ሜሪ ጆይ የልማት ማኅበር ከሚያሳድጋቸው ወላጆቻቸውን ካጡ ሕፃናትና ወጣቶች መካከል ለ17 ያህሉ በድምሩ 160 ሺሕ ብር፣ ታህሳስ 30 ቀን 2007 ዓ.ም. በዕርዳታ ተበረከተላቸው፡፡ ዮድ አቢሲኒያ የባህል ምግብ አዳራሽ ባከናወነው ሥነ ሥርዓት ላይ ዕርዳታው ከተበረከተላቸው መካከል 16 ሕፃናት እያንዳንዳቸው አሥር ሺሕ ብር፣ አንድ ሌላ ታዳጊ ወጣት ደግሞ ላፕቶፕ አግኝተዋል፡፡ ገንዘቡን ያበረከቱት አቶ ቴዎድሮስ ሽፈራው የተባሉ ባለሀብት ሲሆኑ፣ ላፕቶፑን የለገሰው ደግሞ በአሜሪካ ሚኒሶታ የተቋቋመው ወገን ለወገን የተባለው ማኅበር ነው፡፡ ማኅበሩ ገዝቶ የሰጠውን ላፕቶፕ በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት የሁለተኛ ዓመት የኮምፒዩተር ኢንጂነሪንግ ተማሪ ለሆነው ወጣት ማኅበሩን ወክለው ያስረከቡት በማኒሶታ ከተማ ነዋሪና የማኅበሩ አባል የሆኑት አቶ ዳዊት ይትባረክ ናቸው፡፡ አቶ ቴዎድሮስ የገንዘቡን ቼክ ለሜሪ ጆይ መሥራችና ዋና ሥራ አስኪያጅ ሲስተር ዘቢደር ዘውዴ ካስረከቡ በኋላ ዕርዳታውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ቃል ገብተዋል፡፡ ሲስተር ዘቢደር የገንዘብ ዕርዳታ ከተደረገላቸው ሕፃናት መካከል ከኤችአይቪ ጋር አብረው የሚኖሩ እንደሚገኙባቸው፣ በድርጅቱ ከመታቀፋቸው አስቀድሞ ብዙዎቹ ካገኙ በልተው ካጡ ደግሞ ባዶ ሆዳቸውን በቱቦ ውስጥ ይኖሩ እንደነበር ተናግረዋል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ዮድ አቢኒሲያ የባህል ምግብ አዳራሽ ለበርካታ አረጋውያንና ወላጅ አልባ ሕፃናት በዚሁ ዕለት የምሳ ግብዣ አድርጐላቸዋል፡፡