮች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ የአማራ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ያቀረባቸው አቶ ተካ አስፋው የዳሸን ባንክ ቦርድ ሰብሳቢ ሲሆኑ፣ ለሥራ አስፈጻሚነት ደግሞ የቀድሞ የዋሊያዎቹ ዋና አሠልጣኝ አቶ ሰውነት ቢሻው መሆናቸው ታውቋል፡፡
እንደ ምንጮች ከሆነ፣ በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ፕሬዚዳንት በመሆን በማገልገል ላይ የሚገኙት አሸብር ወልደጊዮርጊስ (ዶ/ር) ለፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ከደቡብ ክልል ተወክለዋል፡፡ ለሥራ አስፈጻሚ ምርጫ ደግሞ አሁን በአመራር ላይ የሚገኙት አቶ ዘሪሁን ቀቀቦ እንደሆኑ እየተነገረ ይገኛል፡፡
በአራት ዓመት አንድ ጊዜ በሚደረገው የፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንታዊና የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ምርጫ እያንዳንዱ ክልልና የከተማ አስተዳደር የሚያቀርቧቸው ዕጩዎች ማንነትና ምንነት በይፋ የሚታወቀው፣ ረቡዕ ጥቅምት 15 ቀን 2010 ዓ.ም. መሆኑ ፌዴሬሽኑ አስታውቋል፡፡
ከመዋቅራዊ ይዘትና ውሳኔ አሰጣጥ ጋር ተያይዞ ከፍተኛ ትችትና ወቀሳ ከሚቀርብባቸው የስፖርት ተቋማት መካከል የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳል፡፡ የዘርፉ ሙያተኞች ከዚሁ በመነሳት ዕጩዎችን የማቅረብ ሥልጣኑ ያላቸው ክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች፣ ለምርጫ የሚያቀርቧቸውን ተወካዮች በጥንቃቄ ሊመርጡ እንደሚገባ ይጠይቃሉ፡፡ እንደ ሙያተኞቹ፣ እያንዳንዱ ክልልና ከተማ አስተዳደር እስከዛሬ ከነበረው ‹‹ሠርገኛ መጣ. . .›› ዓይነት አሠራር ተላቆ ለወደፊቱ ዕጩዎቻቸውን ቀደም ብለው በማሳወቅ በሚዲያው አማካይነት የስፖርት ቤተሰቡና ሙያተኞች አስተያየት እንዲሰጡባቸው ቢያደርጉ የተሻለውን ለመለየትና ለመምረጥ እንደሚያመች ጭምር ያስረዳሉ፡፡