በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ካዛንችስ አካባቢ የሚገኘው ዮርዳኖስ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር (ዮርዳኖስ ሆቴል) ፍርድ ቤቶች እንዲከፍል የወሰኑበትን ክፍያ ሊፈጽም ባለመቻሉ፣ ተሽከርካሪው ተሸጦ ለፍርድ ባለመብት ከነወለዱ እንዲከፍል ትዕዛዝ ተሰጠ፡፡ ሆቴሉ ትዕዛዝ የተላለፈበት አቶ ንጉሤ ከፈለኝ የተባሉ ግለሰብ፣ ከውጭ ወደ አገር ቤት ለሚመጡ እንግዳ የተከራዩትን የመኝታ ክፍል እንደማይጠቀሙበት በማሳወቅ፣ የከፈሉት ገንዘብ እንዲመለስላቸው ፍርድ ቤት ውሳኔ በማስተላፉ ነው፡፡ ግለሰቡ ከውጭ አገር ለሚገቡት እንግዳቸው በደረሰኝ ቁጥር 33746፣ 11,648 ብርገንዘብ ከከፈሉ በኋላ፣ እንግዳቸው ወደ አገር ውስጥ ሊገቡ የማያችስል ችግር እንደገጠማቸው ሲነግሯቸው፣ ለማደሪያ የተከራዩትን ክፍል ጊዜው ከመድረሱ አንድ ሳምንት (ስምንት ቀናት) በፊት ለሆቴሉ በማሳወቅ እንዲመልስላቸው መጠየቃቸውን ክሱ ያስረዳል፡፡ ሆቴሉ ሊከፍላቸው ፈቃደኛ ባለመሆኑ በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍትሐ ብሔር ፍርድ ቤት ክስ በመመሥረት፣ የሆቴሉን ሠራተኞች ምስክር ቆጥረው ባደረጉት ክርክር ሆቴሉን ይረታሉ፡፡ ሆቴሉ ወደ ከፍተኛ ፍትሐ ብሔር ፍርድ ቤት ይግባኝ በማለት ክፍያውን ሳይፈጽም ቢቆይም፣ ከፍተኛው ፍትሐ ብሔር ፍርድ ቤትም የሆቴሉን ይግባኝ ውድቅ በማድረግ የሥር የፍርድ ቤትን ውሳኔ ያፀናል፡፡ መሠረታዊ የሕግ ጥሰት እንደተፈጸመበት በመግለጽ ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት አቤት ያለው ዮርዳኖስ ሆቴል፣ በውሳኔው ላይ የተለየ የሕግ ስህተት እንዳልተፈጸመ በመግለጽ ‹‹አያስቀርብም›› ተብሎ በሆቴሉ ስም የተመዘገበውን የሆቴል ንብረት የሆነውን፣ ኮድ 3-80341 ተሽከርካሪ ተሽጦ ከዘጠኝ በመቶ ወለድ ጋር ለፍርድ ባለመብት እንዲከፍል ታኅሳስ 23 ቀን 2007 ዓ.ም የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት፣ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ምድብ አምስተኛ አፈጻጸም ችሎት ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡