የአዲስ አበባ ከተማ እሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከያና መቆጣጠሪያ ባለሥልጣን፣ ከሁለት ወራት በፊት በእቴጌ ጣይቱ ሆቴል ላይ ቅኝት ማድረጉንና በቅኝቱ ወቅት ሆቴሉ ለአደጋ ተጋላጭ መሆኑን ለሆቴሉ ማኔጅመንት ማሳወቁን ገለጸ፡፡ የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ኮማንደር አለነ ገብሩ ባለፈው ዓርብ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ የባለሥልጣኑ ባለሙያዎች በጣይቱ ሆቴል ሁለት ጊዜ ፍተሻ አካሂደዋል ብለዋል፡፡ በፍተሻዎቹ ሆቴሉ ለአደጋ የተጋለጠ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ኮማንደር አለነ እንዳሉት፣ በሆቴሉ ጅምር የእሳት ማጥፊያ መሣሪያ አልተሟላም፡፡ የሆቴሉ ሠራተኞች ስለጅምር እሳት ማጥፊያ መሣሪያ ግንዛቤ የላቸውም፡፡ የኤሌክትሪክ መስመሮች በአግባቡ አልተዘረጉም፡፡ በሆቴሉ የደኅንነት ምልክቶች የሉም፡፡ ‹‹እነዚህ ግድፈቶች እንዲስተካከሉ ለመጨረሻ ጊዜ በኅዳር ወር 2007 ዓ.ም. ለሆቴሉ ኃላፊዎች ተገልጿል፤›› በማለት ኮማንደር አለነ ባለሥልጣኑ ቀደም ብሎ ለመከላከል ሞክሮ እንደነበር አስረድተዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም አደጋው ከተከሰተ በኋላ የአዲስ አበባ እሳት አደጋ ማጥፊያ ብርጌድ ያካሄደው ተጋድሎ ሊደነቅ እንጂ ሊወቀስ እንደማይገባ ኮማንደሩ አስታውቀዋል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ለባለሥልጣኑ ጥሪ የደረሰው እሑድ ጥር 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ከረፋዱ 3 ሰዓት ከ08 ደቂቃ ላይ ነው ይላሉ፡፡ ለባለሥልጣኑ ጥሪ እንደደረሰ አንድ እሳት አጥፊ ተሽከርካሪ በሁለት ደቂቃ ውስጥ ቦታው ደርሷል፡፡ ነገር ግን በሥፍራው የደረሰው ተሽከርካሪ ቃጠሎው ከአቅሙ በላይ እንደሆነ ሪፖርት በማድረጉ ከሰባቱም ጣቢያዎች እሳት አጥፊ ተሽከርካሪዎች እንዲንቀሳቀሱ ተደርጓል ብለዋል፡፡ ሁለተኛው ተሽከርካሪ በአምስት ደቂቃ ውስጥ ከሜክሲኮ ጣቢያ ተነስቶ መድረሱን ኮማንደሩ አክለዋል፡፡ ‹‹የባለሥልጣኑ እሳት አጥፊ ብርጌድ ባካሄደው ተጋድሎ ሆቴሉን ከሙሉ በሙሉ ውድመት ታድጎታል፡፡ በዚህም ሊመሰገን እንጂ ሊወቀስ አይገባውም፤›› በማለት ኮማንደሩ ተናግረዋል፡፡ ‹‹አደጋው እንደደረሰና ጉዳቱ ከባድ እንዲሆን ያደረጉት የሆቴሉ ባለቤቶች ናቸው፡፡ ለሆቴል ደኅንነት ዋስትናው መጀመርያ የሚደረግ ጥንቃቄ ነው፡፡ የአደጋው መንስዔ ኤሌክትሪክ በመሆኑ የሆቴሉ ባለቤቶች ኃላፊነት ሊወስዱ ይገባል፡፡ በዚህ ጉዳይ ባለሥልጣኑን መውቀስ ተገቢ አይደለም፤›› ሲሉ ኮማንደር አለነ መከራከሪያቸውን አቅርበዋል፡፡ ታሪካዊው እቴጌ ጣይቱ ሆቴል ቅርስ እንደመሆኑ ግምቱ ለጊዜው የማይታወቅ ጉዳት ደርሶበታል፡፡