የዘጠኙ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ትብብር ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የመድብለ ፓርቲ ሥርዓትን በር ለመዝጋት እየተንቀሳቀሰ ነው ሲል ቅሬታውን ገለጸ፡፡ ትብብሩ ይኼን ያስታወቀው ጥር 4 ቀን 2007 ዓ.ም. በሰማያዊ ፓርቲ ጽሕፈት ቤት በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ነው፡፡ ምርጫ ቦርድ ከሕግ አግባብ ውጪ የፓርቲዎችን ትብብር ‹‹ሕገወጥ›› በማለት በአባል ፓርቲዎቹ መካከል ‹‹አሰባሳቢና ተሰብሳቢ›› እንዳለ በማስመሰል፣ አለመተማመን ለመፍጠር የሚያደርገው እንቅስቃሴ ተቀባይነት የሌለው ነው ሲሉ የትብብሩ ዋና ጸሐፊ አቶ ግርማ በቀለ ገልጸዋል፡፡ የትብብሩ አባል ፓርቲ የሆነውን ሰማያዊ ፓርቲ ምርጫ ቦርድ ‹‹ትብብር በሚል ማሰባሰብን›› እንደ ጥፋት ቆጥሮ ይቅርታ እንዲጠይቅ ደብዳቤ መጻፉ ተገቢነት የሌለውና ትብብሩ የሚያወግዘው መሆኑን አስታውቋል፡፡ ‹‹ነገር ግን ቦርዱ በአደባባይ ፓርቲዎችን በእኩል ዓይን ነው የምመለከተው፣ በሆደ ሰፊነት እያስተናገድኩ ነው ቢልም፣ በፓርቲዎች መካከል አድልኦ እንደሚፈጽም በማስረጃ ማሳየት እንደሚችል ማሳያ ነው፤›› በማለት ገልጿል፡፡ የቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ ዶ/ር አዲሱ ገብረ እግዚአብሔር፣ ‹‹ሰማያዊ ፓርቲ ከአንዳንድ ፓለቲካ ፓርቲዎች ጋር መልካም ግንኙነት በማድረጉና የተለያዩ ጉዳዮችን እያነሳ ሥራውን ማከናወኑ ላይ ችግር የለውም፤›› ብለው ‹‹ከሕግ ውጪ የሚደረግ አደረጃጀት ኢሕጋዊ ስለሆነ መሠረት የለውም ነው በቦርዱ እየተባለ ያለው፤›› በማለት ጥር 5 ቀን 2007 ዓ.ም. በሒልተን ሆቴል በተሰጠ መግለጫ ገልጸዋል፡፡ ቦርዱ ለሰማያዊ ፓርቲ በጻፈው ደብዳቤ ትብብሩን አባል ፓርቲዎችን በማበላለጥ አሰባሳቢና ተሰብሳቢ፣ የሁከት ጠንሳሽና ጀሌ፣ በማለት ያለመተማመን ስሜት በመፍጠር ለመከፋፈል ያደረገው ሙከራን መጥቀስ ይቻላል በማለት ትብብሩ በመግለጫው አስረድቷል፡፡ ፓርቲዎች በትብብር የጋራ አቋም ለመውሰድም ሆነ የጋራ ተግባር ለመፈጸም የቦርዱ ዕውቅና እንደማያስፈልግ፣ ከዚህ በፊት ለበርካታ ጊዜያት ፓርቲዎች በጋራ የጠሯቸውን ሰላማዊ ሠልፎች፣ በሕጋዊ ሰውነታቸው የመሠረቷቸውን ግንኙነቶች (የኢተፓዴኅ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት፣ መኢአድ፣ አብኮ፣ ደቡብ ኅብረት፣ ኅብረትና አማራጭ የመሠረቱትን) የመሳሰሉትን እያወቀ ትብብሩ ላይ ለምን ቀነሰ ብሏል፡፡ በተጨማሪም ገዢው ፓርቲ አምስት ክልሎችን ከሚመሩ ፓርቲዎች ጋር አጋር በሚል የሚያደርገው ግንኙነት ከትብብሩ ቀርቶ በግንባር ከተደራጁ ያለፈና የጠነከረ መሆኑ የአደባባይ ሚስጥር ሆኖ ለዘመናት በዘለቀበትና አንድም ቀን ጥያቄ ባላነሳበት ትብብሩን መተቸቱ ተገቢ አይደለም በማለት ኮንኗል፡፡ ‹‹ትብብራችን በእንቅስቃሴ በገዢው ፓርቲ ላይ የፍርኃት ስሜት ሥጋት መፍጠሩን፣ ለዚህም ምርጫ ቦርድ ይህን ዓይነቱን ሕገወጥ ፖለቲካዊ ድጋፍ ለኢሕአዴግ በመገናኛ ብዙኃን በማሰራጨት ሕዝቡ የሚሰጠንን ሁለንታዊ ድጋፍ ለመግታት ወይም ፈሪ ከተገኘ ለማስፈራራትና ለማሸማቀቅ የሚደረግ ተራ ፕሮፓጋንዳ ነው፤›› በማለት ምርጫ ቦርድን ተችቷል፡፡